በኢትዮጵያ የዘ-ህወሀት የዘር ማጥፋት ተራ ውሸት እና ማወናበጃ ማስረጃ ሲጋለጥ

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም 

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

የጸሐፊው ማስታዋሻ፡ ይህንን ትችት የማቀርበው ለበርካታ ምክንያቶች ነው፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ እ.ኤ.አ መስከረም 5/2016 አቅርቤው በነበረው ትችቴ በአሁኑ ጊዜ በሀገሪቱ ውስጥ መጠነ ሰፊ በሆነ መልኩ ተቀጣጥሎ የሚገኘውን ሕዝባዊ አመጽ ዋጋ ለማሳጣት እና የኢትዮጵያን ሕዝብ እውነተኛ የጀግንነት እና የደፋርነት ታሪክ አዛብቶ ለማቅረብ ዘ-ህወሀት (የህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ) ስልታዊ የሆኑ ውሸቶችን እና ማጭበርበሮችን ተግባራዊ በማድረግ በፍጥነት ታላቅ የሆነ የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻውን ይጀምራል በማለት በግልጽ ተናግሬ ነበር፡፡ ወደ መስከረም 12 ገደማ ዘ-ህወሀት በኢትዮጵያ አድማስ ላይ የዘር ማጥፋት የምጽአት ቀንን በማወጅ ታላቅ የሆነ የማወናበጃ ዘመቻውን በይፋ ጀመረ፡፡ ቀደም ሲል ስናገር የነበረው የዘ-ህወሀት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ በአሁኑ ጊዜ በይፋ ተጀምሮ በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡  አባይ ጸሐይ በሀገሪቱ ውስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል የሚፈጸም መሆኑን በመተንበይ የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ የከፈተ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ የዘ-ህወሀት የዘር ማጥፋት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ፈጣን እና ተከታታይነት ባለው ድርጊት ተሞልቶ ተግባራዊ እየተደረገ ባለበት ሁኔታ ስዩም መስፍን ይህንን የዘር ማጥፋት ወንጀል ትንበያ በማጠናከር የዘ-ህወሀት የብዝሀ ብሄሮች የደህንነት እና ወታደራዊ ኃይሎች መጠነ ሰፊ የሆነውን ሕዝባዊ አመጽ እና መገዳደር እንደሚደመስሱት እና እንደሚያስወግዱት ተናግሯል፡፡

በሁለተኛ ደረጃ ይህንን ትችት በምጽፍበት ጊዜ ግራ በተጋባ ሁኔታ ላይ ነበርኩ።  ምክንያቱም ማንኛውም ምክንያታዊ የሆነ ሰው እንደሚሞግተው ሁሉ በዘራፊዎች ለዘራፊዎች የተቋቋመን የዘራፊ መንግስት ለማስወገድ የሚደረግ መጠነ ሰፊ ትግል በምንም ዓይነት መንገድ ሀገሪቱን ወደ ዘር ማጥፋት ወንጀል ይከታታል የሚል እምነት ስሌለኝ ነው፡፡ ስለሆነም ዘ-ህወሀት በኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል የማይቀር ነው እያለ የሚያሰራጨው ፕሮፓጋንዳ ተጨባጭነት የሌለው የተዛባ የማወናበጃ ዲስኩር ስለሆነ ለዚህ ምላሽ መስጠት ጊዜን በከንቱ የማጥፋት ያህል ነው የሚል ሃሳብ ገንቶኝ ነበር :: ሆኖም ግን መቶ ጊዜ ተደጋግሞ የተነገረ ውሸት እውነት ይሆናል የሚለውን አባባል ከታሪክ ተምሪያለሁ፡፡ ግዙፍ ለሆነ የዘር ማጥፋት ተራ የማወናበጃ የቅጥፈት ፕሮፓጋንዳ ፍቱን ፈዋሽ መድኃኒቱ አወዛጋቢ ባልሆነ ተጨባጭ እውነታ አማካይነት ፈጣን ምላሽ መስጠት ነው፡፡ ስለዘር ማጥፋት ወንጀል የሚነገር የውሸት ማወናበጃ የአመክንዮ ክርክር ሳይቀርብበት ማለፍ የለበትም!

በሶስተኛ ደረጃ ይህንን ትችት የማቀርበው በኢትዮጵያ ውስጥ እየተካሄደ ያለው መጠነ ሰፊ ሕዝባዊ አመጽ ሀገር በቀል አይደለም፣ የኢትዮጵያውያን መገለጫ ነገርም አይደለም፣ ሆኖም ግን በሻቢያ፣ በጸረ ሰላም ኃይሎች፣ በጸረ ልማት ኃይሎች እና በሌሎች በውጭ ኃይሎች (ምናልባትም በመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች) የሚደረግ ሁከት ነው እየተባለ የሚነዛውን እና በአሁኑ ጊዜ በተጠናከረ መልኩ በመካሄድ ላይ ያለውን የዘ-ህወሀትን የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ቅጥፈት ለማጋለጥ ነው፡፡

ዘ-ህወሀት በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ሕዝቦች ሙሉ በሙሉ የተጠላ መሆኑን ባለመቀበል በቅዠት ዓለም ውስጥ በመሆን ጥሬ ሀቁን በመካድ በመንገታገት ላይ ይገኛል፡፡ ለተፈጠረው ሁከት አቀነባባሪዎቹ  ሻቢያ፣ የውጭ ኃይሎች፣ ጸረ ሰላም ኃይሎች፣ ወዘተ እያለ በመጥራት በተደጋጋሚ በውሸት ሲከስ ቢቆይም ዘ-ህወሀት የሕዝቡን መጠነ ሰፊ መገዳደር በተለይም የዘ-ህወሀትን አገዛዝ በጽናት የሚታገሉትን ወጣቶች አኮስሶ እና አሳንሶ በማየት ዋጋ ለማሳጣት እና እርባና የሌለው ለማስመሰል ይፈልጋል፡፡ በዘ-ህወሀት ስለዘር ማጥፋት ወንጀል እየተቀነቀነ ያለው ስብከት እና በውጭ ኃይሎች ሊፈጸም የታቀደ ነው እየተባለ የሚሰራጨው ተራ የቅጥፈት ፕሮፓጋንዳ የዘ-ህወሀት የማታለያ እና ተራ የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ የመሆኑን እውነታነት የኢትዮጵያ ሕዝቦች በውል መገንዘብ አለባቸው፡፡

በአራተኛ ደረጃ የዘ-ህወሀት የዘር ማጥፋት ወንጀል የቅጥፈት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ድብቅ ያልሆነው የዘ-ህወሀት መልዕክት ኦሮሞዎች እና አማሮች አንዳቸው ለሌላቸው ተፈጥሯዊ እና ታሪካዊ ጠላቶች ናቸው፣ እናም በመካከላቸው እውነተኛ ህብረት ወይም አንድነት ሊፈጥሩ አይችሉም የሚል ነው፡፡ አማሮች እና ኦሮሞዎች ዘይት እና ውኃ ናቸው የማለት ዓላማን በመሰነቅ ለማሳመን የሚደረግ ዘመቻ ነው፡፡ በእርግጥ በትክክል የማስታውሰው ከሆነ የዘ-ህወሀት አፈቀላጤ የሆነው ጌታቸው ረዳ በአንድ ወቅት እንዲህ ብሎ ነበር፣ “አማሮች እና ኦሮሞዎች እንደ ጭድ (የኢትዮጵያ ዋና የምግብ እህል የሆነው የጤፍ ገለባ) እና እሳት (የእሳት እና በቀላሉ በእሳት የሚንቀለቀል ደረቅ ሳር እኩያ)  ናቸው፡፡ በምንም ዓይነት ሁኔታ አንድ ሆነው ሊቆሙ አይችሉም“ ነበር ያለው፡፡

ዘ-ህወሀት የረሳው ነገር ቢኖር አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ ጉራጌ፣ ሲዳማ፣ ጋምቤላ፣ አፋር፣ ሶማሊ እና ሌሎች ቡድኖች አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን ቤቶቻቸውን እንደሚመርጉባቸው ሁለት አስፈላጊ ነገሮች እንደ ጭድ እና ጭቃ ናቸው፡፡ ሆኖም ግን ዘ-ህወሀት የድሮውን ያረጀ እና ያፈጀ የከፋፍለህ ግዛ የማታለያ ስልቱን በመተግበር ቀጥሎበት ይገኛል፡፡

በአምስተኛ ደረጃ  የዘ-ህወሀት ሌላው የዘር ማጥፋት ወንጀል የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ደረጃ ደግሞ ሌሎች ትናንሽ ብሄረሰቦች እንዲቀላቀሉት እና የኦሮሞን እና የአማራን ስልታዊ ህብረት በጋራ መመከት እንዲቻል ጥሪ የማቅረብ መሰሪ ተግባር ነው፡፡ በጣም አስከፊ የሆነው የዚህ የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ገጽታ ዘ-ህወሀት የተዛባ የኦሮሞ-አማራ ህብረት ትረካ በመፍጠር የሩዋንዳ ዓይነት የዘር ማጥፋት ዘመቻ/interahamwe (በኪንያርዋንዳ ይህ ማለት “አብረው የቆሙ/የሚሰሩ/የሚዋጉ/ አብረው ጥቃት የሚያደርሱ“) በመፈልፈል እና በማስተባበር ኦሮሞዎች እና አማሮች በትግራይ ሕዝብ ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል ሊፈጽሙ ነው የሚል የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ፕሮፓጋንዳ መክፈት ነው፡፡

በስድስተኛ ደረጃ የዘ-ህወሀትን የውሸት እና የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ በማጋለጥ ለእውነት እያደረግሁት ላለው ዘመቻ ሁሉም የኢትዮጵያ ምሁራን እንዲቀላቀሉኝ ጥሪ ለማስተላለፍ ነው ይህንን ትችት ያቀረብኩት፡፡ በተለይም ደግሞ ዘ-ህወሀት እያቀነቀነ እና እያደረገ ያለውን የመረጃ የማወናበጃ የዘር ማጥፋት ዘመቻ በህብረት ሆነን መመከት እንድንችል ነው ይህንን ጥሪ ያቀረብኩት፡፡ ምሁራን በምልበት ጊዜ አካዳሚሻንን፣ ስኮላሮችን፣ ተመራማሪዎችን፣ ጸሐፊዎችን፣ አርቲስቶችን፣ የሕግ ባለሞያዎችን፣ ጋዜጠኞችን፣ የህክምና ዶክተሮችን፣ ፈላስፎችን፣ የማህበራዊ እና የፖለቲካ አሳቢዎችን ብቻ ማለቴ አይደለም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የተቃዋሚ ፖለቲካ መሪዎችን፣ ተማሪዎችን፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን፣ የሲቪክ ማህበረሰቡን፣ የኃይማኖት እና የሀገር ሽማግሌዎችን እና የኢትዮጵያ ወዳጆችን ሁሉ ይጨምራል፡፡

genocide-mongers2ጊዜው መልካም ነገርን የሚያስቡ ኢትዮጵያውያን ወንዶች እና ሴቶች ሀገራቸውን ለመርዳት በአንድ ላይ የሚቆሙበት ጊዜ ነው፡፡

የማርቲን ሉተር ኪንግን አባባል በመዋስ “በመጨረሻው ጊዜ ኢትዮጵያውያን የሚያስታውሱት ጨቋኞቻቸው ይናገሯቸው የነበሩትን ቃላት እና የንቀት ተግባራት አይደለም፡፡ ሆኖም ግን የእነርሱን ምሁራን እና ጓደኞች ዝምታ እንጅ፡፡

የዘ-ህወሀት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ቁጥር 1፡ የዘር ማጥፋት ተኩላ (ጅብ ) መጣ  እያሉ መጮህ!

መስከረም 12/2016 ወይም ወደዚያ ገደማ ዘ-ህወሀት ለሁለት መስራች አባላቱ ቃለ መጠይቅ በማድረግ የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ቁጥር 1ን ይፋ አደረገ፡፡

አባይ ጸሀይ በኢትዮጵያ ውስጥ የማይቀረውን የዘር ማጥፋት ወንጀል እንዲህ በማለት አወጀ፡

… በሩዋንዳ ሲደረጉ የነበሩ ተመሳሳይ ነገሮች በኢትዮጵያ ውስጥ በመደረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ቱትሲዎች እና ሁቱዎች በመባል የሚጠሩ ሁለት ሕዝቦች አንዱ በስልጣን ላይ የነበረ ሌላኛው ደግሞ ስልጣን የሌለው ነበሩ፡፡ አንደኛው ቡድን በቅኝ ግዛት ዘመን ተጠቃሚ ለመሆን ጥረት ያደረገ እና የሕዝብ መገናኛ ብዙሀንን፣ ወታደራዊ ኃይሉን በቁጥጥሩ ስር በማድረግ የፖለቲካ ፓርቲዎች የዘር ማጥፋት ዘመቻውን አቀነባበሩት፡፡ የነበረውን ልምድ በመጠቀም ቱትሲዎችን በፊቶቻቸው ላይ ምልክት እያደረጉ ለዩአቸው፡፡ ከዚህ በኋላ ቱትሲዎችን እንዲያጠፏቸው ሁቱዎችን አንቀሳቀሷቸው፡፡ እንግዲህ በዚያ ሁኔታ ነው በርካታዎቹ የተገደሉት እና ቀሪዎቹ ደግሞ ለስደት የተዳረጉት፡፡ 

ኢህአዴግ ስልጣን በተቆጣጠረበት ጊዜ ሩዋንዳ እንደ ሀገር፣ እንደ ሕዝብ ተደምስሳ ነበር፡፡ ተበታትና ነበር፡፡ እንደገና አንድ ትሆናለች ብሎ ያሰበ ማንም አልነበረም፡፡ በዚያ ዓይነት ሁኔታ ነበር የተጀመረው፡፡   

ለጥቂት ጊዜም ቢሆን ስለዘር ማጥፋት ወንጀል ቅስቀሳ በሂደት ነበር፡፡ በዝግጅት፣ በመቀነባበር ላይ የነበረ ጉዳይ ነበር፡፡ በኋላ ስለሁኔታው መጸጸት ጀመሩ እናም የብሄራዊ ዕርቅ እና ይቅርታን ሂደት ጀመሩ፡፡ በዚህም መሰረት አንድ ሆነች እና አንድ ሀገር ለመሆን በቁ፡፡ 

በኢትዮጵያ ላይ የሚነሳው ጥያቄ ግን እንደገና ወደ አንድ የመምጣት እና አንድ ሀገር የመሆን ዕድል ሊኖር ይችላልን? የሚለው ነው፡፡ 

ይህንን ነው አንግዲህ ማየት ያለብን፡፡ በሩዋንዳ ውስጥ ሁለት ቡድኖች ብቻ ነበር የነበሩት፡፡ እልቂቱ በጣም አውዳሚ እንደነበር አይተዋል፣ ያንን ሁሉ ዋጋ ከከፈሉ በኋላ ወደ ትክክለኛው አቋም ተመለሱ፡፡  ብሄራዊ ዕርቅ በማውረድ አንድ ሀገር እና ሕዝብ ለመሆን በልማት እና በሰላም ቀጥለው ነበር፡፡ 

በኢትዮጵያ ውስጥ ከ80 በላይ ብሄረሰቦች ስላሉ እና አንድ ቦታ ላይ ግድያ የሚጀመር ከሆነ ወዲያውኑ ከአንዱ ጫፍ ወደሌላው ጫፍ ይዛመታል፡፡ ማንም ሊያቆመው አይችልም፡፡ አሁን ድርጊቱ ተጀምሯል፣ በአንድ ወይም በሁለት ቦታዎች ተጀምሯል፡፡ በሩዋንዳ እንደተደረገው አንድ ጊዜ ከቁጥጥር ውጭ የሚወጣ ከሆነ አንድ ሕዝብ እና አንድ ሀገር የመሆኑ ዕድል አይኖርም“ ነበር ያለው፡፡

አባይ ጸሀይ ሕዝባዊ አመጹን ያቀጣጠሉት እና የመሩት ከሀገር ውጭ የሚገኙት “ሻቢያ [ኤርትራ]“ እና “የውጭ ደጋፊዎች (ምናልባትም ጽንፈኛ ዲያስፖራዎች)  “፣ “ጸረ ሰላም“ እና  “ጸረ ልማት“ ኃይሎች እንደሆኑ በመጥቀስ እንዲህ በማለት ከሷል፡

የጋራ አጀንዳቸው ስርዓቱን ማፍረስ (የዘ-ህወሀትን አገዛዝ) እና በሀገሪቱ ውስጥ ስርዓተ አልበኝነት መፍጠር ነው፡፡ በሚከሰተው ስርዓተ አልበኝነት ‘የገበያ ግርግር ለቀጣፊ በጀው‘ እንደሚባለው አነሰ ቢባል የሀገሪቱን ሀብት የመዝረፍ ዓላማን የሰነቀ እና ለአጭር ጊዜም ቢሆን ስልጣንን መቆጣጠር ነው፡፡ ከዚያ በኋላ የሚዘረፍ ምንም ዓይነት ነገር አይኖርም እናም ሀገሪቱ ትበታተናለች፡፡ ሁከት፣ ግድያ እና እልቂት ይነግሳል፡፡ ያ ከመሆኑ በፊት ግን እርስ በእርሳቸው ይዋጋሉ፡፡ ለምሳሌ ኢህአዴግ ቢዳከም እና ሁኔታውን መቆጣጠር የማይችል ከሆነ ሀገሪቱን መጀመሪያ ማን መዝረፍ እንዳለበት እና የትኛው ኃይል ስልጣን መቆጣጠር እንዳለበት በማሰብ እርስ በእርሳቸው ይዋጋሉ፡፡ ያ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ የማይቀር ጉዳይ ነው፡፡ የውጭ ደጋፊዎች ኢትዮጵያ በልማቷ እንድትቀጥል ለማየት ፍላጎት ያላቸው አይደሉም፡፡ ሰላም የሰፈነባት እና የተረጋጋች ኢትዮጵያን አይፈልጉም፡፡ ደጋፊዎቻቸው ኢትዮጵያ የተዳከመች እና ሰላም እና ልማት የሌለባት ህብረት የሌላት ሀገር እንድትሆን ይፈልጋሉ፡፡ ገንዘብ እና አጀንዳ የሚሰጧቸው ጌቶቻቸው ኢትዮጵያ እንድትበታተን፣ እንድትለያይ እና ደካማ እንድትሆን ይፈልጋሉ፡፡ ኢትዮጵያ እንድትተባበር አይፈልጉም፡፡ ጸረ ኢትዮጵያ እና ጸረ ኢትዮጵያውያን ዓላማ ነው ያላቸው፡፡ 

እንግዲህ ይኸ ነው አጠቃላይ ዓላማቸው እናም አሁንም ሆነ ወደፊት በታሪክ የኦሮሞ እና የአማራ ሕዝቦች ህብረት አይኖራቸውም ብለው ያምናሉ፡፡ በጥንት ጊዜ በኦሮሞዎች እና በአማሮች መካከል ጥላቻ እንዲኖር ያደረጉት እነርሱ ናቸው፡፡ ጥላቻን የፈጠሩ እነርሱ ናቸው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በትግራይ ሕዝብ ላይ የፈጠሩትን የጥላቻ እና የግድያ እንቅስቃሴ በጥንት ጊዜ በኦሮሞዎች እና በአማሮች ላይ ፈጽመውታል፡፡ አሁን ደግሞ በትግራይ ሕዝቦች ላይ ለመድገም ነው ዓላማቸው፡፡ ይህንን ሕዝቡ በሚገባ ያውቀዋል፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ ይህንን በውል ይገነዘበዋል፡፡ ለእራሳቸው ፍላጎት (የውጭ ቀስቃሾች) ለጊዚያዊ ፍላጎት ሲባል በመላ ሀገሪቱ ውስጥ ሁከት ለመፍጠር እና ከዚያም ብጥብጥ ተጠቃሚ ለመሆን እንጅ ስለሀገሪቱ አንድነት የሚያገባቸው ጉዳይ ሆኖ አይደለም፡፡ የእነርሱ ዓላማ በሀገሪቱ ውስጥ በሕዝቦች መካከል ሁከት፣ ግጭት  መፍጠር እና እልቂትን መፈጸም ነው“ በማለት ነበር ሀሳቡን የቋጨው፡፡

አባይ ጸሀይ

አባይ ጸሀይ

እንደ አባይ ጸሀይ ንግግር ከሆነ የውጭ ቀስቃሾች እና የውጭ የገንዘብ ድጋፍ አድራጊዎች ዋና ዓላማ እና አጀንዳ በኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመጫር ነው፡፡

ስለአባይ ጸሀይ ትንታኔ አስገራሚው ነገር በሩዋንዳ ውስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል እያለ ሲጭህ የነበረውን እና የሩዋንዳን የዘር ማጥፋት ወንጀል የጀመረውን ፓውል ጋሜን ሳይጠቅስ ጸጥ ብሎ የማለፉ ጉዳይ ነው፡፡

በፓውል ጋሜ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ወቅት የእርሱ ዋና ሰው የነበረው እና በአሜሪካ የሩዋንዳ አምባሳደር ሆኖ ያገለገለው ቲኦገኝ ሩዳሲንግዋ እ.ኤ.አ በ1994 በመኩራራት ፕሬዚዳንት ሀቢያሪማናን ያሳፈረው አውሮፕላን እንዲመታ ትዕዛዝ ሲሰጥ ሰምቻለሁ“ ነበር ያለው፡፡

አባይ ጸሐይ የኢትዮጵያ ፓውል ጋሜ ነውን?

ስዩም መስፍን ሁለተኛውን የዘር ማጥፋት የምት ትረካ አስተላልፏል፡፡

ስዩም የዘር ማጥፋት ወንጀሉ ይከሽፋል ምክንያቱም በኢህአዴግ (የዘ-ህወሀት ግንባር ድርጅቶች)  የተመሰረቱት የደህንነት እና ወታደራዊ ተቋሞች እንዳይፈጸም ይከላከሉታል ይደመስሱታል በማለት እንዲህ ነበር ያለው፡

“እነርሱ (የውጭ ቀስቃሾች እና የገንዘብ ደጋፊዎቻቸው) ዕድል የሚያገኙ ከሆነ ብሄሮችን፣ ብሄረሰቦችን እና ሕዝቦችን ብቻ ሳይሆን የሚነጣጥሉት ቤተሰብን ሳይቀር ወደ ሁለት ወይም ሶስት ክፍል ነው የሚከፋፍሉት፡፡ ሆኖም ግን የእነርሱ አጀንዳ ይሳካል ማለት በጸሐይ ላይ ጤዛ እንደማየት ያህል ነው፡፡ የዘር ማጥፋት እሳትን ማራገቡን ይቀጥላሉ፡፡ እርስ በእርሳቸው አይተማመኑም፡፡ አንዱ ሌላውን ለማጥቃት ኃይል ይጠቀማሉ፡፡ ጠባቦች እና ትምክህተኞች በአንድ ላይ ሆነው መልካም አስተዳደር ያለው ስርዓት (መንግስት) ለመፍጠር በአንድነት መሄድ አይችሉም፡፡ በፍጹም! የዜሮ ድምር ውጤት ነው ያለው፡፡ 

የደህንነት እና የመከላከያ ተቋሞቻችንን እስቲ እንመልከት፡፡ እነዚህን ተቋሞች የሚቆጣጠሯቸው እና በበላይነት የያዟቸው ትግሬዎች ናቸው ይላሉ፡፡ እናም እነዚህን መዋቅሮች ለማውደም ይፈልጋሉ፡፡ ጠባቦች እና ትምክህተኞች ይህንን ዘመቻ ተቀላቅለዋል፡፡ 

ግን ለምን? እውነታው ተገልጦ ሲታይ የተለዬ ነገር ሆኖ ይገኛል፡፡ የኢህአዴግ መዋቅሮች እና ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች የኢትዮጵያን ሕዝብ ብዝሀነት የሚያሳዩ መዋቅሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መዋቅሮች ሁሉንም ኢትዮጵያውያን አካትተው ይዘዋል፡፡ በማህበረሰቡ ውስጥ ምንም ዓይነት ዕድል ተሰጥቷቸው የማያውቁትን ለምሳሌ ያህል እንደ ቤንሻንጉል፣ ሶማሊ፣ አፋር የመሳሰሉትን ሕዝቦች በመከላከያ ተቋማት ውስጥ እንዲካተቱ በማድረግ የወታደራዊ ኃይሉን ገንብተናል፡፡ 

ስለደህንነት መዋቅሩ እስቲ እንነጋገር፡፡ የሀገሪቱ መስታወት ነው፡፡ እያንዳንዱ ብሄር ብሄረሰብ በደህንነት መዋቅሩ ውስጥ የእራሱን ምስል በመስታወቱ ውስጥ ይመለከታል…“ ነበር ያለው፡፡

 ስዩም መስፍን

ስዩም መስፍን

በሌላው ትችቱ ስዩም መስፍን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ናዚዎች በአይሁዶች ላይ ሲፈጽሙት የነበረውን ጭፍጨፋ በአሁኑ ጊዜ ኦሮሞዎች እና አማሮች በትግሬዎች ላይ ሊያደርጉት ከሚችሉት ጭፍጨፋ ጋር አንድ አድርጎታል፡፡ በእርግጥ ስዩም ኢትዮጵያውያንን እንደ ናዚዎች እና የትግራይን ሕዝብ ደግሞ እንደ አይሁዶች የናዚ አገዛዝ ዓይነት እኩል አድርጎ ማቅረቡ ከልቡ በመነጨ መልኩ የምሩን ነውን?

ስዩም ወታደራዊ እና የደህንነት ኃይሉ ጎሳን ባካተተ መልኩ በኢትዮጵያ ውስጥ ሁሉም እንዲገቡ በማድረግ ዘ-ህወሀት የመጀመሪያው አገዛዝ ነው ሲል ይህንን የታሪክ ትምህርት ከየት እንዳመጣው ግልጽ አይደለም፡፡ ምናልባትም በጫካ ውስጥ በነበረበረት ጊዜ ስለወታደራዊ ኃይሉ ሲነገረው ከነበረው የተባለ፣ የሸውክ እና የሀሜት ትረካ ስለኢትዮጵያ የቃል አፈ ታሪክ እየተቆነጸለ ትንሽ በትንሽ ሲሰጠው ከነበረው በመነሳት ሊሆን ይችላል፡፡

በአጼ ኃይለ ሥላሴ የአገዛዝ ዘመን የነበረው ወታደራዊ አመራር በዘ-ህወሀት አገዛዝ ካለው የበለጠ ብዝሀነት የሚስተዋልበት ነበር፡፡ ምናልባት ስዩም በእርሱ የዘ-ህወሀት አገዛዝ ያለውን ወታደራዊ የአመራር ስብጥር እንደገና ዘወር ብሎ ቢፈትሸው የተሻለ ነገር ሊሆን ይችላል፣ አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት ወይ አይልም የሚባለው ተረት ካልሆነ በስተቀር፡፡ እውነታው ፍርጥርጥ ተደርጎ ሲታይ ግን በንጉሱ እና በደርግ በሁለቱም አገዛዞች የወታደራዊ አመራሩ እና የባለ ዝቅተኛ ማዕረግ መኮንነኖች ስብጥር በኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውን የወታደራዊ ኃይል የጎሳ ብዝሀነት ስብጥር በግልጽ የሚያሳይ ነበር፡፡ ማንኛውም የጎሳ አባል የሆነ ዜጋ ከወታደራዊ ኃይል ተሳትፎ አይከለከልም ነበር፡፡ በእራሱ ድንቁርና እራሱን ደንቆሮ ላደረገ ደንቆሮ ሊታዘንለት ብቻ ይገባል፡፡ ሆን ብሎ በእራሱ ፈቃድ ለደነቆረው ለስዩም መስፍን አዝናለሁ፡፡

እ.ኤ.አ መስከረም 5/2016 “የዘ-ህወሀት ተራ ቅጥፈት እና የመረጃ የማወናበጃ መረጃ የማዛባት ዘመቻ“ በሚል ርዕስ አቅርቤው በነበረው ትችት የዘ-ህወሀት አገዛዝ በአሁኑ ጊዜ በእራሱ ላይ ተቀጣጥሎ የሚገኘውን ሕዝባዊ አመጽ አሳንሶ እና አኮስሶ ለማቅረብ እና በእነርሱ ላይ ተነሳ በማለት የአማራ-ኦሮሞ ህብረት እያሉ በሚጠሩት ላይ የአጻፋ ፕሮፓጋንዳ ለመስራት እና ለማጥፋት መጠነ ሰፊ የሆነ የመረጃ ማዛባት ማወናበጃ ዘመቻ እያደረገ መሆኑን ለዓለም ሕዝብ አሳውቄ ነበር፡፡

ባለፈው ሳምንት በቪዲዮ በተቀረጸው እና በኢሳት ቴሌቪዥን ከርዕዮት ዓለሙ ጋር በአማርኛ አድርጌው በነበረው ቃለ መጠይቅ ይህንን ጉዳይ በመጠኑም ቢሆን ግልጽ አድርጊያለሁ፡፡መስከረም 5 አቅርቤው በነበረው ትችቴ ዘ-ህወሀት በቅርብ ጊዜ ውስጥ ግልጽ የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻውን በመጀመር 10 ዓይነት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ምሳሌዎችን በዝርዝር አቅርቤ ነበር፡፡

በመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ዝርዝር ውስጥ በቁጥር 1 ላይ አቅርቤው የነበረው በጎሳ ቡድኖች በተለይም በኦሮሞ እና በአማራ ጎሳዎች መካከል የማይታረቅ ጥላቻ ለመፍጠር የተወሰኑ ታሪካዊ ክስተቶችን እና ግጭቶችን በመምረጥ መጠቀም በሚል ለይቸ አስቀምጨ ነበር፡፡

ይህንን ትችት ካቀረብኩ ከአምስት ቀናት በኋላ  ዘ-ህወሀት አማሮች እና ኦሮሞዎች በኢትዮጵያ ውስጥ የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመፈጸም አቅደዋል በማለት የዘር ማጥፋት ተኩላ (ጅብ) እያለ በመጮህ! የውሸት መረጃ የማወናበጃ ዘመቻው ቁጥር 1ን በይፋ ጀመረ፡፡

የዘር ማጥፋት ቅስቀሳው ማስጠንቀቂያ ዋና መልዕክተኛ የሆኑት ሁለቱ የዘ-ህወሀት ቁንጮ ባለስልጣኖች አባይ ጸሀይ እና ስዩም መስፍን ለዚህ ዕኩይ ድርጊት ምርጫ ሆነው የመቅረባቸው ሁኔታ በጣም የሚያስገርም ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ እንደ አባይ እና ስዩም ያሉትን በመንግስት ላይ መንግስት የሆኑ ሰዎች ዘ-ህወሀት ከትይንቱ ከመጋረጃ ጀርባ ያስቀምጣቸው ነበር እንጅ እንደዚህ እንደ አሁኑ ጊዜ በአደባባይ ላይ አያውጣቸውም ነበር፡፡ ዘ-ህወሀት እነዚህን ቁንጮ ባለስልጣኖቹን በአሁኑ ጊዜ በይፋ ወደ አደባባይ ሊያወጣቸው የቻለው ለምንድን ነው?

አባይ ጸሀይ ዘ-ህወሀትን እ.ኤ.አ መስከረም 1974 ከመሰረቱት መስራቾች ከ7ቱ መካከል አንዱ ነው፡፡ የዘ-ህወሀት የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና ፖሊስ ዋና ተቆጣጣሪ ካቦ ነበር፡፡

ስዩም መስፍንም እንደዚሁ ከዘ-ህወሀት መስራቾች መካከል አንዱ ነው፡፡ የዘ-ህወሀት የቀድሞው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና አሁን ደግሞ በቻይና አምባሳደር ነው አየተባለ ይወራል፡፡

ዘ-ህወሀት ለምንድን ነው እነዚህ ሁለት ቱባ ባስልጣኖቹ ወደ አደባባይ ወጥተው የዘር ማጥፋት ወንጀል ተኩላ ከበሩ ጋ ቆሟል እያሉ እንዲጮሁ ያደረገው?

በሚስጥር፣ ባልተጠበቀ መልኩ ስለሚከሰተው እና እየዳኸ ስለሚመጣው የዘር ማጥፋት ወንጀል የተደረገው የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ተሳክቷልን?

ዘ-ህወሀት በጥላቻ የተመሰረተ እና በዘር ማጥፋት ስሜት የሚነዳ ጭፍን ድርጅት ነው፡ ማስረጃውን እነሆ!

ዘ-ህወሀት በጥላቻ የተመሰረተ ድርጅት የመሆኑ እውነታን ማንም የዘህዋሃት መሪም ሆነ ደጋፊ ክዶት አያውቅም።

በጣም አሳማኝ እና ጠንካራ የሆነው የዘ-ህወሀት የዘር ማጥፋት የርዕዮት ዓለም ፍልስፍና ማስረጃ ከቀድሞው የህወሀት የገንዘብ ግምጃ ቤት ኃላፊ እና ቁንጮ አመራር ከነበሩት እና ፍርሀት የለሽ እና የማይበገሩ እውነት ተናጋሪ ኢትዮጵያዊ አርበኛ በመሆን ከድርጅቱ ለቅቀው ከሄዱት ከገብረ መድህን አርዓያ የሚገኝ ነው፡፡ (ለመስረቅ ፈቃድ ያላቸው በሚል ርዕስ እ.ኤ.አ ግንቦት 2011 አቅርቤው የነበረውን ትችት ይመልከቱ፡፡)

በቪዲዮ በተቀረጸው እና ልዩ በሆነው ቃለ መጠይቅ (ከዚህ በታች በአማርኛ የቀረቡትን ቃላት ወደ እንግሊዝኛ የተረጎምኩትን) ገብረ መድህን ህወሀት የኢትዮጵያውያንን ማንነነት፣ ታሪክ እና አስተሳሰብ ለማጥፋት ህወሀት ይጠቀምባቸው የነበሩትን 4 መሰረታዊ የርዕዮት ዓለም ምሰሶዎች (በ6፡10 ቪዲዮውን ይጀምሩ) እንዲህ በማለት ገልጸዋል፡

1ኛ) ኤርትራ የኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ናት፡፡ ኤርትራ የበለጸገች ሀገር ናት፡፡ ኤርትራ ከኢትዮጵያ በፊት ቀድማ የኖረች ሀገር ናት፡፡ ኢትዮጵያ የተፈጠረችው በንጉስ ምኒልክ ነው፡፡ ኢትዮጵያ የሚለው ስያሜ አይታወቅም፡፡ ኢትዮጵያ ታሪክ የላትም፡፡ ምንም፡፡ 

2ኛ) ትግራይ በንጉስ አጼ ምኒልክ የተወረረች እና የአማራ ቅኝ ግዛት የተደረገች ነጻ እና ሉዓላዊ የሆነች ሀገር ናት፡፡ ትግራይ የአማራ ቅኝ ግዛት ናት፡፡ ይኸ ነው እንግዲህ በወያኔ (ህወሀት) ፕሮግራም (ማኒፌስቶ) እና ዋና የፖሊሲ በሆነው ሰነድ (ማኒፌስቶው በቪዲዮው ቀርቧል) ተጽፎ የሚገኘው፡፡  ስለሆነም ትግራይን ከአማራ ቅኝ ተገዥነት ነጻ ማውጣት እና የትግራይ ሬፐብሊክን መመስረት አለብን፡፡ [የህወሀትን ማኒፌስቶ እንዳለ የመጀመሪያውን በእጅ የተጻፈ ሰነድ ለማንበብ እዚህ ጋ ይጫኑ፣ ለመስመር ግንኙነት ደግሞ እዚህ ጋ ይጫኑ፡፡] 

3ኛ) አማሮች የትግራይ ጠላቶች ናቸው፡፡ አማሮች ጣላቶች ብቻ አይደሉም ሆኖም ግን ድርብ ጠላቶች ናቸው፡፡ ስለሆነም አማሮችን መግደል አለብን፡፡ እነርሱን ማጥፋት አለብን፡፡ አማሮች ካልጠፉ፣ ካልተሸነፉ፣ ከገጸ መሬት ካልጠፉ ትግራይ በነጻነት ልትኖር አትችልም፡፡ ወደፊት ለምንመሰርተው መንግሰት አማራ ዋና መሰናክል ይሆንብናል፡፡ (አጽንኦ ተጨምሯል፡፡) 

4ኛ) ኢትዮጵያ በምኒልክ ወረራ የተመሰረተች ሀገር እንደመሆኗ መጠን እና በሚኒልክ ወረራ የተፈጸመባቸው በርካታ ብሄሮች እና ብሄረሰቦች ያሉ በመሆኑ እነዚህ ቡድኖች (በቪዲዮ የሚታየውን ማኒፌስቶ ይጫኑ እና ይመልከቱ) በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ እየተባለች ከምትጠራዋ ሀገር ነጻ በመውጣት የእራሳቸውን ሀገር መመስረት አለባቸው፡፡ ኢትዮጵያ እየተባለች የምትጠራዋ ሀገር አዲስ ናት እናም 100 ዓመት እድሜ እንኳ የላትም፡፡ ይህች ሀገር መደምሰስ እና ባዶ መሆን አለባት፡፡ ብሄሮች እና ብሄረሰቦች የእራሳችንን መንግስታት ማቋቋም አለብን፡፡ ኤርትራ ነጻነቷን ማግኘት አለባት እናም የትግላችን መሰረት የሚሆነው ይኸ ነው” የሚሉት ናቸው እንግዲህ የህህወሀት አራቱ የርዕዮት ዓለም ፍልስፍና ምሰሶዎች፡፡

ህወሀት አማራን ጥላሸት ለመቀባት እና ለማዋረድ የተጠቀመባቸው ቃላት እ.ኤ.አ በ1980ዎቹ እና በ1990ዎቹ መጀመሪያ አካባቢ በሩዋንዳ ሁቱዎች በቱትሲዎች ላይ ሲያካሂዱት ከነበረው የንቀት ዘለፋ ጋር አንድ እና ተመሳሳይ ነው፡፡ ሁቱዎች የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ዘመቻን ከማወጃቸው በፊት በቱትሲዎች ላይ ስም የማጠልሸት እና የማዋረድ ተግባራትን ይፈጽሙ ነበር፡፡

የገብረ መድህንን የምስክርነት ማስረጃ ወይም ደግሞ የእርሱን ምስክርነት የሚደግፉትን የዘ-ህወሀትን የውስጥ ፖሊሲ በርካታ የማስረጃ ሰነዶችን ጠንካራነት እስከ አሁን ድረስ ፊት ለፊት በመቅረብ የሞገተ እና ለማስተባበል የሞከረ አንድም ሰው የለም፡፡

ባለፈው ሳምንት “ጸጥታውን መስበር፡ ከትግራውያን ለትግራውያን የተላለፈ መልዕክት“ በሚል ርዕስ ሲራክ አማረ እና ጥላሁን ወልደስላሴ የተባሉ የቀድሞ የህወሀት ኃላፊዎች የነበሩ ሰዎች ገብረ መድህን ስለዘር ማጥፋት ፕሮፓጋንዳ ሲያቀርብ የነበረውን ታሪክ በዘከረበት ሁኔታ በተመሳሳይ መልኩ ከሁሉም ጋር ሊዛመድ በሚችል መልኩ ይህንኑ እውነታ አረጋግጠዋል፡፡

አሁን በህይወት የሌለው አምባገነኑ መለስ ዜናዊ በአንድ ወቅት የሰጠው አስተያት እና ምልከታ ገብረ መድህን እየጮኸበት ስላለው ምስክርነት ማረጋገጫ ነው፡፡ መለስ በአንድ ወቅት አሁን በህይወት ለሌሉት እና የታወቁ ኢትዮጵያዊ ለነበሩት ለፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን እንዲህ በማለት ተናግሮ ነበር፣ “ትግሬዎች አክሱም አላቸው፣ ግን ይኸ ለጉራጌ ምን ማለት ነው? አገዎች ላሊበላ አላቸው ግን ይኸ ለኦሮሞዎች ምን ሊሆን ይችላል? ጎንደሬዎች ቤተመንግስቶች አሏቸው፣ ግን ይኸ ለወላይታው ምኑ ነው?“ ነበር ያለው በሰለጠነ በሀገር የመሪነት አንደበት ሳይሆን በመንደርተኛ ተራ የወሮበላ የዘረኛ ቋንቋ፡፡

ከዚህም በተጨማሪ አምባገነኑ መለስ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ “ቁራጭ ጨርቅ” ነው፣ የኢትዮጵያ ታሪክም የ100 ዓመት እድሜ ብቻ ነው ብሎ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ከዚህ ውጭ እራሳቸውን የሚዶሉ ካሉ ተረት ትረካ ነው ነበር ያለው፡፡

መለስ በህይወት በነበረበት ጊዜ ያምነው እንደነበረው እና አሁንም ዘ-ህወሀት እንደሚያምነው ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር የለችም፣ ያለው በአማሮች የተፈጠረው ምዕናባዊ የሆነው ምድር እና የብሄሮች እና የብሄረሰቦች ስብስብ ብቻ ነው፡፡ (እ.ኤ.አ ግንቦት 2016 “ኢትዮጵያ ሕገ መንግስት ያስፈልጋታልን?“ በሚል ርዕስ አቅርቤው የነበረውን ትችት ይመልከቱ፡፡)

የገብረመድህን ምስክርነት እና በሰነድ የተደገፈው ማስረጃ ጠቀሜታ የዘ-ህወሀትን ማኒፌስቶ በመመርመር በአሁኑ ጊዜ የዘ-ህወሀት መመሪያ እና የፍልስፍናው መሰረት መሆኑን በሚገባ ያስገነዝባል፡፡ በአሁኑ ጊዜ ካሉትም ሆነ ወይም ደግሞ ቀደም ከነበሩት የህወሀት አመራሮች የህወሀትን ማኒፌስቶ ለማረጋገጥም ሆነ የሰነዱን ይዘት ለማሻሻል ሰነዱን በቡድንም ሆነ በተናጠል በፊርማው ያጸደቀ እና ያረጋገጠ ሰው ያለመኖሩ ጉዳይ እጅግ በጣም የሚያስገርም ነገር ነው፡፡

የህወሀት ማኒፌስቶ በጥንቃቄ እና በሚገባ ሲመረመር በአማሮች ላይ የዘር ማጥፋት ሀሳቦች እና ዕቅዶች እንዳሉ እና በመጨረሻም ኢትዮጵያን እና ሕዝቧን መከፋፈል እና መበታተን የሚሉትን ነገሮች አርግዞ እንደሚገኝ መገንዘብ ይቻላል፡፡

ማኒፌስቶው በአማራ ሕዝቦች የበላይነት በትግሬዎች ላይ ይደርስ ስለነበረው ጭቆና፣ ስቃይ፣ መፈናቀል፣ የብሄር የበላይነት እና ብዝበዛ በጥላቻ  ንግግር የተሞላ ሰነድ ነው፡፡

ማኒፌስቶው የአማራ መኳንንት እና ደጋፊዎቻቸው (ከዳግማዊ ምኒልክ ዘመን በኋላ) የትግራይን ነጻነት እንደወሰዱ እና የሕዝቦችንም አንድነት እያናጉት እንደሆነ አድርጎ ያስቀምጣል፡፡

ማኒፌስቶው ሁሉም የአማራ ሕዝቦች የትግራይን ሕዝቦች በድንቁርና፣ በበሽታ እና በረሀብ ባህር ውስጥ እንዲሰምጡ ያደረጉ ናቸው በማለት ይከሳል፡፡

ማኒፌስቶው ሁሉም የአማራ ሕዝቦች በትግራይ ሕዝብ ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል እንደፈጸሙ እና የትግራይ ልጆች ያለፈቃዳቸው አማራ እንዲሆኑ በኃይል ይገደዱ እንደነበር ያስቀምጣል፡፡ የትግሬዎችን መሬት በኃይል ይቀሟቸው እና ይጨቁኗቸውም ስለነበር ትግሬዎች ለመሰደድ ይገደዱ እንደነበር አድርጎ ይናገራል፡፡

ማኒፌስቶው የአማራ ሕዝቦች የትግራይ ሕዝቦች ለረዥም ጊዜ በአማራ ጨቋኝ ሕዝቦች እና ጭቆናን የመንግስታቸው ፖሊሲ ባደረጉ አማሮች አማካይነት የሰብአዊ እና የፖለቲካ መብቶቻቸውን ይነጠቁ እንደነበር በግልጽ ይናገራል፡፡

ማኒፌስቶው የአማራ ጨቋኝ ሕዝቦች በትግራይ ሕዝቦች ላይ የኢኮኖሚ ብዝበዛ በማድረግ የበላይነትን ያሳዩባቸው እንደነበር ያስቀምጣል፡፡

ማኒፌስቶው የአማራ ሕዝቦች እኛን የትግራይ ህዝቦችን) ለማዳከም እና ልማዶች እና ቋንቋችንን ለማጥፋት ወይም ደግሞ የአማራ ገዥዎችን ፍላጎቶች ለመጠበቅ ሲሉ አማሮች የነበረንን የ3 ሺ ዘመን ታሪክ እና ልማድ መፈክር አድርገው እና ለእራሳቸው ክብር ማስገኛ አድርገው ሲጠቀሙበት ቆይተዋል ይላል፡፡

ማኒፌስቶው ሁሉም የአማራ ሕዝቦች (በስልጣን ላይ ያሉ የተወሰኑ የአማራ ግለሰቦች ወይም ደግሞ ቡድኖች ብቻ ሳይሆኑ) ሁላቸውም በአጠቃላይ ደም የተጠሙ ዘር አጥፊዎች ስለሆኑ ከምደረ ገጽ መጥፋት አለባቸው ይላል፡፡

የህወሀት ማኒፌስቶ ከገጽ ብዛቱ በስተቀር ከናዚ ሜይን ካምፕ ድርጅታዊ እና የርዮት ዓለም ፍልስፍና ጋር መሳ ለመሳ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ በማኒፌስቶው ህወሀት ከአማራ ጨቋኞች ጋር የሚያደርገውን ትግል ዘርዝሮ ያስቀመጠ እና አስላጊ ናቸው ያላቸውን የዘር ማጥፋት ፍልስፍና ጉዳዮች እና ወደፊት የአማራ ሕዝብ ሳይኖር እነርሱ ብቻ ስለሚሰሩት ስራ ዕቅድ ያስቀምጣል፡፡

አሁን በቅርቡ “ኢትዮጵያ፡ እ.ኤ.አ በ2016 የአማራ ደደቦች እና የኦሮሞ ወንጀለኞች እና አሸባሪዎች መነሳት“ በሚል ርዕስ አዘጋጅቸው በነበረው ትችቴ የዘ-ህወሀትን የጥላቻ ፖለቲካ መርምሪያለሁ፡፡

ህወሀት እንደ ድርጅት ጥላቻ በተሞላባቸው 7 አሮጌ ወሮበላ ዘራፊዎች ጭንቅላት ውስጥ ተጸንሶ የተወለደ የማፊያ ድርጅት እንደሆነ የሚያጠያይቅ ጉዳይ አይደለም፡፡ የዘ-ህወሀት መሪዎች እና ደጋፊዎች ጥላቻን ይተነፍሳሉ፡፡ እናም ጥላቻ በደም ስሮቻቸው ውስጥ ይዘዋወራል፡፡

የዘ-ህወሀት የተበሳጨ የዘር ማጥፋት ጭራቅ እ.ኤ.አ በ2016 እንደገና ተመልሶ መጥቷል፣

ዘ-ህወሀት አስፈላጊ ሆኖ ባገኘው ሁሉ የማጭበርበር ድርጊቱን ለመፈጸም እንዲመቸው የተለመደውን የተበሳጨ አዛውንት ጭራቅ መልሶ አምጥቶታል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የዘ-ህወሀት አህያ ሳር ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ደግሞ ሳሩን የሚያጭዱ ማሽኖች ናቸው!

እ.ኤ.አ በነ1990ዎቹ አሁን በህይወት የሌለው የዘ-ህወሀት ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ፈላጭ ቆራጭ ቁንጮ የነበረው መለስ ዜናዊ ያለእርሱ እጅ እና የዘ-ህወሀት አመራር ኢትዮጵያ ዩጎስላቪያ እንደሄደችበት መንገድ ትሄዳለች ማለት ይወድ ነበር፡፡ አምባገነኑ መለስ ምክር ሲሰጥባት የነበረችው የቀድሞዋ ዩጎስላቪያ በአሁኑ ጊዜ ሰባት ሀገራት ሆናለች፡፡ መለስ እ.ኤ.አ በ2009 በቢዲዮ በተቀረጸ ቃለ መጠይቅ ተመሳሳይ መልዕክት ነበር ደግሞ ያስተላለፈው፡፡

መገነጣጠል ለኢትዮጵያ የመለስ ህልም ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜም የዘ-ህወሀት ህልም ሆኖ ይገኛል፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት መለስ እና የእርሱ ዘ-ህወሀት የአገዛዝ ዘመናቸውን ለማራዘም ሲሉ ኢትዮጵያን ሌት ከቀን በመከፋፈል እና እንደ ሽንኩርት በመክተፍ ላይ ይገኛሉ፡፡ የመሄጃቸው ቀን ሲደርስ ምንም ነገር እንዳይተርፋት ያደርጋሉ፡፡ በኢትዮጵያ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል እንዳለችው አህያ ተረት ማለት ነው፡፡ ዘ-ህወሀት እርሱ ከሞተ በኋላ ሀገሪቱን ጎርፍ ያጥለቅልቃት ብሎ እንደሚመኘው ማለት ነው፡፡

የቀድሞዋ ዩጎስላቪያ ለ7 መንግስታት ተከፋፈለች፡፡ ኢትዮጵያ በዘ-ህወሀት አገዛዝ በ9 አፓርተይድ መሰል ባንቱስታንስ እየተባሉ በሚጠሩ ክልሎች ወይም የማጎሪያ በረቶች ተከፋፈለች፡፡ ዘ-ህወሀት በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ በእነርሱ መዳፍ ላይ ካልሆነች በስተቀር ወደ 9 ቁርጥራጭነት ትቀየራለች በማለት ኢትዮጵያውያንን እና የዓለም አቀፉን ማህበረሰብ ለማሳመን ሌት ቀን በመቋተን ላይ ይገኛል፡፡ ዘ-ህወሀት ላለፉት 25 ዓመታት ያህል ኢትዮጵያን በ9 ባንቱስታንስ ከፋፍሎ ሲያተራምስ ቆይቷል፡፡ አሁን ደግሞ እነርሱ ካልገዟት በስተቀር ኢትዮጵያ እንደገና ወደ 9 ባንቱስታንስ ትከፋፈላለች እያለ በማስፈራራት ላይ ይገኛል፡፡ የእብድ አመክንዮ! በአማርኛ እንደሚተረተው ተረት “ደፋር ሌባ ስለሰረቀው ሀብት የባላቤትነት መብት ንብረቱ ከተሰረቀበት ባለቤት ጋር ልደራደር ይላል“ ይባላል፡፡

የጥቂት ነጮች ዘረኛ የበላይ ዘገዛዝ የአፓርታይድ መሪዎች በደቡብ አፍሪካ ውስጥ የጥቂት ነጮች አገዛዝ በቀጣይነት መኖር እንደሚያስፈልገው ለማሳመን በማለት እነርሱ ከስልጣናቸው ከተወገዱ ደቡብ አፍሪካ በሁለት ምዕራፍ አብዮት ትበታተናለች፡፡ እናም ኮሙኒዝም በመላ አፍሪካ ውስጥ ይስፋፋል የሚል የክርክር ጭብጣቸውን ያቀርቡ ነበር፡፡ ዘ-ህወሀትም በበኩሉ ተመሳሳይ የክርክር ጭብጡን በማቅረብ ላይ ይገኛል፡፡ እነርሱ በስልጣን ላይ ከሌሉ ኢትዮጵያ በመላ የአፍሪካ ቀንድ ሊያሳትፍ በሚችል መልኩ በጎሳ ትከፋፈላለች እያሉ በመስበክ ላይ ይገኛሉ፡፡

እ.ኤ.አ ግንቦት 6/2005 ምርጫው ከመካሄዱ ከስድስት ቀናት በፊት አምባገነኑ መለስ ግንቦት 15 በሚካሄደው ምርጫ የምርጫው ድል ወደ ተቃዋሚዎች የሚሄድ ከሆነ እንደ ሩዋንዳ ዓይነት የዘር እልቂት ሊፈጸም ይችላል በማለት ተቃዋሚዎችን በመክሰስ የጎሳ ጥላቻን ለማስፋፋት ጥረቱን ቀጥሎበት ነበር፡፡ አምባገነኑ መለስ እንዲህ በማለት ነበር የተማጽዕኖ ጥሪውን ያቀረበው፡

“ግንቦት 15 በሚደረገው ሀገር አቀፍ ምርጫ የጎሳ ጥላቻ ፍልስፍና ለሚያራግቡት፣ መከፋፈልን ለሚሰብኩት ለተቃዋሚዎች ድምጻችሁን ባለመስጠት በድምጽ ካርዳችሁ እንድትቀጧቸው ለኢትዮጵያ ሕዝብ የተማጽዕኖ ጥሪዬን አቀርባለሁ…የእነርሱ ፖሊሲዎች በሩዋንዳ ኢንተርሃምዌ ሁቱዎች ቱትሲዎችን በሚጨፈጭፉበት ጊዜ ሲያደርጉት እንደነበረው ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ በጎሳዎች መካከል ጥላቻን እና በቀልን የሚቀፈቅፉ ናቸው፡፡ የዚህ ዓይነቱ ፖሊሲ አደገኛ እና ወደ ኃይል እና እልቂት የሚያመራ ነው“ ነበር ያለው ዓይኑን በጨው ታጥቦ የእምዬን ወደ አብዬ በማላከክ፡፡

እ.ኤ.አ ግንቦት 16/2005 አምባገነኑ መለስ ዜናዊ እንዲህ በማለት ነበር ያወጀው፣ “ለቀጣዩ አንድ ወር ያህል በከተማው ውስጥ በአካባቢው ምንም ዓይነት ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ አይፈቀድም፣ የደህንነት እና የፖሊስ ኃይሉ እንዲሁም ሚሊሻው አስፈላጊ የሆነውን ማናቸውንም ዓይነት እርምጃ ሁሉ ኃይልን ጨምሮ እንዲወስዱ“ በማለት ነበር ትዕዛዝ ያስተላለፈው፡፡

እ.ኤ.አ ህዳር 2006 መለስ እራሱ ያቋቋመው የምርመራ ኮሚሽን 193 ምንም ዓይነት የጦር መሳሪያ ያልታጠቁ ሰላማዊ ተቃዋሚዎች ግንባራቸውን እና ደረታቸውን ዒላማ በማድረግ የተገደሉ ሲሆን 763 የሚሆኑ ንጹሀን ሰላማዊ ዜጎች ደግሞ በጥይት ቁስለኛ ሆነዋል በማለት ነበር ዘገባውን ያቀረበው፡፡

የአምባገነኑ የመለስ እልቂቶች (የፖለቲካ መጠነ ሰፊ የኃይል ጥቃት መፈጸም የዘር ማጥፋት ወንጀል) በሰው ልጆች ላይ የተፈጸመ የዘር ማጥፋት ወንጀልን ይወክላል፡፡

እ.ኤ.አ ሰኔ 2005 የግንቦቱ ምርጫ ከተጠናቀቀ ከአንድ ወር በኋላ የዘ-ህወሀት የኮሙኒኬሽን ሚኒስትር የነበረው የዘር ማጥፋት ጭራቅ ሆኖ ብቅ አለ፡፡ በረከት ስምኦን በተቃዋሚ መሪዎች እና በደጋፊዎቻቸው በኩል የዘር ማጥፋት ድርጊት የመፈጸም ዕቅድ እንዳለ ለቢቢሲ ጋዜጠኛ ለማርቲን ፕላውት ቃለ መጠይቅ በማድረግ እንዲህ ብሎ ነበር፡

ሌላው አማራጭ በተለያዩ የኢትዮጵያ ብሄረሰቦች መካከል የህጻናት ጨዋታ የሚመስል የሩዋንዳን ዓይነት የዘር ጭፍጨፋ የማድረግ ብቀላ ነበር፡፡ ስርዓት እና ሕግን ለሚጥሱ ሰዎች የሚፈቀድ ከሆነ እና መንግስት ዝም ብሎ እጆቹን አጣምሮ ለጉዳዩ ምንም ዓይነት ትኩረት ሳይሰጥ የሚመለከት ከሆነ የሕግ እና ስርዓት የማስከበር ኃላፊነቱን አልተወጣም ማለት ነው፡፡ እናም ማንም እየተነሳ ጉዳዩን በእራሱ እጅ ለማድረግ የሚሞክር ሁሉ በሕዝብ ላይ እንዳመጸ እና ይህም ሁኔታ ያለምንም ጥርጥር የኢትዮጵያን ሕዝብ ወደ ብጥብጥ የሚያስገባ ነገር ነው፡፡ ከዚህ የተለየው አስከፊው አማራጭ ደግሞ በቀጣዮቹ ቀናት እና ወራት ውስጥ በሚሊዮኖች፣ በአስር እና በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሊያልቁ እንደሚችሉ ሊታሰብ ይገባል“ ነበር ያለው፡፡ 

እ.ኤ.አ ህዳር 2005 ፕሮፌሰር ክሪስቶፈር ክላፓም እንዲህ በማለት ጽፈው ነበር፣ “የመንግስት ዋና አፈቀላጤ በሆነው በበረከት ስምኦን አማካይነት በኢህአዴግ መንግስት የደረሰውን መጠነ ሰፊ ጉዳት አጋንኖ ማቅረብ አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ የእርሱ ስሜታዊ እና በተከታታይነት ቆጥቋጭ የሆኑ ንግግሮቹ ከዚህም አልፎ እንደ ሩዋንዳ ዓይነት የዘር ማጥፋት ሊኖር ይችላል እያለ የማስፈራራቱ ሁኔታ ኢህአዴግ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ወይም ደግሞ ምክንያታዊ በሆነ የፖለቲካ ሂደት ለመሳተፍ ዝግጁ ያለመሆኑን ለተቃዋሚዎች እና ለውጭው ዓለም ለሁለቱም ግልጽ የሆነ መልዕክትን አስተላልፏል…“ ነበር ያሉት፡፡

አምባገነኑ መለስ ዜናዊ በበኩሉ ተቃዋሚዎችን በሚስጥር የደገፉ ትግሬዎች በትግራይ ሕዝቦች ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል እንደፈጸሙ አድርጎ ነበር ያሰበው፡፡

እ.ኤ.አ ሰኔ 2006 የኢትዮሜዲያ ድረ ገጽ አርታኢ የነበረው አብረሀ በላይ አሁን በህይወት የሌሉትን እና ታዋቂ ኢትዮጵያዊ ለነበሩት ለፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪኒን በተቃዋሚዎች ላይ በመለስ ዜናዊ ቀርቦባቸው ለነበረው የዘር ማጥፋት ወንጀል ክስ ጉዳይን በማስመልከት ቃለ መጠይቅ አድርጎላቸው ነበር፡፡

አብረሀ በላይ፡ ፕሮፌሰር ሌቪን ለእርስዎ አንድ ጥያቄ ለመጠየቅ እንደሚያውቁት ሁሉ ኢትዮጵያውያን የሆኑ የትግራያ ተወላጅ የሆኑ ሰዎች በቅንጅት አመራር ቦታ ላይ ይገኛሉ፡፡ ታዋቂ ምሁር እና የተውኔት ጸሐፊ የሆኑትን ዶ/ር ኃይሉ አርዓያን እንደሚያውቋቸው ተስፋ አድርጋለሁ፡፡ ስለሆነም ትግሬዎች ለቅንጅት ለምን እንደሚሰሩ እና ቅንጅትን ለምን እንደመረጡ መለስ ዜናዊን ጠይቀዋቸው ነበርን?

ፕሮፌሰር ሌቪን፡ አዎ፣ በእርግጥ፡፡ ቅንጅት ለምን ትግሬዎች በአመራርም ሆነ በአባልነት እንዳሉት እና ኗሪዎች ቅንጅት እነርሱን የሚያጠፋቸው ከሆነ በአዲስ አበባ የሚኖሩት የትግራይ ተወላጆች በአብዛኛው ድምጻቸውን ለቅንጅት ለምን እንደሰጡት እሱን ጠይቄው ነበር፡፡ ለምንድነው በዚህ የምትደነቀው? አለ፡፡ በናዚ ውስጥ አገልግሎት የሚሰጡ አይሁዶችም ነበሩ! አለኝ፡፡ ያንን ከልብ በሰማሁ ጊዜ ሆዴን አቅለሸለሸኝ፡፡

በሌላ አገላለጽ ለመለስ ቅንጅትን (ወይም ሌሎች ተቃዋሚ ቡድኖችን) በድፍረት የሚረዱት አብዛኞቹ ትግሬዎች እራሳቸው ትግሬነታቸውን የሚጠሉ እና በድብቅ የእነርሱ ወገኖች የሆኑትን ትግሬ ጓደኞቻቸውን ለማጥፋት የሚመኙ ናቸው ማለት ነው፡፡

እ.ኤ.አ ሀምሌ 4/2005 መለስ ዜናዊ ለቢቢሲ የሀርድ ቶክ ለስቴፈን ሳኩር እንዲህ በማለት ቃለ መጠይቅ ሰጥቶ ነበር፡፡

ሳኩር፡ ሆኖም ግን አንተ እንደነገርከኝ ነገሮች ሁሉ ወደ መጥፎ ሁኔታ የሚጓዙ ከሆነ ሀገሪቱ እንደ ሩዋንዳ ሁሉ ወደ ስርዓተ አልበኝነት ልትገባ ትችላለች ብለሀል፡፡ ያንን ለእኔ ነግረኸኛል፡፡ ያ ማለት ግን ወደፊት ሀገሪቱ የተረጋጋ እና በእራስ ላይ መተማመን ባለው መልኩ ለመምራት መሰረት ጥለሀል የሚል ሀሳብን ይሰጣልን?

መለስ፡ ከችግር ውጭ አይደለንም፡፡ ከዚያ ለመውጣት ጥረት በማድረግ ላይ እንገኛለን፡፡ ጥቂት መሻሻሎችን አድርገናል፡፡ ሆኖም ግን እስከ አሁንም ድረስ ከችግር ውጭ አይደለንም፡፡ ማንም የአፍሪካ ሀገር ደቡብ አፍሪካን ጨምሮ ፍጹም በሆነ መልኩ ከአደጋ ነጻ ሊሆኑበት  የሚችሉበት ሁኔታ እንደሌለ አምናለሁ፡፡

በሌላ አባባል የዘር ማጥፋት ጭራቅ በአፍሪካ ውስጥ ከእያንዳንዱ ቋጥኝ እና ከእያንዳንዱ ዛፍ ስር ያንዣብባል፡፡ እንደ ዘ-ህወሀት ከሆነ በአሁኑ ጊዜ የዘር ማጥፋት ጭራቅ በኢትዮጵያ ላይ ምድር ደርሷል፡፡

መለስ ዜናዊ እ.ኤ.አ ህዳር 2005 የተቃዋሚ መሪዎችን በቁጥጥር ስር እንዴት እንዳዋለ እና እንዴት አድርጎ በሀሰት እንዳቀነባበረው እና በሸፍጥ የዘር ማጥፋት እና የሀገር ክህደት ወንጀል ክስ እንደመሰረተባቸው እራሱን ሀቀኛ በማስመሰል ብልጣብልጥነትን አሳይቷል፡፡

የአፍሪካ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት እና ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴዎች የአፍሪካ ንኡስ ኮሚቴ ሊቀመንበር የሆኑት የምክር ቤት አባል ክርስቶፈር ስሚዝ እ.ኤ.አ መጋቢት 28/2006 (ኤች አር 4423 “የ2005 የኢትዮጵያ ማጠናከሪያ ድንጋጌ“ የምስክርነት ቃላቸውን በሚሰጡበት ጊዜ ከመለስ ዜናዊ ጋር አድርገውት የነበረውን ውይይት በመግቢያው ንግግራቸው ላይ እንዲህ በማለት አቅርበው ነበር፡

ባለፈው ነሀሴ [እ.ኤ.አ 2005] አዲስ አበባን በጎበኘሁበት ጊዜ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር ተገናኝቸ እንደነበር እና በሰኔ ተደርጎ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ በእራሱ የመንግስት ወኪሎች በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ ጥይት እየተተኮሰ ላላቁት ዜጎች ለምን የማጣራት ስራ አልተሰራም ብዬ ጠይቄው ነበር፡፡ እርሱ የሰጠው ምላሽ ግን ምርመራው የተቃዋሚ መሪዎችን በቁጥጥር ስር ማዋል አስፈላጊ ስለሆነ እናም የማሟያ ምርጫዎች ገና በዕቅድ ላይ ስላሉ ያንን ነገር አሁን ማድረግ እንዳልፈለገ ነግሮኛል፡፡ በሁሉም የተቃዋሚ መሪዎች ላይ ከበቂ በላይ የማስረጃ ዶሴዎች ስላሉኝ በፈለግሁት ጊዜ የሀገር ክህደት ወንጀል በማለት በቁጥጥር ስር ለማዋል እንደሚችል ነግሮኛል፡፡ ስለሆነም ሁሉም ከምርጫ ማሟያው በፊት በቁጥጥር ስር ውለው መታሰራቸው የማይቀር እንደሆነ ነግሮኛል“ ነበር ያሉት፡፡

እ.ኤ.አ ጥቅምት 2007 የምክር ቤት አባል ስሚዝ ከመለስ ጋር አድርገውት የነበረውን ውይይት ለናሽናል ፕሬስ ክለብ እንዲህ በማለት ንግግር አድርገው ነበር፡

እኔም እራሴ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር ረዥም ጊዜ የፈጀ ስብስሰባ አድርጌ ነበር፡፡ የዴሞክራሲ አቀንቃኝ ሰላማዊ ሰልፍኞች የተገደሉበት ሁኔታ እንዲጣራ እና ጥፋቱን የፈጸሙ ሰዎች እና አካሎች ተጠያቂ እንዲሆኑ እና በቁጥጥር ስር የዋሉ ሁሉም የፖለቲካ እስረኞችም እንዲለቀቁ የተማጽዕኖ ጥያቄዬን አቅርቤለት ነበር፡፡ ስለፍትሀዊነት ጉድለት በተለይም በቅርቡ ስለሚደረገው ሀገር አቀፍ ምርጫ በእርሱ ወኪሎች በተቃዋሚዎች ላይ ስለሚደረጉት የማስፈራራት ስልቶች የነበረኝን ስጋት አንስቸለት ነበር…በመጨረሻም ከተቃዋሚዎች ጋር በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ እና ለእነርሱም ክብር እንዲያሳዩ እና ኢትዮጵያ ተጋፍጠውባት ስላሉት ችግሮች የተለያዩ ሀሳቦች ካላቸው ሰዎች እና አካሎች ጋር መቻቻል እንዲኖር ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄ ባቀረብኩለት ጊዜ እንዲህ ነበር ያለው፣ “ሁሉም በሀገር መክዳት እና በዘር ማጥፋት ወንጀል ጭምር ጥፋተኞች ናቸው፡፡ በሁሉም ዘንድ የማስረጃ ፋይሎች አሉኝ“ ነበር ያለው፡፡

እ.ኤ.አ ህዳር 2005 መለስ ዜናዊ 76 የተቃዋሚ ፖለቲከኞችን፣ ጋዜጠኞችን እና የሲቪል ማህበረሰብ ወትዋቾችን የሀገር ክህደት እና የዘር ማጥፋት ወንጀሎችን ፈጽማችኋል እንደዚሁም ሁሉ ሕገመንግስታዊ ስርዓቱን በኃይል ለመናድ ወይም ደግሞ በሕገ ወጥ መልክ ለማስወገድ አሲራችኋል፡፡ በዚህም መሰረት ስርዓተ አልበኝነት እንዲነግስ ተንቀሳቅሳችኋል በሚል የሸፍጥ ክስ መሰረተባቸው፡፡ ሌሎች 55 ተከላካዮች 35ቱ በሌሉበት እንደዚሁም ሁሉ በዩናይትድ ስቴትስ የሚገኙትን አምስት የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት ዘጋቢዎችን ጨምሮ እና ሌሎችን ለአዲስ አበባ ከተማ ምከር ቤት ተመርጠው የነበሩትን አባላት እና የጋዜጣ አሳታሚዎች በተመሳሳይ ወንጀል ክስ መሰረተባቸው፡፡

መለስ በቪኦኤ ላይ እንዲህ የሚል ክስ መሰረተ፡

“ከበርካታ አቅጣጫ ለበርካታ ዓመታት እንዳየነው የቪኦኤ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት እንደ ሩዋንዳው ሬዲዮ ሚሌ ኮሊንስ ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ ዝቅተኛውን የጋዜጠኝነት መስፈርትን በማያሟላ መልኩ አፍራሽ በሆነ ፕሮፓጋንዳ ተጠምዶ ይገኛል“ ነበር ያለው፡፡

የዘ-ህወሀት የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ አንቀጽ 269 የዘር ማጥፋት ወንጀል ተፈጽሟል ለማለት ሶስት ነገሮች መሟላት እንዳለባቸው በማያሻማ መልኩ በግልጽ ያስቀምጣል፡፡ እነርሱም፡

ሀ) መግደል፣ በሰውነት ላይ ጉዳት ማድረስ ወይም ደግሞ ከፍተኛ የሆነ አካላዊ ጉዳት ማድረስ ወይም ደግሞ በቡድን አባላት ላይ የስነ ልቦና ጉዳት ማድረስ፣ በማንኛውም መንገድ ወይም ደግሞ ምንም ይሁን ምን ሰውሮ ማጥፋት፣

ለ) በአባላት ወይም ደግሞ በልጆቻቸው ላይ ዘለቄታዊ በሆነ መልኩ መኖር እንዳይችሉ ተከታታነት ያለው ቅስቀሳ ማድረግ እና ይህንን መከላከል ያለመቻል፣ ወይም ደግሞ፣

ሐ) በግዴታ ማፈናቀል ወይም ደግሞ ሰዎችን ወይም ልጆቻቸውን ከቦታዎቻቸው ለሞት በሚያበቃ መልኩ ተገቢ ያልሆኑ ተግባራትን መፈጸም ወይም መሰወር፣ ወይም ደግሞ ሆን ተብሎ በጅምላ ወይም በከፊል ብሄርን፣ ብሄረሰብን፣ ጎሳን፣ ዘርን፣ ዜግነትን፣ ቀለምን፣ ኃማኖትን ወይም ደግሞ የፖለቲካ ቡድንን ማጥፋት፡፡

እ.ኤ.አ በ2005 ተካሄደ የተባለውን የይስሙላ የቅርጫ ምርጫ ውዝግብ ተከትሎ እ.ኤ.አ በ2006 “ዋና የፖሊስ ኃላፊዎች፣ አቀብያነ ሕጎች እና ዳኞች በፖሊስ መንግስት“ በሚል ርዕስ በተቃዋሚዎች እና በሌሎች መሪዎች ላይ በሸፍጥ ተመስርቶ በመካሄድ ላይ ስለነበረው የውሸት የዘር ማጥፋት ወንጀል ክስ የሚሞግት ባለ32 ገጽ ትችት አቅርቤ ነበር፡፡

አሁን እየተካሄደ ካለው የውሸት የዘ–ህወሀት የዘር ማጥፋት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ አንጻር አንድ እውነታ ለአንባቢዎች ግልጽ ለማድረግ የምፈልገው ነገር በዘ-ህወሀት የይስሙላው የዝንጀሮ ፍርድ ቤት በተከላካዮች ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል ይፈጸም እንደነበር ማረጋገጫ ነው፡፡ የዘ-ህወሀት ዓቃቤ ሕግ የነበረው ሽመልስ ከማል የእርሱን የዘር ማጥፋት ወንጀል በማስረጃ ለማረጋገጥ እንዲህ የሚል ንግግር አድርጎ ነበር፡

በአንድ በትግራይ ተወላጅ በሆነ ሰው ላይ ድብደባ በመፈጸም የአካል ጉዳት ማድረስ…ቤት ማቃጠል እና የሁለት የትግራያ ተወላጆችን ንብረት መዝረፍ…ፍርሀት እና ጉዳት ሊያስከትሉ የሚችሉ ድርጊቶችን መፈጸም፣ የጎሳ ማንነታቸውን መሰረት ባደረገ መልኩ በአንድ የጎሳ አባላት ላይ የስነ ልቦና ጉዳት ማድረስ፣ በቀጥታ ወይም ቀጥተኛ ባልሆነ መልኩ ከማህበራዊ ኑሮ በማገድ እና በቀብር ስነስርዓት ላይ እንዳይገኙ በኢህአዴግ አባላት እና ደጋፊዎች ላይ ክልከላ ማድረግ“ የሚሉ ነበሩ፡፡

(ለተሟላ መረጃ እና አሳማኝ ለሆነ ውሱን ዘገባ ከዘር ማጥፋት ወንጀል የዝንጀሮው ፍርድ ቤት የህግ ሂደት ጋር በተያያዘ መልኩ አምነስቲ ኢንተርናሽናል እ.ኤ.አ በ2011 ያወጣውን “የተቃዋሚ መሪዎች፣ጋዜጠኞች እና የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተከላካዮች የፍትህ ሂደት በእሳት ላይ“ በሚል ርዕስ የቀረበውን ዘገባ ይመልከቱ፡፡)

እ.ኤ.አ መጋቢት 2005 መለስ የዘር ማጥፋት ወንጀል ክስ ከመሰረተ ከአምስት ወራት በኋላ ከማል ፍርድ ቤቱ የዘር ማጥፋት ወንጀል ሙከራ ለማድረግ በሚል እንዲያስተካክለው ፍርድ ቤቱን አዘዘ፡፡ በዚያን ጊዜ ከማል እና ዘ-ህወሀት ዓለም አቀፍ ደረጃውን ከጠበቀ የዘር ማጥፋት ወንጀል ጋር እንደማይገናኝ እና ሁለቱም ምንም ዓይነት የዘር ማጥፋት ወንጀል መሰረታዊ ምንነት ምን እንደሆነ የማያወውቁ በመሆናቸው በዓለም አቀፍ የሕግ እና የሰብአዊ መብት ተመጓቾች ዘንድ መሳቂያ እና መሳለቂያ ሆነው ነበር የከረሙት፡፡

ሆኖም ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ስለተደረገው የዘር ማጥፋት ወንጀል ዘ-ህወሀት ብቸኛው ተጠያቂ ነው፡፡

እ.ኤ.አ ጥር 2004 ጀኖሳይድ ዎች የተባለ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት “እ.ኤ.አ ታህሳስ 2003 በኢትዮጵያ በጋምቤላ እና በአካባቢው የአኟክ ህዝቦች ላይ የተፈጸመ የዘር ማጥፋት ወንጀል“  በሚል ርዕስ ዘገባ አዘጋጅቶ ነበር፡፡

እ.ኤ.አ ታህሳስ 2006 መለስ ዜናዊ ሶማሌን በመውረር ለመናገር በሚያስቸግር መልኩ በሶማሌ ሕዝቦች ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀል ፈጸመ፡፡ የመለስ/ዘ-ህወሀት በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሟቸው ወንጀሎች እና በሶማሌ ሕዝቦች ላይ የፈጸሟቸው የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ሂዩማን ራይትስ ዎች በተባለው የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት “የአእምሮ መቃወስ፡ በሞቃዲሾ የሰቪል ሰዎች መሰወር“ በሚል ርዕስ ዘገባ አቅርቦ ነበር፡፡

እ.ኤ.አ ሰኔ 2008 ሂዩማን ራይትስ ዎች የተባለው ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ዘ-ህወሀት በኢትዮጵያ የሶማሌ ክልላዊ መንግስት ውስጥ የፈጸመውን የዘር ማጥፋት ወንጀል ዘግቦ ነበር፡፡ ሂራዎ እንዲህ በማለት ነበር የዘገበው፣ “እ.ኤ.አ በ2008 የመጀመሪያ አካባቢ የኢትዮጵያ ወታደራዊ ዘመቻዎች መንደሮችን የማዛወር እና የማውደም ድርጊቱ እ.ኤ.አ በ2007 አጋማሽ በጣም ከፍተኛ ከነበረበት ሁኔታ ጋር ሲነጻጸር ቀንሶ ይታይ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ሌሎች የሰብአዊ መብት ረገጣዎች ማለትም በዘፈቀደ በቁጥጥር ስር የማዋል፣ በእስር ቤቶች ውስጥ ማሰቃየት፣ ተገቢ ያልሆነ የእስር አያየዝ መካሄዱ ቀጥሎ ነበር“ ነው ያለው፡፡

እ.ኤ.አ በ2012 ሂዩማን ራይትስ ዎች የተባለው ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት “ሞትን መጠበቅ፣ በኃይል ማፈናቀል እና የመንደር ምስረታ በኢትዮጵያ ጋምቤላ ክልል“ በሚል ርዕስ ዘገባ አቅርቦ ነበር፡፡

እንደዘገባው ከሆነ የኢትዮጵያ መንግስት እ.ኤ.አ በ2013 1.5 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎችን በአራት ክልሎች ለማስፈር ዕቅድ አወጣ፡ ጋምቤላ፣ አፋር፣ ሶማሊ እና ቤንሻንጉል ጉሙዝ፡፡ ሂደቱ በጋምቤላ የበለጠ ተጠናክሮ ነበር፡፡ የማስፈር ሂደቱ ተጀምሮ የነበረው እ.ኤ.አ በ2010 ነበር፡፡ እናም በግምት ወደ 70 ሺ ሰፋሪዎች እ.ኤ.አ በ2011 መጨረሻ አካባቢ እንዲንቀሳቀሱ ተደርጎ ነበር፡፡ ያም ጎሳን በማጽዳት የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው፡፡

እ.ኤ.አ ታህሳስ 2012 ጀኖሳይድ ዎች የተባለው ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ዘ-ህወሀት መሬታቸውን ለውጭ እና ለሀገር ውስጥ ኢንቨስተሮች ለማከራየት በማሰብ  70 ሺ ሰዎችን ከመሬታቸው በግዴታ አፈናቅሏል፡፡

እ.ኤ.አ ነሀሴ 3/2016 ቢቢሲ እንዲህ የሚል ዘገባ አውጥቶ ነበር፣ “ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ማክሰኞ ዕለት በጎረቤት ሀገሮች እንደሚታየው ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ ወደ ጎሳ ግጭት እያመራች ነው በማለት አስጠንቅቋል“ ብሎ ነበር፡፡

በአሁኑ ጊዜ የዘር ማጥፋት ወንጀል የመረጃ ማወናበድ ለምን አስፈለገ?

የዘ-ህወሀት የዘር ማጥፋት የመረጃ ማወናበድ ዘመቻ በአሁኑ ጊዜ በርካታ ዓላማዎች አሉት፡፡

የመጀመሪያው የዘር ማጥፋት የመረጃ የማወናበድ ዘመቻ ዓላማ በሀገሪቱ ውስጥ ያለውን መጠነ ሰፊ ሕዝባዊ ተቃውሞ በሻቢያ እና በስም የለሽ የውጭ ኃይሎች ምናልባትም በመካከለኛው ምስራቅ ባሉ ሀገሮች መንግስታት እና የግል ፍላጎቶች ትዕዛዝ እና ቁጥጥር እንዳለ አድርጎ አሳንሶ እና አኮስሶ ለማሳየት የሚል ነው፡፡

በተከታታይ የውጭ ኃይሎች ለሕዝባዊ አመጹ ምክንያቶች ናቸው እያለ በመጥራት ዘ-ህወሀት መጠነ ሰፊውን ሕዝባዊ አመጽ እና በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉትን ወጣቶች ሚና አሳንሶ እና አኮስሶ ይመለከታል፡፡

እነዚህ የውሸት መረጃን የሚያቀርቡ የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻዎች የሚከተሉትን ነገሮች ተግባራዊ ለማድረግ ዓላማ አላቸው፡

1ኛ) ሁሉም ኢትዮጵያውያን በዘ-ህወሀት አገዛዝ ደስተኞች ናቸው፣ ሆኖም ግን በውጭ ኃይሎች በሚደረግ ቅስቀሳ ነው ችግር እየተፈጠረ ያለው እንዲባል ይፈልጋሉ፡፡

2ኛ) ይህ ተቃውሞ፣ አመጽ እና መገዳደር ሀገር በቀል ለመሆኑ ሊታሰብ የሚችል ነገር አይደለም ምክንያቱም፡

ሀ) ኢትዮጵያውያን በእራሳቸው አነሳሽነት ተነሳስተው ለመገዳደር አይችሉም ምክንያቱም ፈሪዎች ናቸው፡፡

ለ) ኢትዮጵያውያን የጭቆናቸው መንስኤ ዘ-ህወሀት መሆኑን ለመለየት የማይችሉ ደደቦች እና በእርሱም ላይ ለማመጽ ወኔው የሌላቸው ህዝቦች ናቸው፡፡

ሁለተኛው የዘር ማጥፋት የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ዓላማ በሀገሪቱ ውስጥ በደም የመታጠብ እልቂት እና ወድመት የሚከሰት ለመሆኑን ችግሩ በማዕዘን ላይ ቆሞ የሚገኝ መሆኑን ኢትዮጵያውያን ሁሉ አምነው እንዲቀበሉ እና እንዲፈሩ ለማድረግ ነው፡፡

በተለይ ወደ ትግራይ ህዝብ ፊታቸውን በማዞር ዘ-ህወሀት ከሌለ እና ለእነርሱ የሚከላከልላቸው ከሌለ በአሮሞዎች እና በአማሮች የተባበረ ኃይል እንደሚገደሉ እና የዘር ማጥፋት እልቂት ሊፈጸምባቸው እንደሚችል ለማሳመን ይፈልጋሉ፡፡ የዘ-ህወሀት ጀኔራል የሆነው ሳሞራ የኑስ በአንድ ወቅት እንዲህ ብሎ ነበር፣ “ህወሀት ማለት የትግራይ ሕዝብ ማለት ነው እንደዚሁም ሁሉ የትግራይ ሕዝብ ማለት ህወሀት ማለት ነው“ ነበር ያለው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የተበሳጨውን ጭራቅ ደግመው እና ደጋግመው በማሳየት ዘ-ህወሀት በስልጣን ላይ ካልተቀመጠ እንደ ሩዋንዳ ዓይነት ጭፍጨፋ እንደሚከሰት እና ሀገሪቱ ደም በደም በመሆን ከፍተኛ የሆነ የዘር ማጥፋት ድርጊት ሊፈጸም እንደሚችል ሕዝቡን ያስፈራራሉ፡፡

ሶስተኛው የዘር ማጥፋት የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ዓላማ የትግራይ ሕዝብ ሰላሙ እና ደህንነቱ የተጠበቀ መሆኑን በማረጋገጥ ለሕዝቡ ለማሳየት ነው፡፡ ምክንያቱም ኃይለኞቹ የህወሀት የደህንነት እና ወታደራዊ ኃይሎች የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመፈጸም ዕቅድ የሚይዙትን ኃይሎች ሁሉ መደምሰስ እንደሚችሉ በተለይ አሁን ተቀጣጥሎ የነበረውን ሕዝባዊ አመጽ እና ተግዳሮት በማኮላሸት በተግባር በማሳየት የትግራይ ሕዝብ በእነርሱ ላይ እምነት እንዲኖረው ማድረግ ነው፡፡

አራተኛው የዘር ማጥፋት የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ዓላማ ኢትዮጵያውያንን እና በተለይም ለጋሽ እና አበዳሪ ድርጅቶችን እና ዓለም አቀፍ የድህነት አቃጣሪዎችን ዘ-ህወሀት ከሌለ ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር ልትኖር አትችልም በማለት ለማሳመን ነው፡፡ ይህንን ውሸት በመደጋገም የዘ-ህወሀት መሪዎች በኢትዮጵያ ውስጥ እና በውጭ ያሉትን ደጋፊዎቻቸውን ለማሳመን እና የተለመደውን በሙስና የመዘፈቅ ተግባራቸውን እና የሰብአዊ መብት መርገጣቸውን አጠናክረው ለመቀጠል ያስባሉ፡፡

አምስተኛው የዘር ማጥፋት የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ዓላማ እንደ ቤንሻንጉል፣ አኙአክ፣ ሶማሊ፣ አፋር እና ሌሎች ትናንሽ የጎሳ ቡድኖች ዘ-ህወሀት በምዕናባዊ ሀሳቡ የፈጠረውን የኦሮሞ-አማራ ኢንተርሃምዌ የዘር ማጥፋት የምጽዓት ቀንን ለመቋቋም ከዘ-ህወሀት ጋር ህብረት እንዲፈጥሩ ለማድረግ እና አዲስ የመረጃ የማወናበጃ መሰረት ለመጣል ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን በየዕለቱ በዘ-ህወሀት ማለቂያ እና መቋጫ በሌለው የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ቦምብ እየተደበደቡ ያሉበትን እውነታ በሚገባ ማወቅ አለባቸው፡፡

ለምሳሌ ያህልም ከጥቂት ቀናት በፊት “አዲስ ፎርቹን” እየተባለ በሚጠራ መጽሄት የግንኙነት መስመር ክፍሉ በኩል የማወናበጃ መረጃውን ለቋል፡፡ ከውስጥ የዘ-ህወሀት ምንጮች የተገኘ መረጃ መሆኑን በመጥቀስ አዲስ ፎርቹን “የኃይል ሚዛን ወደ አብዮታዊ ዴሞክራቶች አዘንብሏል“ በማለት አውጇል፡፡

አዲስ ፎርቹን በዘ-ህወሀት ውስጥ ያለውን ትግል እና ጽንፈኛ ኃይሎች እንዴት አድርገው በፖለቲካ ክርክራቸው ማሸነፍ እንደሚችሉ ለማመላከት የስነ ልቦና የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ፕሮፓጋንዳ ለመልቀቅ ነው፡፡

አዲስ ፎርቹን እንዲህ የሚል ትንበያ ሰጥቷል፣ “በኢህአዴግ ጥምረት እና የስራ አስፈጻሚ አባላት ውስጥ እና በእያንዳንዱ ፓርቲ የፖለቲካ ቢሮ ውስጥ ሊቀር የማይችል ከስልጣን ዝቅ የማድረግ እና የማባረር እርምጃ ይኖራል“ በማለት የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻውን አጧጡፎ ይገኛል፡፡ አዲስ ፎርቹን የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ዋና መሰረቱ የሚከተለው መሆኑን ግልጽ አድርጓል፡

“የኢህአዴግ ሊቀመንበር ኃይለማርያም ደሳለኝ የበለጠ በቴክኒካዊ ዕውቀት የተካኑ ሰራተኞች ያሉበት፣ ባለፉት ሁለት ተኩል አስርት ዓመታት ውስጥ በፓርቲው ውስጥ ተደርጎ የማያውቅ የፓርቲው አባላት ያልሆኑ ሰራተኞች በካቢኔው እንዲገቡ በማድረግ አዲስ አስተዳደር ለማዋቀር የእራሱን መንገድ በመስራት ላይ ነው፡፡ አሁን ካለው ምክር ቤት ስብስባ ጠንካራ ሆኖ የሚወጣ ካለ እሱም ኃይለማርያም ነው፡፡ ቢያንስ በንግግርም ቢሆን እራሱን ግልጽ አድርጓል፡፡ እናም እራሱን ከፍ ባለ ቦታ ላይ አስቀምጧል“ የሚል የውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻ ነው፡፡

የአዲስ ፎርቹን የውሸት የማወናበጃ መረጃ በእርግጥ የሚመራው በዘ-ህወሀት ማዕከላዊ ትዕዛዝ ነው፡፡ የውጭ አበዳሪዎች እና ለጋሽ ድርጅቶች እንዲሁም ዓለም አቀፍ የድህነት አቃጣሪዎች ምን ምላሽ እንደሚሰጡ አስቀድሞ ለማወቅ ዘ-ህወሀት የመንሳፈፊያ የሙከራ ባሉን ወደ አየር ላይ ይለቃል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ወደፊት ታላቅ ለውጦች ይመጣሉ እናም ለዚያ ለውጥ መምጣት ዋናው አንቀሳቃሽ ኃይለማርያም እንደሆነ ተደርጎ እንዲያምን ለማድረግ በውሸት የመረጃ የማወናበጃ ዘመቻን ዓላማ በማድረግ ለማታለል እና ሕዝባዊ ትግሉ እንዲረግብ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡

ሆኖም ግን ማንም እንደሚያውቀው ኃይለማርያም በእራሱ ምንም ማድረግ የማይችል አሻንጉሊት እንደሆነ ማንም ያውቃል፡፡ እንደዚህም ሆኖ ዘ-ህወሀት በውስጣዊ የኃይል የበላይነት ትግል ሽኩቻው እሱን እንደገና በመፍጠር እና የኢትዮጵያ አዳኝ አድርጎ ለማቅረብ ይሞክራል፡፡

እውነታው ፍርጥርጥ ተደርጎ ሲታይ ግን እንደ መለስ ሁሉ በኃይለማርያም፣ በዘ-ህወሀት መሪዎች እና በበታቾቻው እጅ ብዙ ደም ያለ የመሆኑ ጉዳይ ነው፡፡

በወፍ እና በድንቢጥ መካከል ምንም ዓይነት ልዩነት የለም፡፡ እንደዚሁም ሁሉ እጃቸውን በደም በታጠቡት የዘ-ህወሀት መሪዎች፣ የበታቾቻቸው እና በኃይለማርያም መካከል ምንም ዓይነት ልዩነት የለም፡፡

እውነታው ፍርጥርጥ ተደርጎ ሲታይ፣

የዘ-ህወሀት መሪዎች በእርግጥ የእነርሱ ከስልጣን መወገድ በሩዋንዳ እንደታየው ሁሉ ኢትዮጵያ ወደ ዘር ማጥፋት ግጭት ትገባለች በማለት እያሳዩ ያሉት እምነት የሚያስገርም ጉዳይ ነው፡፡ እራሳቸውን ከምንም በላይ በመውደድ የሚያደርጉት ኢምክንያታዊ ድርጊት ነው ወይም ደግሞ ከመጠን በላይ በፍርሀት ቆፈን ተውጠው በስልጣን ኮርቻ ላይ ተጣብቀው ለመቆየት የዘር ማጥፋት ድርጊትን ለመፈጸም ተዘጋጅተዋል፡፡

በታሪክ ማንኛውም አምባገነናዊ አገዛዝ ከስልጣን ከተወገደ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ ያለ እና ሁሉም ነገር ጨለማ ሆኖ ይታየዋል፡፡

ንጉሠ ነገሥት አጼ ኃይለ ሥላሴ ከሞቱ ኢትዮጵያ የምትጠፋ የሚመስላቸው ሰዎች ነበሩ፡፡

መንግስቱ ኃይለማርያም ያለእርሱ ማካላዊ አመራር ኢትዮጵያ እንደምትበታተን አድርጎ በስልጣኑ ይጠቀም ነበር፡፡

መንግስቱ ከኤርትራ አማጺዎች ጋር 100 ዓመታትም ያህል ቢሆን እዋጋለሁ ብሎ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ነገሮች ሁሉ ገፍተው በመጡበት በመጨረሻው ጊዜ አሁን ወደሚኖርበት ወደ ዝምባብዌ አውሮፕላኑን በማዞር ነበር የሸሸው፡፡

የመለስ ዘ-ህወሀት እንደ መንግስቱ ደርግ ሁሉ የመከራውን ደወል በሚሰሙበት ጊዜ የመጀመሪያውን የአውሮፕላን በረራ ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ በማዞር ወደ ቪርጂኒያ፣ ሚያሚ፣ ዴንቨር እና ሌሎች የአሜሪካ ሀገር ቦታዎች ሁሉ መፈርጠጣቸው የማይቀር ሐቅ ነው፡፡

ሆኖም ግን በዛሬው በ21ኛው ክፍለ ዘመን የሰውን ልጅ ክቡር ህይወት ያለምንም የሕግ ተጠያቂነት እና በማንአለብኝነት ሲቀጥፉ እና ሲያስቀጥፉ ኖረው፣ የሀገርን ድንበር እንደ ድፎ ዳቦ እየቆረሱ እና እየሸነሸኑ ለባዕድ ሲሰጡ እና ለሙን መሬት ከኢትዮጵያውያን ዜጎች እየነጠቁ በርካሽ ዶላር ለባዕድ ሲቸረችሩ ከርመው፣ የወደብ ባለቤት የነበረችውን ታላቅ ሀገር ወደብ አልባ አድርገው እና የወደብ ኪራይ ቀፍቃፊ እንድትሆን አድርገው ከኖሩ በኋላ፣ ኢኮኖሚውን በጅምላ ተቆጣጥረው ዜጎችን በችጋር አለንጋ ሲያሰቃዩ ከከረሙ በኋላ፣ ሀገሪቱን በጎሳ በመሸንሸን ዜጎች ከታጠረላቸው የክልል በረት በስተቀር ከስርዓቱ ተጠቃሚ ጆሮ ጠቢ ጀሌዎች በስተቀር የትም ሄደው መስራት እንዳይችሉ ተቀፍድደው ተይዘዉ እንዲኖሩ ከተደረገ በኋላ።

ዜጎች በማናቸውም ጊዜ በክረምቱ ወቅት ሳይቀር ቤቶቻቸው በላያቸው ላይ እየፈረሰ ለሊዝ ጨረታ ለብር ማግበስባሻ ወደ ሜዳ እየተጣሉ ባሉበት ሁኔታ፣ የሀገሪቱ የነጻነት እና የድንበር ጠባቂ ሆኖ የኖረውን ጀግናውን የኢትዮጵያን የጦር ኃይል አፈራርሰው የሀገር እና የወገን ፍቅር በሌላቸው በእነርሱ ማይማን፣ ዘረኛ እና ዘራፊ ሙሰኛ ሰራዊት ሀገሪቱን ቁምስቅል እያሳዩ ከቆዩ በኋላ፣ እንዲሁም ላለፉት 25 ዓመታታ ዜጎች በጎሳ፣ በዘር፣ በኃይማኖት፣ በፖለቲካ እየተለያዩ በጎሪጥ አንዲተያዩ እና እንዲናቆሩ ሲደረግ ቆይቶ በሀገሪቱ ውስጥ ፍቅር ጠፍቶ ጥላቻ እና የበቀል ሰይጣኖች ዳብረው እና ፋፍተው ባለቡት ደረጃ ዛሬ  የዓለም የዴሞክራሴ ጠበቃ ነኝ በምትለው ወደ አሜሪካ ሀገር ሸሽቶ መደበቅ ይቅር እና ወዳጆቻችን ናቸው ወደሚሏቸው የሰብአዊ መብት እና የዴሞክራሲ ደፍጣጭ አምባገነኖች ወደእነ ካጋሜ፣ አልባሽር እና ኡሁሩ ኬንያታ ሀገር እና ወደ ቻይናም የዘረፉትን ይዞ ፈርጥጦ ለመኖር የማይቻልበት ዘመን ላይ የተደረሰ መሆኑን የወያኔ መሪዎች እና ግብረ አበር አጫፋሪዎቻቸው በውል ሊገነዘቡት ይገባል፡፡

በነገራችን ላይ በአሁኑ ጊዜ የዘ-ህወሀት መሪዎችና ግበረ አበሮቻቸው “የደጀ ሰላሙ ደወል የሚጮኸው ለማን ነው?” በማለት እራሳቸውን በመጠየቅ ላይ ይገኛሉ፡፡ 

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!  

መስከረም 10 ቀን 2009 ዓ.ም