በግድቡ ሕይወታቸው የተገደበ ኢትዮጵያውያንን ለማትረፍ የሚደረገው እርብርብ

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

ORB 10

 

ከሁለት ዓመታት በፊት በዚህ በያዝነው ወር “ግድቡ እና አደጋው፡ ግልገል ጊቤ ሦስት በኢትዮጵያ“ በሚል ርዕስ በደቡብ ኢትዮጵያ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ከሚካሄደው ልማት ጋር በተያያዘ መልኩ ግድቡ ሊያስከትል በሚችለው እንደምታ ላይ ትኩረት በማድረግ ትንታኔ አቅርቤ ነበር፡፡ በዚያ ትንታኔዬ በዚህ የልማት ሰበብ እየተካሄደ ያለው እንቅስቃሴ በአካባቢው ስነምህዳር ላይ የሚያስከትለውን አሉታዊ ተጽእኖ እና ግድቡ በአካባቢው ለዘመናት ሰፍረው በሚኖሩት ህዝቦች ህይወት ላይ የሚያስከትለውን ኢኮኖሚያዊ፣ ባህላዊ እና ማህበራዊ ቀውስ ከግምት ውስጥ በማስገባት በተለያዩ ዓለም አቀፋዊ የሰብአዊ መብት ተሟጋች እና የአካባቢ ጥበቃ ድርጅቶች መንግስት ከዚህ ድርጊቱ እንዲታቀብ ድምጻቸውን ሲያሰሙ እኔም የሀሳቡ ተጋሪ በመሆን የነበረኝን ጥልቅ ስጋት በተደጋጋሚ አሰምቸ ነበር፡፡

ከዚህም በተጨማሪ “በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ያለውን ምቹ ያልሆነ ሁኔታ እና ተጋርጦ የሚታየውን የወደፊት አደጋ አስቀድመው ግንዛቤ በመውሰድ ታላላቆቹ ዓለም አቀፋዊ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ማሳወቃቸውን በማስመልከት የነበረኝን ልዩ አድናቆት እና ምስጋና አቅርቤ ነበር፡፡“ በይበልጥም ደግሞ የዓለም አቀፍ ወንዞች/International Rivers፣ የዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ሂዩማን ራይትስ ዎች/Human Rights Watch፣ የኦክላንድ ተቋም/Oakland Institute፣ የዓለም አቀፉ የኑሮ ዋስትና/Survival International፣ እና የአፍሪካ ሀብቶች የስራ ቡድን/the Africa Resources Working Group በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት የአካባቢውን የተፈጥሮ ስነምህዳር ለመጠበቅ እና ለዘመናት ሰፍረው የኖሩትን ህዝቦች ህይወት ለመታደግ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ላይ ለመተግበር የተያዘው መጠነ ሰፊ ዕቅድ ወደ ተግባር እንዳይሸጋገር ባደረጓቸው እና አሁንም በማከናወን ላይ ባሏቸው ጉልህ እና አንጸባራቂ ተግባራት ላይ የተሰማኝን አድናቆት እና ጥልቅ የሆነ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡ እነዚህ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች በግልገል ጊቤ ሦስት የሀይድሮኤሌክትሪክ ግድብ ግንባታ ምክንያት ህይወታቸው ለከፋ አደጋ ተጋልጦ የሚገኙትን ኢትዮጵያውያን/ት ህይወት ለመታደግ በሚደረገው የህይወት ማዳን እርብርብ ለዓመታት በመጀመሪያው ረድፍ ላይ በጽናት ተሰልፈው የሚገኙ ናቸው፡፡

የተለያዩ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች የህዝቡን ግንዛቤ ከፍ በማድረግ እና የቅስቀሳ ዘመቻዎችን በማካሄድ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ላይ ሊከሰት በሚችለው የከፋ የአካባቢ ስነምህዳር አደጋ ላይ የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የጠራ አቋም እንዲይዝ በማድረግ እረገድ በርካታ ተግባራትን አከናውነዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት በጥንቃቄ የተዘጋጁ ዘገባዎችን፣ የጥናት ውጤቶችን እና ዝርዝር የፖሊሲ ትንተናዎችን እንዲሁም ሌሎች ሳይንሳዊ እና አሀዛዊ ዘገባዎችን በማዘጋጀት በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ያለው ገዥው አካል በሚተገብራቸው “የልማት መርሀግብሮች” ሰበብ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ ለዘመናት ሰፍሮ በሚኖረው ህዝብ የዕለት ከዕለት ኑሮ እና አጠቃላይ ህልውና ላይ ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ ውጤት በሰነድ አስደግፈው አቅርበዋል፡፡ እነዚህ ዓለም አቀፍ የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ እና የመብት ተሟጋች ድርጅቶች በጊቤ ሦስት የሀይድሮኤሌክትሪክ ግድብ ግንባታ አማካይነት በወንዙ ሸለቆ የሚገኙትን የተለያዩ ጎሳዎች መሬት በማይመጥን የኪራይ ተመን ሰበብ ገዥው አካል በመንጠቅ ለወጭ ገበያ ምርትነት የሚውሉ የስኳር እና ሩዝ ልማቶች ዘርፍ ተግባራዊ በማድረግ በሸለቆው ግራ እና ቀኝ ሰፍሮ ለዘመናት ሕይወቱን ሲመራ የኖረውን ህዝብ በግዳጅ “የመንደር ሰፈራ” (“villagization”) በሚል ከቀየው ለማፈናቀል እያደረገ ባለው ጭካኔ የተሞላበት አካሄድ ላይ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የጋራ ግንዛቤ እንዲጨብጥ እና የኗሪውን ህዝብ ተጠቃሚነት አሽቀንጥሮ የጣለው የስመ ልማት ከንቱ ሙከራ ተግባራዊ እንዳይሆን ለማስቆም እና ተጽዕኖ መፍጠር እንዲችል በመፈጋቻቸው ነው፡፡

እ.ኤ.አ በ2012 ባቀረብኩት ትችቴ የዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እና የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ድርጅቶች እንዲሁም ቡድኖች በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የልማት መርሁግብር ሰበብ ህልውናቸው ለከፍተኛ አደጋ ተጋልጦ የሚገኙትን ኢትዮጵያውያን/ት ህይወት ለመታደግ ከልማት ሰለባው ህዝቦች ጎን በመሰለፍ ድርጊቱን በማውገዝ እና ለመቀልበስ እንዲቻል የሞት ሽረት ትግል እያደረጉ ባሉበት ወቅት እኛ ኢትዮጵያውያን/ት በተለይም ደግሞ የዲያስፖራው ማህበረሰብ አባላት እጃችንን አጣጥፈን ከዳር የመቆማችን እውነታ ለምን እንደሆነ በመጠየቅ ለዚህ አንገብጋቢ አደጋ ልዩ ትኩረት ባለመሰጠቱ ጉዳይ ላይ በማብሰልሰል የተሰማኝን ቅሬታ ለወገኖች በይፋ ገልጨ ነበር፡፡ እነዚህ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ ተቋማት እና ቡድኖች ለእኛ ብለው እንደዚህ ያለ ከባድ እና ቀጣይነት ያለው ስራ እያከናወኑ እያሉ እኛ ግን በጸጥታ እየተመለከትን ነው፡፡ በዚያን ጊዜ “ከዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት እና ከአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ድርጅቶች ጋር በመቀላቀል ለአካባቢያችን ለመሟገት እራሳችን ንቁ ተሳታፊ በመሆን እገዛ እናድርግ በማለት ለኢትዮጵያውያን/ት ወገኖቸ ሁሉ የተማጽዕኖ ጥያቄ አቅርቤ ነበር፡፡” እንዲሁም “በተፈጥሮ ሀብት የበለጸገው እና የተለያዩ ብዝሀ ህይወት ዝርያዎችን አካትቶ የያዘው የኢትዮጵያ ሀብት አሁን ላለው እና ለወደፊቱ ትውልድ ጠቀሜታ እንዲውል ክብካቤ እና ጥበቃ እንዲደረግለት የእራሳችንን የአካባቢ ጥበቃ ሲቪል ድርጅት እኛው ኢትዮጵያውያን/ት በተለይም የዲያስፖራው ማህበረሰብ እናቋቁም” የሚል የተማጽዕኖ ጥሪ አቅርቤ ነበር፡፡ የሁኔታውን አሳሳቢነት በመገመትም እንዲህ የሚል ማስጠንቀቂያ ሰጥቸ ነበር፣ “ይህንን ማድረግ ካልቻልን በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ ቀኝ በሚኖሩ ወገኖቻችን ላይ ግድቡ እያደረሰ ያለው አደጋ ዓይነት እጣ ፈንታ ውስጥ እራሳችንን ማግኘት እንደምንገደድ መገንዘብ ይኖርብናል፡፡“

 ያንን ትችት ጽፌ ካቀረብኩ ከሁለት ዓመታት በኋላም ቢሆን እስከ አሁን ድረስ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መበቶች እና የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ድርጅቶች ለእኛ ብለው ያንን ሁሉ እልህ አስጨራሽ ትግል እና ጥረት እንዲሁም የእኛን ወገኖች ህልውና ለመታደግ እርብርብ እያደረጉ ባሉበት ወቅት እኛ ከዳር ቆመን እየተመለከትን የመገኘታችንን ሁኔታ ሳስበው ለመቀበል በጣም ይቆጠቁጠኛል (በግልጽ ለመናገር ሀፍረት ይሰማኛል፡፡) እነዚህ ከዚህ ቀጥሎ የቀረቡት ተመሳሳይ ጥያቄዎች ምንም ምላሽ ባይኖራቸውም ደግሜ ደጋግሜ እንዳነሳቸው እገደዳለሁ፡ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች እና የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ድርጅቶች በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ላይ እየተካሄደ ላለው የከፋ አደጋ የሚያመጣ መርሀግበር መቀልበስ ለእኛ ሲሉ ሁሉንም እልህ አስጨራሽ ስራዎች እንዲሰሩ መጠበቅ በእውነቱ ፍትሀዊ ነውን? እነዚህ ዓለም አቀፋዊ ድርጅቶች ለወጎኖቻችን እና ለሀገራችን ሲሉ ይህንን የመሰለ ጥንቃቄ እና ክብካቤ ሲያሳዩ እኛ የጉዳዩ ባለቤቶች ምንም ዓይነት ትኩረት ያልሰጠነው ለምን ይሆን? ለወገኖቻችን ህልውና ሲሉ ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ከሚያሰሙት ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር የማንቀላቀል እና ድጋፍ የማናደርግላቸውስ ለምን ይሆን? ጨቋኙ ገዥ አካል የጭቃ ጅራፉን እያጮኸ በእነዚህ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ላይ ቅጥፈት የተሞላበት እና አሳፋሪ መግለጫ እየሰጠ መልካም ስራቸውን እና ስማቸውን ሲያጠለሽ ለምንድን ነው ወደ እነዚህ ድርጅቶች በመጠጋት የማናግዛቸው እና የማንከላከልላቸው? ተመሳሳይ የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ወንጀሎች እና የሰዎችን ሰብአዊ መብቶች የመደፍጠጥ ወንጀሎች በስመ “ልማት” ሰበብ በሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች ቢፈጸሙ ኖሮ በእውነት ግድየለሾች እና በዝምታ የምንመለከተው ይሆን ነበርን? በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ የሚኖሩ ወገኖቻችን የተገለሉ አናሳ ጎሳዎች በመሆናቸው ብቻ ለእነርሱ መብቶች መደፍጠጥ  ግድየለሾች መሆን ይኖርብናልን? በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ የሚኖሩ ወገኖቻችን እንደሌሎቻችን ሁሉ “ዘመናዊነትን” የተላበሱ ባለመምሰላቸው በእነርሱ አፍረንባቸው ወይም ደግሞ በቅርቡ ያረፉት አቶ መለስ ዜናዊ በአንድ ወቅት የእነዚህ ህዝቦች አኗኗር “ኋላቀር ስልጣኔ“ ነው በማለት በግልጽ እንደፈረጇቸው ቆጥረነው ሊሆን ይችል ይሆን? በምን ዓይነት ሁኔታ ነው እረፍት በሌላቸው ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ከፍተኛ ተጋድሎ አማካይነት በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ ለሚኖረው ህዝብ የተገኘ የአካባቢ ክብካቤ እና ጥበቃ ቅርስ ነው እናም ኑ ተረከቡን ብለን የወደፊቱን ትውልዶች ለማሳምን የምንሞክረው? ውድ አንባቢዎች በእነዚህ ጥያቄዎች ላይ በአንክሮ እንድታስቡ እጠይቃለሁ፡፡

እኛን እየረዱን ያሉትን ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ቢያንስ በገንዘብ ልናግዛቸው የሚገባ መሆኑ ፍትሀዊ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ ለሚኖሩት ወገኖቻችን ሰብአዊ መብት ጥበቃ ይህን ያህል ተጋድሎ እያደረጉ ባለበት ሁኔታ እኛ ድጋፋችንን በተጨባጭ ሁኔታ ለወገኖቻችን የማናሳይበት ምክንያት ሊኖር አይችልም፡፡ ከእነርሱ ጋር በጋራ መቆም ይገባናል እናም ከዳር ቆመን የእነርሱ ተመልካች መሆን አይኖርብንም፡፡

የግልገል ጊቤ ሦስት ግድብ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ በሚኖሩ ህዝቦች ላይ የሚያስከትለው ግልጽ እና ወቅታዊ አደጋ፣

የጊቤ ሦስት ግድብ ግንባታ በአሁኑ ወቅት በመቶ ሺዎች ለሚቆጠሩ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን/ት ወገኖቻችን ማለትም በቦዲ፣ ካሮ፣ ሙጉጂ፣ ሙርሲ፣ ኒያንጋቶም እና ዳሰነች ከብዙዎች ጥቂቶቹ ሲሆኑ ለሺህ ዓመታት “ባህረ ሸሽ ግብርና” እየተባለ የሚጠራውን የግብርና ስራ በመስራት ህይወታቸውን ሲመሩ በኖሩት ላይ ግልጽ ወቅታዊ አደጋ አንዣቦ ይገኛል፡፡ የዝናብ ወራት ከተጠናቀቁ በኋላ ውኃው ሲሸሽ በወንዙ ዳርቻዎች አካባቢ ተሸፍኖ የነበረው መሬት ለም የሆነ ደለል በርካታ የአዝዕርት ዓይነቶችን ማለትም ማሽላ፣ በቆሎ እና ባቄላ ለማምረት ያስችላል፡፡ የእነዚህ ኢትዮጵያውያን ህልውና የተመሰረተው በየጊዜው በሚለዋወጡት የጎርፍ ወቅቶች አማካይነት ነው፡፡ የጊቤ ሦስት ግድብ የወንዙ የላይኛው ክፍል ወደ ውጭ አገር ለሚላክ የኤሌክትሪክ ምርት ማመንጫነት ሲባል በሚገደብበት ጊዜ ወንዙ በሸለቆው ውስጥ የሚያደርገውን የተፈጥሮ የውኃ ፍሰት መጠን በመሰረታዊ መልኩ ያናጋዋል፡፡ ወደግድቡ ማጠራቀሚያ እና ለስኳር ልማት የመስኖ ስራ ለሚውለው ውኃ ፍጆታ ሲባል የውኃው የፍሰት አቅጣጫ ሲቀየር አጠቃላይ የኦሞ ወንዝ የውኃ መጠን ዘለቄታዊ ባለው ሁኔታ በእጅጉ እንደሚቀንስ በመስኩ የተሰማሩ ባለሙያዎች አሳማኝ በሆነ መልኩ ሞግተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት በሸለቆው ውስጥ የሚኖሩ ህዝቦች በእርግጠኝነት ባህረ ሸሽ እየተባለ የሚጠራውን የግብርና ዘይቤ ለማካሄድ አይችሉም፡፡ እ.ኤ.አ በ2012 በዓለም ዕውቅናን ያተረፉት የተፈጥሮ ሀብት ክብካቤ እና ጥንታዊ የሰው ዘር ተመራማሪ የሆኑት ባለሙያ ዶ/ር ሪቻርድ ሊኬይ የጊቤ ሦስት ግድብ ግንባታ የግል ጥቅም ማሳደጃ “ሳይንሳዊ” ጥናት በስነምህዳሩ ላይ ሊከሰቱ የሚችሉትን ውጤቶች አሳንሶ የሚያይ መሆኑን የምር በመሞገት “ግድቡ በርካታ የሆኑ አሉታዊ ውጤቶችን እንደሚያስከትል እንዲያውም አንዳንዶቹ በሁለቱም በኩል ማለትም በአካባቢው ስነምህዳር እና ለዘመናት ህይወቱን በዚህ ወንዝ የታችኛው ክፍል ላይ መስርቶ ለሚኖረው ማህበረሰብ ህይወት ውድመት እና ዕልቂት“ ሊሆን እንደሚችል አስረግጠው ተንብየዋል፡፡ 

የኦሞን  ወንዝ  “ማልማት

እ.ኤ.አ በ2011 መጨረሻ አካባቢ አቶ መለስ ዜናዊ በደቡብ ኦሞ ዞን በጅንካ ከተማ በመገኘት ንግግር አድርገው ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ አቶ መለስ ረዥም እና የማስመሰያ፣ እንዲሁም ጠንከር ያለ እና እብሪት የተሞላበት ንግግር ነበር ያደረጉት፡፡ “በኋላ ቀር ስልጣኔ” ተተብትበው የሚገኙት ላሏቸው በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ ለሚኖሩ ህዝቦች ከሰማይ መና እንደሚያወርዱላቸው ነበር ቃል የገቡት፡፡ እነዚህን ህዝቦች ከድንጋይ ዘመን መንጥቀው በማውጣት ወደ ስልጣኔው ዘመን በእልልታ በማምጣት “የፈጣን ልማት ምሳሌ” እንደሚያደርጓቸው ምለው ተገዝተው ነበር፡፡ እንዲህ በማለት ነበር ለማህበረሰቡ የመተማመኛ ንግግር ያደረጉት፣ “በኦሞ ወንዝ የሚገነባው ግድብ የጎርፍ አደጋውን ያስወግድላችኋል፣ ግዙፍ የሆነ የመስኖ ልማት ስርዓት ይዘረጋል፣ እናም ከቦታ ቦታ የምትዘዋወሩት የማህበረሰብ አባላት (pastoralists) ዘለቄታዊ የሆነ ገቢ ያስገኝላችኋል፣ እንዲሁም ደግሞ ዘመናዊ ህይወት ትኖራላችሁ”::

ለጊቤ ሦስት ግድብ ግንባታ ሂደት ጥንቃቄ እና ትኩረት በመስጠት እንዲከናወን እና ለዘመናት በኦሞ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ ኑሮውን በመግፋት ላይ የሚገኘውን ህዝብ የህይወት ዘይቤ እና ባህል በጠበቀ መልኩ የልማት ስራው እንዲከናወን ተማዕጽኗቸውን ላቀረቡ ዓለም አቀፍ የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ እና የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች አቶ መለስ በአጻፋው ጥላቻ በተሞላበት መልኩ ስራቸውን ስማቸውን በማጠልሸት እና በነገር በመሸንቆጥ የአቅማቸውን ያህል ተግትገዋቸዋል፡፡ እነዚህን ዓለም አቀፍ ድርጅቶች “ወንዞቻችንን የመጠቀም ነጻነታችንን ለመገደብ እና ህዝቦቻችንን ከድህነት እንዳናወጣ“ ሁልጊዜ ለተቃውሞ የተዘጋጁ እና እልቂት ናፋቂ ሟርተኞች ናቸው በማለት ፈርጀዋቸዋል፡፡ እንዲሁም አደገኛ የልማት አደናቃፊዎች የሚል ታርጋ ለጥፈውላቸዋል፡፡ እንዲህ በማለትም አክለውላቸዋል፣ “ግዙፍ የሆነ ፕሮፓጋንዳ በመፍጠር ላይ ናቸው… የልማት ፕሮጀክቶቻችንን እንዳናጠናቅቅ ከውጭ የገንዘብ ብድሮችን እንዳናገኝ መሰናክል በመፍጠር ላይ ናቸው፡፡“ እንዲህ ሲሉም ተሳልቀውባቸዋል፣ “የኋላቀርነት እና የድህነት ሁነኛ ጓደኞች…በእርግጥ ምንም ዓይነት ተጨባጭነት ያለው ነገር የማይሰሩ” ብለዋቸዋል፡፡  ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ ለእራሳቸው ጥቅም ብቻ የቆሙ ዘረኞች ብለዋቸዋል፣ ምክንያቱም ይላሉ፣ “ሁሉም እንዲሆን የሚፈልጉት ነገር እነዚህ ዘላኖች የቱሪስት መስህብ ሆነው እንዲቀሩ ነው፡፡“ እናም የኦሞ ወንዝ ሸለቆ ህዝቦች፣ “ለሳይንቲስቶች እና ለተመራማሪዎች ለጥንታዊ የሰዎች የአኗኗር ዘይቤ የተናጠል ጥናት“ ማድረጊያ ማዕከል ሆነው እንዲቀሩ ለማድረግ አስበው ነው ብለዋል፡፡

አቶ መለስ እና ሎሌዎቻቸው ከዚህ ቀደም የተደረገውን እና በአሁኑ ጊዜም በጊቤ ሦስት ግድብ እና ሸለቆውን “ለማልማት” በሚል ሰበብ እየተደረገ ያለውን የአካባቢ ውድመት ለመደበቅ ብዙ ርቀቶችን ተጉዘዋል፡፡ እ.ኤ.አ በጁላይ 2008 በግድቡ ላይ የግንባታ ስራ ከተጀመረ ከሁለት ዓመታት በኋላ እና ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እና የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ድርጅቶች ዓለም እንዲገነዘብ ደወሉን ማሰማት ከጀመሩ በኋላ አቶ መለስ “የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን መስሪያ ቤታቸው” የጊቤ ሦስትን ፕሮጀክት የአካባቢ ስነምህዳር እና ማህበራዊ እንደምታ ጥናት አሳትመው እንዲያቀርቡ ትዕዛዝ ሰጡ፡፡ ያ የጥናት ዘገባ ለማስመሰያነት የአቶ መለስን የማይቀየር ጽኑ ውሳኔ ህጋዊ በማስመሰል ወዲያውኑ በህገወጥ መልክ የፕሮጀክቱን የወደፊት ስራ ለማስቀጠል የተደረገ አሳፋሪ ክንውን ነበር፡፡ ያ ዘገባ ዓይን ያወጡ ቅጥፈቶች የታጨቁበት ነበር፡፡ የጊቤ ሦስት ግድብ የውኃ ማጠራቀሚያ አካባቢ ለሰው ልጅ መኖሪያነት ምቹ አይደለም፣ ምክንያቱም ገዳይ በሆኑት የወባ ትንኝ እና የቆላ ዝንቦች/tsetse flies (“ለእንቅልፍ በሽታ” የሚዳርጉ) ተህዋስያን የተወረረ አካባቢ መሆኑን ሀፍረተቢስ በሆነ መልኩ ያቀረበ ዘገባ ነበር፡፡

ዘገባው እንዲህ ይላል፣  “ወደፊት በግድቡ የውኃ ማጠራቀሚያ አካባቢ ምንም ዓይነት ሰፈራ አይኖርም፣ እናም ሰፈራዎች የሚኖሩት በላይኛው ከፍታ ቦታዎች ከሸለቆው ውጭ በሆኑ አካባቢዎች ብቻ ነው… በታችኛው የኦሞ ወንዝ ሸለቆ የመጨረሻ ጠርዝ አካባቢ መሬቶች ላይ በጣም ውስን የሆነ የእርሻ ስራ አለ… በመርሀግበሩ በተያዘው ግድብ ዙሪያ የሚኖረው ህዝብ እና በውኃ ማጠራቀሚያው መካከል ያለው የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት/UNESCO ከያዘው የባህል ቅርስ ቦታ በቅርብ ርቀት የሚገኙ አይደሉም፡፡ በግድቡ እና በዙሪያው ባሉ አካባቢዎች ሳይንሳዊ፣ ባህላዊ፣ የዘር እና የታሪክ ጠቀሜታ ያላቸው በግልጽ የሚታዩ ቅሬተ አካሎች የሉም፡፡“

የአቶ መለስ የኦሞ ወንዝ ሸለቆን “ኋላቀርነት” ወደ “ዘመናዊነት” ኑሮ የመቀየር ዘይቤ ሸለቆውን ለሳውዲ አረቢያ እና ለሌሎች የውጭ መዋዕለ ንዋይ አፍሳሾች እና ለጓደኞቻቸው ለማዛወር የታቀደ ነበር፡፡ አቶ መለስ በንግግራቸው በመቀጠል “መንግስት ዕቅድ ያወጣል፣ እናም 150,000 ሄክታር የስኳር አገዳ ልማት ከዚህ ዓመት ጀምሮ ተግባራዊ ያደርጋል“ በማለት መንግስታቸው ጠንክሮ እንደሚሰራ ገልጸው ነበር፡፡ በእርግጠኝነት እንደ አይሲ/IC የተባለው መጽሔት ከሆነ “የሳውዲ አረቢያው ባለሀብት አልሙዲ በከፍተኛ ደረጃ ካሉት የመንግስት አመራሮች ጋር ጥብቅ የግንኙነት ትስስር ስላለው ለሩዝ ምርት የሚሆን 10,000 ሄክታር መሬት ተሸንሽኖ ተሰጥቶታል፡፡“ የእርሱ ግዙፍ ፕሮጀክት በአካባቢው ስነምህዳር ማለትም በብሄራዊ ፓርኩ እና በዱር እንስሳት መጠለያ ላይ እንዲሁም ለዘመናት በአካባቢው ሲኖሩ በነበሩ ትውልዶች ማህበረሰብ አባላት ላይ ታላቅ ጉዳትን አስከትሏል፡፡”

አቶ መለስ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ በኦሞ ኩራዝ የስኳር ልማት ፕሮጀክት ስር አምስት የስኳር ፋብሪካዎች ይቋቋማሉ በማለት ተናግረው ነበር፡፡ እንደ “ኢትዮጵያ ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ድርጅት” ከሆነ “መስፍን ኢንዱስትሪያል ኢንጅነሪንግ/Mesfin Industrial Industry (MIE) የተባለው ድርጅት በአማራ ክልል ከሚገኘው ጣና በለስ የተቀናጀ የስኳር ልማት ፕሮጀክት እና በኦሞ ሸለቆ ከሚገኘው ኩራዝ ስኳር ልማት ፕሮጀክት ከሚባሉ መንግስታዊ ድርጅቶች ጋር የብር 3 ቢሊዮን (162.2 ሚሊዮን ዶላር) የሚያወጣ ዋጋ ያላቸው ማሽነሪዎችን ለማቅረብ የስምምነት ውል ተፈራርሟል…“ መስፍን ኢንዱስተሪያል ኢንጅነሪንግ “ከድሬዳዋ እስከ አዲስ አበባ ለሚዘረጋው የባቡር መስመር ግንባታ ፕሮጀክት እና በተመሳሳይ መልኩ ከጅቡቲ በአፋር በኩል አድርጎ ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ ለሚዘረጋው የባቡር መስመር አገልግሎት የሚውሉ የባቡር ሃዲዶችን የመዘርጋት የማጠናቀቅ ስራ ያከናውናል፡፡“

እ.ኤ.አ በጁን 2011 “የጊቤ ሦስት ግድብ በቱርካና ሐይቅ ላይ ጉልህ የሆነ ለውጥ ሊያመጣ የሚችል አስተማማኝ ያልሆነ የውኃ መጠን በመልቀቅ በውኃ ውስጥ ያሉ ህይወት ያላቸው ዝርያዎችን እና ከእርሱ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን የስነሕይወት ስርዓቶች ለአደጋ እንደሚጥል“ እናም “በኢትዮጵያ ያለው መንግስት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ በሌላ መንግስት ግዛት ውስጥ የተመለከተን ባህላዊ ቅርስ ከጉዳት ላይ ላለመጣል በጊቤ ሦስት ላይ የጀመረውን የግንባታ ስራ በአስቸኳይ እንዲያቆም“ በማለት የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት/UNESCO ከድምዳሜ ላይ ደርሷል፡፡

በአቶ መለስ “የልማት” ዕቅዶች በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ግራ እና ቀኝ የሚኖረው በድህነት የሚማቅቀው እና ተከላካይ የሌለው ህዝብ ፍትሐዊነት በጎደለው መልኩ ግፍ የተፈጸመበት ሲሆን የእርሳቸው ሞራለቢስ ጓደኞች ግን የናጠጡ ሞራለቢስ ሀብታሞች ሆነዋል፡፡ እ.ኤ.አ በጃንዋሪ 2014 የታተመ አንድ የአካባቢ ምህዳር ጥናት ከሆነ “የኩራዝ ስኳር ልማት (161,285 ሄክታር መሬት ይሸፍናል ተብሎ ይገመታል) ግንባታ እና ከዚህ ጋር የተያያዙ የመሰረተ ልማት ስራዎች የስኳር ማምረቻ መሳሪያዎችን ጨምሮ እና በመንደር የማሰባሰብ ስራዎች የጊቤ ሦስት ግድብ ከመጠናቀቁ በፊት ቀደም ሲል የተጀመሩ ስራዎች ናቸው፡፡ የኩራዝ ስኳር ልማት እና ሌላ ተጨማሪ ለሸንኮራ አገዳው ልማት እርሻ አገልግሎት ምቹ የሆነ የተጠና መሬት (47,370 ሄክታር) እንደ መስኖው ሀብትን በአግባቡ የመጠቀም ባህሪ በእርግጠኝነት የኦሞ ወንዝን 50 በመቶ የውኃ ፍሰት ይፈልጋል፡፡“

የአቶ መለስ የኦሞ ወንዝ ሸለቆ “ስልጣኔ” መርሀግብር ለጓደኞቻቸው ነፋስ አመጣሽ ዘረፋ ነው፣ ሆኖም ግን የኦሞ ወንዝ ሸለቆን ኗሪ ህዝቦች ያነጠፈ እና ያደረቀ ዕቅድ ነው፡፡ የአቶ መለስ ስለኦሞ ወንዝ ሸለቆ እና ህዝብ ራዕይ ለሳውዲ አረቢያው ባለሀብት ለአላሙዲ እና ለመስፍን ኢንዱስትሪያል ኢንጅነሪንግ ጥሩ የሆነ ነገር ሁሉ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ህልውናቸውን መስርተው ለሚኖሩ ህዝቦችም ጥሩ ነው“ በሚል ዕይታ ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ ለዚህም ነው በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን/ት ለስግብግብነት እና ከሀዲነት ዓላማ መጠቀሚያ እየሆኑ ያሉት!

የኦሞን ወንዝ እና የኗሪውን ህዝብ ህልውና ለመታደግ ቀጣይ እርብርብ፣

ባለፈው ሳምንት ዓለም አቀፋዊ ወንዞች/International Rivers የተባለው ድርጅት በለቀቀው የቪዲዮ መልዕክት መሰረት ግድቡ እና የመከነው ያልታሰበበት “የልማት” ፕሮጀክት ተብሎ የቀረበው ዕቅድ በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ያለው ገዥው አካል እንደገና ካላሰበበት እና ካልተቋረጠ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የሚያስከትለው ከፍተኛ ስጋት እና በሸለቆው ግራ እና ቀኝ በሚኖረው ህዝብ እና ስነምህዳር ላይ ሊቀለበስ የማይችል አደጋ እንደሚያስከትል አስጠንቅቋል፡፡ ቪዲዮው በአሁኑ ጊዜ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ላይ የተጋረጠውን አደጋ በግልጽ የሚያሳይ ስለሆነ መመልከቱ ጠቃሚነት አለው፡፡

የጊቤ ሦስት ግድብ ግንባታ እና ለመስኖ ስራ ተብሎ የኦሞን ወንዝ ውኃ አቅጣጫ ማስቀየስ በደቡብ ኢትዮጵያ እና በሰሜን ኬንያ በሚኖሩ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ህዝቦች ህልውና ላይ ግልጽ እና ከፍተኛ የሆነ አደጋን ሊያስከትል እንደሚችል ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት የወንዙን የተፈጥሮ የውኃ ፍሰት ኡደት ማቋረጥ ማለት ከዓለም በትልቅነቱ ከፍተኛ የሆነው የቱርካና የበረሀ ሐይቅን ህልውናው አድርጎ የተመሰረተው የእርሻ፣ የግጦሽ መሬት፣ እስከ ቱርካና ሐይቅ ድረስ በወንዙ ዳርቻ የሚገኘው የዓሳ ሀብት ሁሉ እንዳለ ይወድማል፡፡ ግድቡ በታችኛው የኦሞ ሸለቆ እና በቱርካና ሐይቅ ሁለቱም በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት/UNESCO የዓለም የልዩ የባህል እና ስነምድር ቅርስነት የተመዘገቡትን ሀብቶች ሙሉ በሙሉ ያጠፋል፡፡

“የጊቤ ሦስት ግድብ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት/UNESCO በዓለም የቅርስነት መዘገብ የሰፈረውን ቦታ፣ ለ300,000 ተጨማሪ ህዝብ ህልውና መሰረት የሆነውን እና እስከ ቱርካና ሐይቅ ድረስ የተዘረጋውን እንዲሁም፣ 90 በመቶ የሚሆነውን የውኃ ፍላጎቱን የሚያገኘው ከኦሞ ወንዝ የሆነውን” የተፈጥሮ ስነምህዳ በቋፍ ላይ ሊጥለው እንደሚችል የመስኩ ባለሙያዎች ያላቸውን ስጋት ይገልጻሉ፡፡

በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ሊደርስ የሚችለውን የአካባቢያዊ ስነምህዳር አደጋ መጠን እና በግድቡ መሰራት ምክንያት በሰው ላይ የሚደርሰውን ኪሳራ ኢትዮጵያውያን/ት ሁሉ እንዲገነዘቡት ማድረግ ከፍተኛ የሆነ ጠቀሜታ አለው፡፡ በተለይም ኢትዮጵያውያን አንባቢዎቸ የዓለም አቀፍ ወንዞች ቪዲዮንን ( የአማርኛውን ትርጉም አዚህ ይጫኑ ወይም  http://www.internationalrivers.org/amharic-video-translation-omo-cascade  )  አንድትመለከቱት እጠይቃለሁ፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ/USAID እና በኢትዮጵያ የለጋሽ ድርጅቶች እገዛ ቡድን/Donors Assistance Group (በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የሚኖረውን ህዝብ ህልውና ከአደጋ ለመታደግ ከሚደረገው እርብርብ ጋር በተያያዘ መልኩ “ምንም ዓይነት መከራ የማይታያቸው፣ ምንም ዓይነት ስቃይ የማይሰማቸው፣ ስለምንም ዓይነት መከራ የማይናገሩ” ሆኖም ግን ለህዝብ መብት እና እድገት የቆሙ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ናቸው፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) እና የ26 አገሮች ስብስብ የሆነው በኢትዮጵያ የለጋሽ ድርጅቶች እገዛ ቡድን (DAG) ከኦሞ ወንዝ ሸለቆ ጋር በተያያዘ መልኩ በኗሪው ህዝብ ላይ በሚፈጸሙት የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎች ከሚነሱ ጥያቄዎች ጋር ላለመተባበር ጆሮ ዳባ ብለው ተቀምጠዋል፡፡ በጨዋ አነጋገር እነዚህ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች የሚያራምዷቸው አቋሞች በሚከተለው መልክ ሊመሰሉ ይችላሉ፣ “ምንም ዓይነት መከራ አላየንም፣ ምንም ዓይነት ስቃይ አልሰማንም፣ እናም በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ምንም ዓይነት የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ የለም፡፡“

እ.ኤ.አ ኦክቶበር 2010 በዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት በሂዩማን ራይትስ ዎች/HRW በኢትዮጵያ እርዳታ ለሰብአዊ መብት ድፍጠጣ መዋል የሚለው ዘገባ ከመውጣቱ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) እና በኢትዮጵያ የለጋሽ ድርጅቶች እገዛ ቡድን (DAG) በሰብአዊ መብት ድርጅቱ “በኢትዮጵያ የተስፋፋው ስልታዊ ሙስና በልማት እርዳታ“ በሚል የወጣውን ዘገባ በመካድ እንዲህ የሚል መግለጫ አውጥተው ነበር፣ “የእኛ ጥናት ምንም ዓይነት ሙስናን የሚያመላክት ስልታዊ ወይም የተስፋፋ ሙስና መረጃ አላገኘንም፡፡“ እ.ኤ.አ በ2012 የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) የሚከተለውን ዘገባ አቅርቦ ነበር፣ “ደቡብ ኦሞን በጎበኘሁበት ወቅት [የሰብአዊ መብት ረገጣን] የሚያጠናክር ምንም ዓይነት መረጃ አላገኘሁም፡፡“ እ.ኤ.አ ጃኗሪ 17፣ 2014 በተጻፈ ደብዳቤ የዩኤስኤአይዲ/USAID በኢትዮጵያ የአሁኑ ተልዕኮ ዳይሬክተር ዴኒስ ዌለር ድርጅታቸው እና ሌሎችን በሚመለከት እንዲህ ብለው ነበር፣ “ድርጅቴ እና ሌሎች ለጋሽ ድርጅቶች በጋራ ሆነን በደቡብ ኦሞ ያለውን ሁኔታ ስንከታተል ነበር“ እናም “ከእነዚህ ጉዞዎች የተገኘው ዋና ግኝት የሚያመለክተው ምንም ዓይነት የተስፋፋ ወይም ስልታዊ የሆነ የሰብአዊ መብት ጥሰት ዘገባ አልተገኘም፡፡ የእኛ ምልከታዎች ቀደም ሲል በአጽንኦ ሲባሉ እና ሲነገሩ የነበሩትን…ማለትም በሰፈራ የማሰባሰብ ሂደቶች በስልታዊ እና በተስፋፋ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች የታጀቡ ናቸው የሚባለውን ነገር የሚደግፉ ሆነው አልተገኙም፡፡“

የሚገርመው ነገር ግን በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ኗሪ ህዝቦች ላይ የተፈጸሙት የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እንደሌሉ የዌለር ትችቶች ያጣጣሉትን ከእርሳቸው ቀደም ብለው በእርሳቸው ቦታ ከነበሩት ከቶማስ ስታል አስተያየቶች ጋር ፍጹም በተቃራኒው መሆናቸው ነው፡፡ ከኢትዮጵያ በእራሳቸው ፈቃድ ወደ ባግዳዳድ ለመሄድ ከመነሳታቸው በፊት እ.ኤ.አ በኦክቶበር 2010 ቃለመጠይቅ የተደረገላቸው ስታል እንዲህ የሚል ትኩረትን የሚስብ የእምነት ቃል ሰጥተው ነበር፣ “የፖለቲካ ተሳትፎን በሚመለከት ጥሩ ስራ አልሰራንም፡፡ በተለይም ከሁለት ዓመታት በፊት የተካሄደውን ምርጫ በሚመለከት ዴሞክራሲን ለማስፋፋት ምንም ብዙ የሰራነው ነገር የለም…ይህ ደረቅ እውነታ ተስፋ እንድንቆርጥ አድርጎናል፡፡“ ለዌለር ግን በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ኗሪዎች ላይ የሚካሄደው የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ “ተስፋ የሚያስቆርጥበት” ምንም ዓይነት ምክንያት አይኖርም!

በኦሞ ወንዝ ሸለቆ በሚኖረው ህዝብ የሚካሄደውን የሰብአዊ መብት ጥሰት አስመልክቶ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) እና በኢትዮጵያ የለጋሽ ድርጅቶች እገዛ ቡድን (DAG) ይፋ አቋም በሁለት ሀሳቦች ሊጠቃለል ይችላል፣ 1ኛ) በዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት እና የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ተሟጋች ድርጅቶች በግድ ስለማፈናቀል፣ ስለመንደር ምስረታ፣ ስለሰፈራ ፕሮግራም፣ ለህልውና የሚሆንን መሬት ስለመነጠቅ፣ ድብደባዎች፣ ግድያዎች፣ አስገድዶ መድፈር፣ እስራት፣ ማስፈራራት፣ የፖለቲካ ጭቆና እና የመንግስት እገዛ ያለማድረግ የሚወጡ ዘገባዎች ሁሉም አስመሳይ ፍብረካዎች እና ተራ ቅጥፈቶች ናቸው፡፡ 2ኛ) ዘገባዎቹ ትክክለኛ ቢሆኑም እንኳ የተዘጋጁት በተበጣጠሱ እና የሁለተኛ የመረጃ ምንጭን መሰረት አድርገው ስለሆነ “ለስልታዊ እና የተስፋፉ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎች“ ተጨማሪ ግብዓት ሆነዋል፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) በኢትዮጵያ “ስልታዊ እና የተስፋፉ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎች“ እንደሌሉ መካዱ ማንንም ሊያስደንቅ አይችልም፡፡ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) ለዓመታት “ለስልታዊ እና የተስፋፉ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎች“ የሚለውን እውነታ እንደ ባዶ ሀረግ በመቁጠር ሀቅን በመሸፋፈን ከለላ ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ እ.ኤ.አ በ2010 አቶ መለስ ፓርቲያቸው በ99.6 በመቶ  በፓርላሜንታዊ ምርጫ ድል ተጎናጸፍኩ ብለው ሲያውጁ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) ምንም ዓይነት “ለስልታዊ እና የተስፋፉ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎች“ የመብት ጥሰቶች አላገኘም፣ አላየም፣ አልሰማምም፡፡ አቶ መለስ ዜናዊ በጋምቤላ እና በኦጋዴን አካባቢዎች በሰው ልጅ ዕልቂት ወንጀል በፈጸሙበት ጊዜ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) የሚለውን የተከበረ መጠሪያ ስሙን እራሱ ወደ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ ክህደት (USA In Denial) በሚል ስያሜ ቀይሮታል፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ተሟጋቾች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች መሪዎች፣ ጋዜጠኞች፣ የፍትሀዊነት አመጸኞች፣ የድረገጽ አዘጋጆች እና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች በጅምላ ለእስር ወደ ዘብጥያ ሲጣሉ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) ምላሽ “ስልታዊ እና የተስፋፉ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎች“ የሉም የሚል ነበር፡፡ ምንም! ጭራሽ! በፍጹም! “የተስፋፉ እና ስልታዊ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎች“ ማለት በእርግጠኝነት ምን ማለት ነው? የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) “ነጠላ ሞት አሰቃቂ ነው፣ የሚሊዮኖች ሞት ግን ለቁጥር ያህል ነው“ ለማለት ፍልጎ ነውን? ምናልባትም ለዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የአንድ ሰው ሰብአዊ መብት መደፍጠጥ አሰቃቂ ነው፣ ነገር ግን በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የሚኖረው የጠቅላላው ህዝብ ሰብአዊ መብት መደፍጠጥ ለቁጥር ነውን?!

እውነታው ግን የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) እና ሌሎች እ.ኤ.አ በጃንዋሪ 2012 የኦሞን አካባቢ የጎበኙት ሰዎች በግዳጅ “በተለያዩ የታችኛው ኦሞ ማህበረሰብ የተደረጉትን የቪዲዮ ቃለመጠይቅ ቅጂዎች“ እንዲሰጣቸው ተደርጓል፡፡ እነዚህ ቅጅዎች “ለጥርጣሬ ቦታ አይሰጡም፣ ለጋሽ ድርጅቶች ለሰብአዊ መብት ጥሰት በጣም አስተማማኝ የሆነ የመጀመሪያ የመረጃ ምንጭ አድርገው ስለወሰዱት በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት መምሪያ (USAID) እና በኢትዮጵያ የለጋሽ ድርጅቶች እገዛ ቡድን (DAG) የመስክ ጉብኝ አድርገው“ ካጠናቀቁ በኋላ ጉዳዩን ችላ እንዲሉት አስችሏል፡፡

የዩናይትድ ስቴትስ ኮንግረስ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የሚኖሩ ህዝቦችን ህልውና ለመታደግ ከሚደረገው እርብርብ ጋር ተቀላቅሏል፣

እ.ኤ.አ በጁላይ 2013 ሴናተር ፓትሪክ ሊሂ (ዲ ቬርሞንት) በኢትዮጵያ የዩናይትድ ስቴትስ እርዳታ አስተዳደር ላይ የተወሰኑ ማብራሪያዎች በሴኔት ቢል 1372 ላይ እንዲጨመር አድርገዋል፡፡ የሊሂ ማብራሪያ “በ2014 የተጠናከረው የድርጊት መርሀግብር“ እ.ኤ.አ ጃንዋሪ 3፣ 2014 ሁለቱንም ምክር ቤቶች በመዝለል በሰነድ ላይ እንዲካተት ተደርጓል፡፡ የሰነዱ ክፍል የሆነው  ቁጥር 7042 (d) የድርጊት መርሀግብሩ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ የመንግስት ጽ/ቤት “በድርጊት መርሀግብሩ ኮሚቴ አማካይነት የኢትዮጵያ መንግስት 1ኛ) የፍትህ ነጻነት፣ ሀሳብን በነጻ የመግለጽ፣ በነጻ የመደራጀት መብት፣የመሰብሰብ እና የእምነት ነጻነት፣ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች መብቶች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች እና ጋዜጠኞች ያለምንም መሸማቀቅ ወይም ጣልቃገብነት እና የህግ የበላይነት መንቀሳቀስ የሚችሉ መሆናቸውን፣ 2ኛ) የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እና የሰብአዊ እርዳታ በኢትዮጵያ ወደ ሶማሊ ክልል እየገቡ መጎብኘት እንዲችሉ የመፍቀድ“ የሚሉትን ማረጋገጥ ይጠበቅበታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በኦሞ  ወንዝ የታችኛው ክፍል እና በጋምቤላ አካባቢዎች ላይ የዩናይትድ ስቴትስ “የልማት እርዳታ” እና “የኢኮኖሚ ድጋፍ ገንዘብ” ሀ) በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ አስገድዶ ማስፈርን ለሚተገብሩ እንቅስቃሴዎች ሊውል እንደማይችል፣ ለ) የአካባቢ ማህበረሰቦችን ህይወት ሊለውጡ ለሚችሉ ተነሳሽነቶች ማዋል እንደሚቻል እና ሐ) ጉዳት ከመድረሱ በፊት ከማህበረሰቦች ጋር ለሚደረግ ምክክር በማለት በማያሻማ መልኩ በግልጽ ተቀምጠዋል፡፡ ህጉ የሚጠይቀው “የገንዘብ ግምጃ ቤቱ ዋና ጸሀፊ የዩናይትድ ስቴትስ የእያንዳንዱ የገንዘብ ተቋም ኃላፊ የሆኑት ሁሉ በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ በኢትዮጵያ ዜጎችን ሊያፈናቅሉ ለሚችሉ ተግባራት መዋል እንደሌለበት መቃወም እንዳለበት“ ያመላክታል፡፡ “የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እና የአካባቢ ስነምህዳር ጥበቃ ድርጅቶች በኦሞ ወንዝ ሸለቆ እና በጋምቤላ ተፈጥሯዊ ስነምህዳር እና ለዘመናት የህልውናቸው መሰረት አድርገው በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖሩ ህዝቦች መብቶቻቸው እንዲጠበቁላቸው ሲያደርጉት የቆዩት ጥረት ፍሬ ያፈራ ይመስላል፡፡!!

የኦሞ ወንዝ ሸለቆን እና በዚያ ሰፍሮ የሚኖረውን ህዝብ ህልውና ለመታደግ በሚደረገው እርብርብ ኢትዮጵያውያን/ት የት ላይ እንገኛለን?

የይስሙላው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ስለውኃ ልማት እና ስለአካባቢ ንፅህና እውቀት እንዳላቸው ይነገራል፡፡ እንደሚቀርቡት ዘገባዎች ከሆነ በአርባ ምንጭ የውኃ ቴክኖሎጂ ተቋም “የድህረ ምረቃ የአካዳሚ ቦታ“ ይዘው እንደነበር ይነገራል፡፡ እንደዚሁም ደግሞ የእርሳቸው የዘር ግንድ “ዋናው የህብረተሰብ ምድብ ከሆነው ከደቡብ ብሄሮች ብሄር እና ብሄረሰቦች ክልል  ከኦሞቲክ ማህበረሰብ“ የመጡ እንደሆኑ ይነገራል፡፡

አቶ ኃይለማርያም በኦሞ ወንዝ ሸለቆ እየተከሰተ ስላለው አካባቢያዊ የስነምህዳር ውድመት እና “ከልማት” ጋር በተያያዘ መልኩ እየደረሰ ስላለው የማህበራዊ ኪሳራ የግል እና የሙያ ፍላጎት እንዲኖራቸው ሀሳብ ማቅረብ ምክንያታዊ ነው፡፡ ሆኖም ግን አቶ ኃይለማርያም በተደጋጋሚ “አገሪቱን ወደ እድገት ለማሸጋገር የአቶ መለስን ራዕይ ለማስፈጽም ነው ያለሁት“ በማለት  በተደጋጋሚ ተናግረዋል፡፡ እናም ከዚህ መንደርደሪያ መርሀቸው በመነሳት አቶ ኃይለማርያም የኦሞ ወንዝ ሸለቆ የአካባቢ ስነምህዳር ውድመት እና በሸለቆው ውስጥ የሚኖሩ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ህዝቦች ህልውና አደጋ ላይ መውድቅን ከላይ ከቀረበው አስተሳሰባቸው ጋር አቆራኝቶ ማየት ይቻላል፡፡

እርግጥ ነው በዚህ ጉዳይ ላይ የማደርገው ትግል  ባልጬት ድንጋይ ላይ ውሃ ማፍስስ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ሆኖም ግን አቶ ኃይለማርያም እና ገዥው አካል በኢራን አገር ከሚገኘው ኦሮሚህ/Oroumieh ከሚባለው ሐይቅ አሰቃቂ ተውኔት ትምህርት እንዲቀስሙ አጥብቄ እማጸናለሁ፡፡ ያ ሐይቅ ዕውቀትን ባላካተተ መልኩ በተፈጸመበት የግድብ እና የመስኖ ስራ ፕሮጀክት ምክንያት በ10 ዓመታት ጊዜ ውስጥ የውኃው መጠን በ80 በመቶ በመቀነስ ተኮማትሯል፡፡ የኢራን አዲሱ ፕሬዚዳንት ሃሰን ሮሃኒ በሐይቁ መንጠፍ ስለደረሰው አካባቢያዊ ውድመት የሰጡት ምላሽ “ለችግሩ መፍትሄ ለመፈለግ እንዲቻል በአስቸኳይ ቡድን ማቋቋም እና በዘርፉ ክህሎት ያላቸውን ምሁራን መጋበዝ“ ነበር፡፡

አቶ ኃይለማርያም እና የስራ ጓዶቻቸው የኦሞ ወንዝ እንዲነጥፍ ሲደረግ ስለቱርካና ሐይቅ መድረቅ ወይም ደግሞ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ላይ ስለሚደርሰው አካባቢያዊ እና ስነምድራዊ እንዲሁም ማህበራዊ ውድመት ደንታ የላቸውም፡፡ በእብሪት እና በድንቁርና የታወሩ የገዥ አካል መሪዎች ምሁራንን እና በመስኩ ተፈላጊው ክህሎት ያላቸውን ባለሙያዎች በመጋበዝ ለተደቀነው አደጋ ዘለቄታዊ መፍትሄ ይሰጣሉ የሚል እምነት እንደሌለኝ አውቃለሁ፡፡ የገዥው አካል አመራሮች የወሰን ልክን እንደሰበረ ሁሉ በእራሳቸው የይሆናል ባዶ ተስፋ ከሚቦርቅ፣ ስለኦሞ ወንዝ ሸለቆ ጥንቃቄ እና ክብካቤ እንዲደረግ በተደጋጋሚ የሚማጸኑትን ወገኖች ከማውገዝ የዘለለ እርባና የሌለው ንግግር ከመደጋገም ውጭ የገዥው አካል አመራሮች የሚቀይሩት ነገር አይኖርም፡፡ ያም ሆነ ይህ አቶ ኃይለማርያም እና የተግባር ጓዶቻቸው በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ላይ የሚደረገውን የአካባቢያዊ ስነምህዳር ውድመት እና የማህበራዊ ቀውስ መግታት እንዲችሉ የህግ ኃላፊነት ያለባቸው የመሆኑን እውነታ ለታሪክ ተመዝግቦ ለተተኪው ትውልድ እንዲቀመጥ ሰለፈለግሁ ነው፡፡ ከዚህም በላይእውነት በመቃብር ለዘላለም ተቀብራ እንደማትቀር፣ሁሉ ቅጥፈትም ለዘላለም በዙፋን ላይ ተሰይማ እንደማትኖር ከአንገት ሳይሆን ከአንጀት መገንዘብ አለባቸው፡፡ 

የኢትዮጵያ የዲያስፖራው ማህበረሰብ አባላትስ ምን እያደረጉ ነው? 

የዲያስፖራው ማህበረሰብ ኢትዮጵያውያን/ት ወገኖቻችንን በጊቤ ሦስት ግድብ ምክንያት ህልውናቸውን ለመታደግ ከሚደረገው እርብርብ ጋር እንቀላቃለለን? በኦሞ ወንዝ ሸለቆ ለሚኖሩ ድምጽ፣ መጠለያ፣ አቅም እና ድጋፍ ለሌላቸው ወገኖቻችን በአንድ ላይ ቆመን ልንናገርላቸው አንችላለን? ከኦሞ ወንዝ ሸለቆ ህዝቦች ጋር በአንድ ላይ ቆመን እንሟገትላቸዋለን ወይስ ደግሞ አቶ መለስ ዜናዊ እንደተናገሩት “በኋላቀር ስልጣኔ” ውስጥ ያሉ በመሆናቸው ምክንያት ጆሮ ዳባ ልበስ እንላቸዋለን? ዓለም አቀፍ ወንዞችን/International Rivers፣ ሂዩማን ራይትስ ዎችን/Human Rights Watch፣ ዓለም አቀፍ የኑሮ ዋስትናን/Survival International፣ እና የአፍሪካ ሀብቶች የስራ ቡድን/the Africa Resources Working Group በመቀላቀል የኦሞን ወንዝ ሸለቆ ኗሪን ህዝብ ህልውና ለመታደግ እና በላያቸው ላይ የተጫነውን ታላቅ መርግ ከጫንቃቸው ላይ ፈንቅሎ ለማንሳት ጥረት ልናደርግ እንችላለን?

የእነዚህን ጥያቄዎች መልሶች አላውቅም፣ ሆኖም ግን ሁልጊዜ እንደማደርገው አደርጋለሁ፡ ትልቁን ሸክም ተሸክመው በመታገል ላይ ላሉት እና አቀበቱን ለመውጣት እየተፍጨረጨሩ ላሉት ውኃ እናቀብል (ከኦሞ ወንዝ ባይሆንም እንኳ)! 

“እንደስብስብ ወይም ደግሞ እንደ ግለሰቦች በተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብቶች ድንጋጌ/Universal Human Rights Declaration of Human Rights እና ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ህግ መሰረት ለዘመናት የኖሩ የአንድ አካባቢ ቋሚ ዝርያ ያላቸው ህዝቦች ባሉበት ቦታ ተደስተው የመኖር መብት እና መሰረታዊ ነጻነቶቻቸው ተከብረውላቸው የመኖር መብት አላቸው፡፡“ (የተባበሩት መንግስታት ድንጋጌ የአንድ አካባቢ ዝርያ ያላቸው ህዝቦች 61/295)

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!    የካቲት 25 ቀን 2006 ዓ.ም

Leave a Reply