ጥላቻ ጥላቻን፣ ኃይል ኃይልን፣ ሕግ አልባነት ስርዓተ አልበኝነትን ይወልዳል፣

[For an English version of this post, click HERE.]

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም 

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

በዚህ ባለፈው ሳምንት አሜሪካውያን መንፈሳቸውን በሚፈታተን ክስተት ውስጥ ወድቀዋል፡፡ አሜሪካውያን አጅግ በጣም አዝነዋል፡፡ አሜሪካውያን በጥንቃቄ በማሰብ ስቃይ ውስጥ ተዘፍቀው ይገኛሉ፡፡

ሁለት አፍሪካ አሜሪካውያን ዜጎች በሁለት እምነተ ቢስ የፖሊስ ኃላፊዎች ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ መገደላቸውን ተመልክተናል፡፡ እምነተ ቢስ የፖሊስ ኃላፊዎች የሚለውን ሀረግ ላሰምርበት እፈልጋለሁ፡፡

በአንድ ብቸኛ ጥቃት ፈጻሚ እና የነጭ ፖሊስ ኃላፊዎችን መግደል እንደሚፈልግ በሚዝት ሰው አምስት የፖሊስ ኃላፊዎች ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ መገደላቸውን እና ሌሎች ሰባት ዜጎች ደግሞ መቁሰላቸውን ተመልክተናል፡፡ ብቸኛ ጥቃት ፈጻሚ በሚለው ሀረግ ላይ ላሰምርበት እፈልጋለሁ፡፡

ከ72 ሰዓታት ባነሰ ጊዜ ውስጥ የበርካታ ግለሰቦች፣ ቤተሰቦች እና ማህበረሰቦች ህይወት እና ተስፋ ለዘላለሙ እንዳይመለስ ሆኖ ጠፋ፡፡ እንደ ሀገር የዘመናት የሕግ የበላይነት ኩራታችን ከመቅጽበት ተሸርሽሮ አፈር ድሜ በላ፡፡ በህዝቦቻችን ደህንነት ተቋማት ላይ ያለን እምነት ተሸርሽሮ ጠፋ፡፡ ለሰው ልጆች ያለን ፍቅር፣ ክብር እና ስልጣኔ ተንኮታኩቶ ወደቀ፡፡

ፖለቲከኞች የተለመደውን የባዶ ጩኸት ንግግራቸውን ያሰሙ ነበር፡፡

ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በዳላስ ከተማ ሕግን በመጣስ በዜጎች ላይ የተፈጸመው ጭካኔ የተሞላበት፣ በስሌት የተቀነባበረ እና አረመኒያዊ ጥቃት እጅግ ያሳዘነው መሆኑን ተናግሯል፡፡ እንዲህ የሚል መልዕክት አስተላልፏል፣ “አሜሪካውያን በባንቶን ሮግ በአልቶን ስተርሊንግ፣ በሉሲኒያ እና በፋልኮን ሄይትስ በፊላንዶ ካስል በሚኒሶታ በተፈጸሙት አሰቃቂ ግድያዎች ጥልቅ የሆነ ችግር ደርሶባቸዋል፡፡ እንደዚህ ያሉ አሰቃቂ የሆኑ አደጋዎችን ለበርካታ ጊዚያት ተመልክተናል፣ እናም የዚህ አሰቃቂ የእልቂት አደጋ ሰለባ ለሆኑት ቤተሰቦች እና ማህበረሰቦች ልባችን በሀዘን ተነክቷል“ ብሏል፡፡

ሂላሪ ክለሊንተን “በዳላስ በፖሊስ የተፈጸሙት ግድያዎች ፍጹም የሆኑ አረመኒያዊ ድርጊቶች ነበሩ፣ እንደዚሁም ሁሉ በሉሲያኒያ በአልቶን ስተርሊንግ እና በሚኔሶታ በፊላንዶ ካስል በፖሊሶች ላይ የተፈጸሙት ግድያዎች እያንዳንዱን አሜሪካዊ ዜጋ ሊያሳስቡ ይገባል” ነበር ያለችው፡፡ እንዲህ የሚል የተማጽዕኖ ጥሪም አቅርባለች፣ “በፖሊስ በሚወሰዱ የኃይል እርምጃዎች በተለይም ግድያን በሚመለከት ሀገራዊ መመሪያ ማውጣት አለብን“ ብላለች፡፡

ዶናልድ ትራምፕ “በዳላስ በፖሊስ የተፈጸሙት ግድያዎች የሀገራችንን መንፈስ አናግተዋል” ነበር ያለው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ “በስልጡን እና ፍጹም በሆነው በስርዓተ አልበኝነት መካከል ያለውን ኃይል በማስታወስ ለሕግ ተፈጻሚነት አንድነታችንን ማጠናከር አለብን” ብሏል፡፡ ትራምፕ በቀጣይነትም እንደዚህ ነበር ያለው፣ “በሉሲኒያ በአልቶን ስተርሊንግ እና በሚኒሶታ በፊላንዶ ካስል የተፈጸሙ ግድያዎች እያንዳንዱ አሜሪካዊ ደህንነቱ ስለመጠበቁ ወደፊት ምን ያህል ስራ መስራት እንዳለብን የሚያመላክቱ ናቸው“  ነበር ያለው፡፡

የጥቁሮች ህይወት ያሳስበናል መስራች የሆኑት አሊሲያ ጋርዛ እንዲህ ብለው ነበር፣ “የጥቁሮች ህይወት ያሳስበናል ድርጅት ስለፖሊስ ግድያ አሳሳቢነት ጉዳይ ጥሪ ያላቀረበበት ጊዜ የለም፡፡ በአሁኑ ጊዜ በዚህ ሀገር የፖሊሳዊ ስራ ተጠያቂነት፣ ግልጽነት እና ኃላፊነትን የተላበሰ መሆን እንዳለበት ደግመን እና ደጋግመን ተናግረናል፡፡“

በአትላንታ የጥቁሮች ህይወት ያሳስበናል አስተባባሪ የሆኑት ሰር ማጆር ግልጽ በሆነ መልኩ የፖሊስን ግድያ እንዲህ በማለት እውግዘዋል፡፡ “የጥቁሮች ህይወት ያሳስበናል ድርጅት ሕገ ወጥ ግድያውን አሳንሶ አልተመለከተውም፡፡ ሆኖም ግን እውነተኛ መሆን አለብኝ፡ ይህ ለምን እንደተደረገ እገነዘባለሁ፡፡ ይህንን ነገር አላበረታታም፣ ጉዳዩን ቀላል አድርጌ አላየውም፡፡ ይህንን ማብራራት አልችልም፡፡ ሆኖም ግን ግንዛቤው አለኝ”  ነበር ያሉት፡፡

ሆኖም ግን እንደዚህ ያለውን ተመሳሳይ እና ተደጋጋሚ የአሜሪካውያን አሰቃቂ ተውኔት ሊገልጸው የሚችለው ምንድን ነው?

ለዚህ ጥያቄ መልስ ሊሆኑ የሚችሉ በጥብቅ የተሳሰሩ ሁለት መልሶች እንዳሉ አምናለሁ፡፡

የመጀመሪያው መልስ እ.ኤ.አ በ1928 በአሜሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት በጀስቲስ ሊዊስ ብራንዲስ እንዲህ በማለት ግልጽ በሆነ እና በማያሻማ መልኩ ተጽፎ ይገኛል፡

የሞራል ልዕልና፣ ደህንነት እና ነጻነት ሁሉም በአንድ ላይ የመንግስት ባለስልጣኖች ዜጎችን ለሚያዝዙ ሕጎች ሁሉ ተገዥ መሆን እንዳለባቸው ይጠይቃሉ፡፡ ሕግን በሚከተል መንግስት ውስጥ መንግስት ሕጉን በንቀት መልክ የሚያየው እና ለተፈጻሚነቱ ክትትል የማያደርግ ከሆነ የመንግስት ህልውና እራሱ ለአደጋ ይጋለጣል፡፡ የእኛ መንግስት ጠንካራ እና በየቦታው የሚገኝ መምህር ነው፡፡ ለመልካምም ሆነ ለመጥፎ ነገር እራሱን ምሳሌ በማድረግ ሁሉንም ህዝብ ያስተምራል፡፡ ወንጀል ተላላፊ በሽታ ነው፡፡መንግስት እራሱ ሕግን የሚጥስ ከሆነ ለሕግ ያለውን ንቀት ያመላክታል፣ እንደዚሁም ሁሉ እያንዳንዱ ሰው እንደ እርሱ ሁሉ ሕጉን እንዲጥስ አርዓያ ሆኖ ያሳያል፡፡ ስርዓተ አልበኝነትን ይጋብዛል፡፡ የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ አዋጅን ለማስተዳደር ዓላማው የአሰራር መንገዱን ይወስነዋል – መንግስት እራሱ የግል ወንጀለኛን ለመቅጣት ሲል እራሱ ወንጀሎችን የሚፈጽም ከሆነ የቅጣቱን ተፈጻሚነት አስቸጋሪ ያደርገዋል፡ (ኦልምስቲድ ዩናይትድ ቴትስ፣ 277 ዩኤስ (1928))

ሁለተኛው መልስ እንዲህ በሚሉት የዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግ ነብያዊ ቃላት ተጽፎ ይገኛል፡

ጥላቻ ጥላቻን ይወልዳል፣ ኃይል ኃይልን ይወልዳል፣ የጉልበት ኃይለኝነት የበለጠ የጉልበት ኃይለኝነትን ይወልዳል…የኃይል የመጨረሻው ደካማነት ለማጥፋት የሚፈልገውን ደጋግሞ ለማጥፋት በሚያደርገው ጥረት በቀልን በተደጋጋሚ እየፈለፈለ በመሄድ ሰይጣናዊነትን ከማጥፋት ይልቅ የበለጠ እያባዛው ይሄዳል፡፡ ኃይልን በመጠቀም ጥላቻ ያደረበትን ሰው መግደል ትችላለህ ሆኖም ግን ጥላቻን እራሱን መግደል አትችልም፡፡ በእርግጥ ኃይል ጥላቻን የበለጠ እንዲጨምር ያደርጋል…ኃይልን በኃይል መመለስ እንደገና የበለጠ ኃይልን ይወልዳል፣ ከዋክብት የሌሉበት ሰማይ የበለጠ ጥልቅ ጨለማን ይፈጥራል፡፡ ጨለማን ጨለማ በፍጹም አያስወግደውም፡፡ ይህንን ለማድረግ የሚችለውብርሀን ብቻ ነው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ጥላቻን ጥላቻ አያስወግደውም፡፡ ይህንን ማድረግ የሚችለው ፍቅር ብቻ ነው” ነበር ያሉት፡፡

ሆኖም ግን በአሁኑ ጊዜ እነዚህ መሬትን በማደን ላይ ያሉት ህሊና የለሾች፣ ስሜተቢሶች እና ትርጉመቢስ ኃይል ተጠቃሚ ፍጡሮች ምንጫቸው ምንድን ነው?

ፈላስፋው እና የሰላም አባቱ ዳይሳኩ ኢኬዳ ለዚህ ምላሽ ይሰጣሉ፡፡ ኃይል የአእምሮ በሽታ ነው በማለት እንዲህ የሚል መልስ አላቸው፡

ኃይል ከተቃጠለ እና በእብሪት እሳት ከቆሰለ መንፈስ፣ ከተከፋፈለ መንፈስ እና በኃይልየለሽነት እጦት ከተጠበሰ መንፈስ፣ የህይወት ትርጉም ማለት ምንጊዜም አሸናፊ ለመሆን ከተራበ እና ከተቃጠለ መንፈስ፣ የበታችነት ስሜትን ተላብሶ ከሚገኝ መንፈስ ይወለዳል፡፡ ራስን በማክበር ከተጎዳ መንፈስ፣ እና ከውርደት  ኃይል ይከተላል፡፡ ማንኛውንም ነገር ለመደምሰስ እና ሌሎችን በመደብደብ ለእራሱ ተገዥ ለማድረግ አብዛኛውን ጊዜ በህዝብ መገናኛ ዘዴዎች በመጠቀም የኃይልን መንፈስ በህብረተሰቡ ላይ ለማሰራጨት፣  የኃይል ባህል ለመፍጠር ደስተኛ ይሆናል…ከተፈወሰው እና ከሰላማዊው ልብ ውስጥ ስልጣኔ ይወለዳል፣ ከስልጣኔ ደግሞ ሌሎችን የማዳመጥ ፈቃደኝነት ይወለዳል፣ ሌሎችን ከማዳመጥ ፈቃደኝነት ደግሞ የጋራ መግባባት ይወለዳል፣  እንደዚሁም ከጋራ መግባባት ሰላማዊ ማህበረሰብ ይወለዳል“ ነበር ያሉት፡፡

ባለፈው ሳምንት ስለተደረገው ዘግናኝ የግድያ እልቂት ሁኔታ በግልጽ የመናገር ችሎታ፣ የቃላት ምርጫ የማድረግ፣ በግልጽ የመናገር ጥበብ ተሰጥኦ እና የፍልስፍና ጥልቀትን እና ግፊትን በመላበስ የእራሴን ሀዘን እና የተደበላለቁ ስሜቶች ስለተፈጸመው ሰይጣናዊ ድርጊት በማውገዝ፣ የማውገዝ የመከራከሪያ ነጥብ በማቅረብ፣ በመክሰስ፣  የሌባ ጣትን በሰዎች ላይ በመቀሰር እና በኃይለኛ ድምጽ ከፍ አድርጎ በመጮህ ማውገዝ በጣም ቀላል ነገር ነበር፡፡

ሆኖም ግን ቁጣ እና ጥልቅ ሀዘን አንዳቸው ለአንዳቸው ፍጹም የሆነ እንግዳ ነገሮች ናቸው፡፡

ቁጣ በቀልን፣ ንዴትን፣ የኃይል ድርጊትን እና የቁጣነት ስሜትን የሚቀሰቅሱ ነገሮችን ሲያዝዝ ጥልቅ ሀዘን ደግሞ ትልቅ እሳቤ ማንጸባረቅን፣ ቀጣይነት ያለው ማሰብን እና መጥፎ ነገሮችን ከማድረግ የመታቀብ ሀሳብን በስራ ላይ ለማዋል ትዕዛዝ ይሰጣል፡፡ ጥልቅ ሀዘን እንዲህ የሚሉ ጥያቄዎን ያቀርባል፡ ከዚህ ስሜት አልባ ከሆነው የሉሲኒያ፣ ሚኔሶታ እና ከዳህላስ የሞት እልቂት ተጠቃሚው ማን ነው? በነጻዋ እና የጀግኖች ሀገር በሆነችው እንደዚህ ያለ ስሜት አልባ የሞት እልቂት እና ውድመት የተፈጸመው ለምንድን ነው? (አዎ በአሜሪካ የተለዬ ለመሆኑ አምናለሁ፡፡)

ስለሆነም ቁጣየን አጥብቄ በመያዝ የሀዘን ስሜቶቼን በማስወገድ በዚህ ባለፈው ሳምንት በሉሲኒያ፣ በሚኔሶታ እና በዳላስ በተፈጸመው አሰቃቂ የሞት እልቂት ያለኝን ሀዘን እገልጻለሁ፡፡

ሆኖም ግን ቁጣየን እና ቁጣዬን ለመግለጽ የሚያስችል የአነጋገር ጥበብ ኃይል ስለሚያጥረኝ የዚህ ዓይነት ክህሎት በተፈጥሮ ተሰጥኦ ከታደሉት መዋስ አለብኝ፡፡

ባለፈው ሳምንት ስለተፈጸመው ስሜትአልባ የኃይል ጥቃት እንዲህ የሚሉት የሮበርት በርንስ የግጥም ስንኞች ያለኝን ስሜት እንዴት እንደገዙት በግልጽ የሚያመላክት ነው፡ “ሰው በሰው ላይ ያለው ኢሰብአዊነት/በሺዎች የሚቆጠሩትን ለቁጥር የሚያዳግቱ ሰዎች በሀዘን እንዲወድቁ ያደርጋል!…/… ይህ ካልሆነ እኔስ ለምን የሀዘን ሰላበ እሆናለሁ/የእርሱ ጭካኔ ወይስ ደግሞ የንቀት ድርጊቱ?/ነው ወይስ ደግሞ ሰው የእራሱ ወንድም በሆነው ሰው ላይ ሀዘን እንዲደርስ የሚያደርገው ለምንድን ነው?”

በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ማዘን ያለባቸው ለምንድን ነው?! እኮ ለምን?

ስለዚህ በሉሲኒያ፣ በሚኔሶታ እና በዳላስ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የፈጸሙትን ኢሰብአዊነት የእልቂት ድርጊት ሳስብ በአሜሪካ እና በሌሎች ሀገሮች ከሚገኙ በሚሊዮኖች ከሚቆጠሩ ህዝቦች ጋር በአንድነት በመሆን አዝናለሁ፡፡

በጣም ጥቂት ቁጥር ባላቸው እና በጥላቻ እና በእብሪት የሚነዱ ጨካኝ የፖሊስ አባላት ጥቁር ወንዶችን እና ሴቶችን በዘፈቀደ እንደ አውሬ በመንገድ ላይ እያሳደዱ ሲገድሉ እና ሲያሰቃዩ እንደ ዳኞች፣ ችሎቶች እና አስፈጻሚዎች ሆነው እራሳቸው እያገለገሉ ሲታዩ ይህ እንግዲህ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

አንድ ሰው የጥይት ባሩድ የተሞላ መሳሪያ በመታጠቅ እንደ ዳኛ፣ ችሎት እና አስፈጻሚ ሆኖ የሚሰራ ከሆነ እና በቆዳ ቀለማቸው ምክንያት በዘፈቀደ 5 የፖሊስ ኃላፊዎችን የሚገድል ከሆነ እና ሌሎችን 7 ሰላማዊ ዜጎችን ደግሞ በጽኑ እንዲቆስሉ የሚያደርግ ከሆነ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

በአመራር ላይ ያሉ ሰዎች ፖሊሲዎችን እና የአሰራር ሂደቶችን በመከተል ፖሊስ ኃይልን በመጠቀም የሚያደርገውን ግድያ መቆጣጠር ካልቻሉ፣ በፖሊስ መምሪያዎች ዘንድ ኃይልን የመጠቀም እና በወንጀል ያለመጠየቅ ባህልን የማይለውጡ ከሆነ እና በህገወጥ የፖሊስ አባላት ህጋዊ ግድያን የሚፈቅዱ ከሆነ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

የአፍሪካ አሜሪካዊ ወላጆች ስለልጆቻቸው ደህንነት የሚፈሩ ከሆነ እና በየተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ከህገወጥ የፖሊስ ኃላፊዎች ግድያ እንዲጠነቀቁ ትምህርት የሚሰጡ እና የፖሊስ ኃላፊውን ለጠብ የሚጋብዝ ምንም ዓይነት ቃላትን እንዳይጠቀሙ የሚያስተምሩ ከሆነ የዚህ ውጤት የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

ሕገወጥ ፖሊሶቹ አፍሪካ አሜሪካዊ የሆኑ ዜጎችን የመንግስት እና የነጭ ጠላት አድርገው የሚመለከቱ ከሆነ ለዚህ መፍትሄው ተኩሰው መግደል እና በኋላ ጥያቄዎችን መጠየቅ ከሆነ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

ወጣት አፍሪካዊ አሜሪካውያን ስራ አስፈጻሚ ነጭ የፖሊስ አባላትን ሰላምን እና ጸጥታን ከማስከበር ይልቅ ዜጎችን እንደሚገድል እንደ አዳኝ እና ገዳይ ፖሊሶች አድርገው የሚያዩአቸው ከሆነ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

በአመራር ስልጣን ላይ ያሉ ዜጎች ያለምንም ገደብ መሳሪያ ከሚይዙ ታጣቂዎች ገንዘብ የሚቀበሉ ከሆነ እና በአሸባሪነት ከሚጠረጠሩ እና ከሌሎች ሰዎች እጅ ላይ የጦር መሳሪያዎች እንዳይገቡ እና እንዳይታጠቁ ሕጉን ተከትለው መከልከል ካልቻሉ እና ኃላፊነታቸውን በአግባቡ መወጣት የማይችሉ ከሆነ  የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

በፖሊስ መምሪያዎች የፖሊስ ዘረኝነት እየተጠናከረ የሚሄድ ከሆነ እና የፖሊስ አመራር ሕገወጥ የፖሊስ ኃላፊዎች በህዝብ ላይ ስቃይ ሲፈጽሙ እና ህብረተሰቡ የሚያቀርባቸውን ቅሬታዎች አላየሁም አልሰማሁም በማለት የዝሆን ጆሮ ይስጠኝ በማለት ጆሮ ዳባ የሚል ከሆነ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

ወጣት ሰዎች በችጋጎ ከተማ እና በሌሎች ከተሞች ጠብመንጃ በመያዝ ሌሎችን በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ሰዎችን ስሜት አልባ በሆነ መልኩ የሚገድል፣ አካለ ጎደሎ የሚያደርግ እና ጉዳት የሚያስከትል ከሆነ የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሙት ኢሰብአዊ ድርጊት ነው ከማለት በስተቀር ሌላ ምንም ሊባል አይችልም፡፡

ሌሎችንም በርካታ የሆኑ ወቀሳዎች ለማቅረብ ረዥም ርቀት መጓዝ ይቻላል፡፡ ሆኖም ግን የሞራል ስብዕና ምርጫዎች ውሱን ናቸው፡፡ የሌባ ጣታችንን በሌሎች ሰዎች ላይ ስንቀስር ሌሎቹ ሶስቱ ጣቶቻችን ወደ እኛ እንደሚቀሰሩ መገንዘብ አለብን፡፡ ግልጽ በሆነ መልኩ ለማስቀመጥ እኛው እራሳችን የመፍትሄው አካል እስካልሆን ድረስ የችግሩ አካል እኛው እንደሆን ማወቅ ተገቢ ነው፡፡

የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሟቸው ኢሰብአዊ ድርጊቶች በማንኛውም ዘር፣ ጎሳ፣ ጾታ ወይም ደግሞ ዜግነት ላይ ብቻ የተወሰኑ አይደሉም፡፡

የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሟቸው ኢሰብአዊ ድርጊቶች ከነጭ፣ ከጥቁር፣ ከቡናማ፣ ከብጫ ወይም ደግሞ ከሰማያዊ ቀለም ሊመጣ ይችላል፡፡

ኃይል የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሟቸው ኢሰብአዊ ድርጊቶች የመጨረሻ መገለጫ ነው፡፡ ኃይል በሰዎች መንፈስ ውስጥ ያለ አውዳሚ በሽታ ነው፡፡ ለዚህ የመንፈስ በሽታ ብቸኛ ፈውስ ዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግ በአንድ ወቅት እንዳሉት የታገሉለት፣ የተሰቃዩለት እና ህይወታቸውን በሙሉ የሰውለት ፍቅር ብቻ ነው፡፡

የኃይል ስልጣን አውዳሚ በሆነ መልኩ ቀስ በቀስ በሰዎች ልብ እና አእምሮ ውስጥ ጥላቻን፣ ቁጣን፣ እብሪተኝነትን፣ መኮፈስን፣ ተስፋማጣትን እና ውርደትን የሚሞላ ኃይል ነው፡፡ ለዚህም ነው የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሟቸው ኢሰብአዊ ድርጊቶች በጦር ሜዳ በመንገድ ላይ ወይም ደግሞ በዘፈቀደ ድርጊት በሰላማዊ ሰዎች ላይ በጠብመንጃ የሚከፈት ጦርነት ሳይሆን ይልቁንም በወንዶች ሰዎች እና በሴቶች ሰዎች መልካም ፈቃደኝነት በልቦቻቸው እና በአእምሯቸው ውስጥ ትግል በማድረግ ማሸነፍ እንደሚቻል የማምነው፡፡

ሰብአዊነትን ወደ ወንዶች እና ሴቶች መመለስ አለብን፡፡

ሰብአዊነትን ወደ ወንድ ፖሊስ፣ ወደ ሴት ፖሊስ፣ ወደ ጥቁር ወንድ፣ ወደ ቡናማ ወንድ እና ወደ ብጫ ወንድ መመለስ አለብን፡፡ ሰብአዊነትን ወደ ሰበአዊነት መመለስ አለብን፡፡

መንገስታት የሰው ልጅ በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሟቸው ኢሰብአዊ ድርጊቶችን ለመቆጣጠር የተመሰረቱ ለመሆናቸው አምናለሁ፡፡

ጀስቲስ ብራንዲስ “መንግስት ሕግን የሚጥስ ከሆነ ለሕግ ያለውን ንቀት ይፈለፍላል፣ እያንዳንዱ ሰው ሕግን እንዲጥስ ይጋብዛል፣ ስርዓተ አልበኝነትን ይጋብዛል“ በማለት ማስጠንቀቂያ በሚሰጡበት ጊዜ የሰው ልጅ በሰው ልጆች ላይ ስለሚፈጽማቸው ኢሰብአዊ ድርጊቶች አሜሪካውያንን ማስጠንቀቃቸው ነበር፡፡

ታማኝ ያልሆኑ ህገ ወጥ ፖሊሶች ለአፍሪካ አሜሪካውያን ዜጎች አንዳንድ ድርጊቶችን ሲያደርጉ ለምሳሌ ያህልም ኮምፓክት ዲስክ ወይም ደግሞ ድራይቭ ዲስክ በሚሸጡበት ጊዜ በሌሎች የተለያዩ የቆዳ ቀለሞች ባሏቸው ሰዎች አማካይነት በመንግስታቸው እና በዜጎቻቸው ላይ መጠነ ሰፊ የሆነ ጥላቻ እንዲፈለፈል ያደርጋሉ፡፡

እምነት የሌላቸው ፖሊሶች ጠብመንጃቸውን እራሱን ሕግ ማድረግ ሲጀምሩ ለሕግ የበላይነት ያላቸውን ንቀት ለዜጎች ያስተምራሉ፣ እናም እራሳቸው ሕግ ደፍጣጮች ይሆናሉ፡፡

ከጀስቲስ ብራንዲስ በርካታ ምዕተ ዓመታት በፊት ታላላቆቹ የፖለቲካ ህልወት ቀማሪዎች እንዲህ የሚል ጥያቄ አቅርበው ነበር፡  “የሰው ልጆች የኃይልን አደገኛነት እና ፍርሀትን በማስወገድ እንዴት አድርገው በአንድነት በሰላም መኖር ይችላሉ?“

በእራሳቸው መልሶች የሰው ልጆች በሰው ልጆች ላይ የሚፈጽሟቸው ኢሰብአዊ ድርጊቶች (የጫካው ሕግ) መሆኑን እና ትልቁ እና ጠቃሚው የሕግ አስፈጻሚም ትልቁን ኃይል የያዘው ሰው የነበረ መሆኑን እንደ የተፈጥሮ መንግስት አድርገው አስበው ነበር፡፡ በተፈጥሮ መንግስት ውስጥ ሰው እራሱን ከሰው ለመጠበቅ ዋናው መሳሪያ እያንዳንዱ ሰው ጦርነትን ማካሄድ ነበር፡፡ እያንዳንዱ ሰው የእራሱን ፈቃድ ለመፈጸም ትልቅ ኃይል እስካለው ድረስ ስለእያንዳንዱ ነገር ተፈጥሯዊ መብት ነበረው፡፡ በተፈጥሮ መንግስት ጊዜ ህይወት “ብቸኛ፣ ደኃ፣ የተናቀ፣ ጭካኔ የተሞላበት እና አጭር” የሆነ እያንዳንዱ ሰው እያንዳንዱን ሰው የሚፈራበት እና እርስ በእርሱ መተማመን ያልነበረበት ጊዜ ነበር፡፡ በተፈጥሮ መንግስት ብቸኛ የሆነው እርግጠኛው ነገር ዓለም አቀፋዊ የደህንነት እጦት ነው፡፡

የጥላቻ ቡድኖች እና የጸረ መንግስት ንቅናቄዎች እየተባሉ የሚጠሩት “እያንዳንዱ ሰው ከእያንዳንዱ ሰው ጋር ጦርነት እንዲያደርግ“ ወደሚጋብዘው ወደ ተፈጥሮ የመንግስት ስርዓት እንድንመለስ ይፈልጋሉ፡፡

ሆኖም ግን እኛ የጫካው ሕግ በላያችን ላይ የሚጣልብን ሳይሆን እራሳችንን ከህገ ወጥነት ሊከላከሉልን የሚችሉ ሕጎች እና ሕገ መንግስት ያሏት ሀገር ህዝቦች ነን፡፡

በከፊልም እንኳ ወደ ተፈጥሮ መንግስት መመለስ እንዳንችል ስለእያንዳንዳችን ህይወት ህልውና፣ ስለነጻነት፣ ስለሰብአዊ መብቶች አጠባበቅ፣ ስለክብር እና ስለሕግ የበላይነት መስፈን ሁላችንም ጥረት ማድረግ አለብን፡፡

ሁለቱን አፍሪካ አሜሪካዊ ዜጎች የገደሏቸው እምነት የለሾች ፖሊሶች በቀን ከቀን ህይወታቸውን የዜጎችን ደህንነት በመጠበቅ ላይ የተሰማሩትን 99.9 በመቶ የሚሆኑትን ፖሊሶች በምንም ዓይነት መልኩ ሊወክሉ አይችሉም፡፡

የጠብመንጃ ምላጭ በመሳብ 5 የፖሊስ ኃፊዎችን የገደለው እና 7 ያቆሰለውን ብቸኛ ገዳይ ማንንም አፍሪካ አሜሪካዊ ፖሊስ አይወክልም፡፡

ሆኖም ግን ሁሎቹም ነብሰ ገዳዮች ሌላ ማንንም ሳይሆን ጥላቻን እና ጥላቻን ብቻ የሚፈለፍለውን እራሱን ጥላቻን ይወክላሉ፡፡

ለእራሱ ለጥላቻ ቦታ መስጠት ወይም የጥላቻን መንገድ መከተል የለብንም ምክንያቱም የጥላቻ መንገድ የሚመራን ወደሌላ ወየትም ሳይሆን ማለቂያ ወደሌለው የኃይል እና የቅጣት አዙሪት ነው፡፡

በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ በርካታ የአሜሪካውያንን እና በአጠቃላይ በዓለም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎችን ህይወት ለቀጠፈው የኃይል ለእርምጃ መፍትሄው ምንድን ነው?

መልሱ እንዲህ የሚል አጭር እና ግልጽ ነው፡ ኃይል አልባ መንገድ/ሰላምን መከተል! ይህ የሰላም መንገድ መሳሪያ ምንም ዓይነት ቁስል ሳያደርስ የሰላም ፈውስን ያመጣል፡፡ ሰላም ፈውስን የሚያመጣ ጎራዴ ነው፡፡

ሆኖም ግን ይህንን የአንድ ቃል መልስ ከማስወገድ እና ውጤታማ መሳሪያ አይደለም፣ ያለፈበት ነው፣ አሮጌ ነው እና የቦቅቧቃ ፈሪዎች አስተሳሰብ ነው በማለት ከማሰብ በፊት እባክዎ እንዲህ የሚሉትን የዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግን ቃላት ያዳምጡ (የዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግን የ7 ደቂቃዎች ንግግር ከዚህ በታች ከዩቱቤ የግንኙነት መስመር ጋር በማገናኘት ያዳምጡ)፡

በሰላማዊ የሆነ ተቃውሞ ፍልስፍና መረጃን ከውስጥ ቆፍሮ በማውጣት የመገዳደር ትግላችንን መቀጠል አለብን፡፡ ስለዚህ መንገድ ዘዴ ኃይል ያለው አንድ ነገር አለ፡፡ ይህንን መንገድ በየጊዜው የሚንቁ  ሰዎች እንዳሉ አውቃለሁ፡፡ በደቡብ ታምር ሰርቷል፡፡ ከእርሱ ጋር የሞራል ልዕልና አለው ምክንያቱም በጠንካራ የሞራል ስብዕና የሞራል ስብዕና ዓላማዎችን ለማግኘት መልካም አጋጣሚ ሰጥቶናል፡፡ የሞራል ስብዕና ማለት ይህ ነው፡፡ እናም የተወሰኑ ተግባራዊ ውጤቶች አሉት፡፡ የተቃዋሚውን የመከላከል ሞራል ስብዕና ያጋልጣል… መሳሪያ አልባ ያደርገዋል፣ እንደዚሁም በእርሱ ምን ማድረግ እንዳለበት አያውቅም፡፡ በእስር ቤት ውስጥ የሚያጉርህ ከሆነ ይኸ በቂ ነገር ነው፡፡ በእስር ቤት የማያስገባህ ከሆነ ደግሞ መልካም ነገር ነው፡፡ የሚደበድብህ ከሆነ ይኸ በቂ ነገር ነው፡፡ የማይደበድብህ ከሆነ ግን መልካም ነገር ነው… ስለዚህ ጉዳይ ተቃዋሚው ምን ማድረግ እንዳለበት ማወቅ የማያስችለው አንድ ነገር አለ፡፡ አሁን ኃይልን በመጠቀም ምን ማድረግ እንደሚችል ሊያውቅ አይችልም፡፡ የመንግስት ሚሊሻዎችን መጥራት ይችላል፡፡ ብሄራዊ የደህንነት ጥበቃን መጥራት ይችላል፣ እናም በመቶዎች እና በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ህዝቦችን መግደል እና ብጥብጥ ሊያስነሱ የነበሩ ናቸው በማለት የክርክር ጭበጡን ማቅረብ ይችላል፡፡ ኃይልን እንዴት መያዝ እንዳለባቸው ያውቃሉ፡፡ ሆኖም ግን ኃይልአልባን/ሰላማዊ መንገድን እንዴት መያዝ እንዳለባቸው ደግመው እና ደጋግመው አያውቁትም…“ (የ7 ደቂቃዎች ሙሉ ንግግር በዩቱቤ ለማዳመጥ እዚህ ጋ ይጫኑ፡፡)

የግድያ የኃይል ጥቃት በተፈጸመባቸው በአልቶን ስተርሊንግ፣ በፊናዶ ካስል እና በዳላስ የፖሊስ ኃላፊዎች በሚካኤል ብራውን፣ ኤሪክ ጋርነር፣ ኦስካር ግራንት፣ ዶንትሬ ሀሚልተን፣ ጆን ክራውፎርድ 3ኛ፣ ኢዜል ፎርድ፣ ዳንቴ ፓርከር፣ ታኒሻ አንደርሰን፣ አካይ ጉርሌይ፣ ታምር ራይስ፣ ሁማይን ብሪስቦን፣ ጀራሜ ሬይድ፣ ቶኔ ሮቢንሰን፣ ፊሊፕ ኋይት፣ ኤሪክ ሀሪስ፣ ዋልተር ስኮት፣ ፍሬዲ ግራይ፣ ካጀሜ ፓውል፣ ታይሪ ውድሰን፣ ቪክቶር ኋይት 3ኛ፣ ቬቴ ስሚዝ፣ ማኬንዚ ኮችራን፣ ጆርዳን ቤከር፣ አንዲ ሎፔዝ፣ ጆናታን ፌሬል፣ ካርሎስ አልሲስ፣ ላሪ ኢውጀኔ ጃክሰን፣ ዲኦን ፍሉድ፣ ጆኒ ካማሂ ዋረን፣ አያኔ ጆኔስ፣ ሳንድራ ብላንድ፣ በእኔ መኖሪያ ከተማ በሳንበርናርዲኖ የሽብር ጥቃት ሰለባ ለሆኑት፣ በኦርላንዶ የጥላቻ ወንጀል እና የሽብር ሰለባ ለሆኑት፣ የጋብቻ ችግር ያለባት እናት በመሆኗ ምክንያት ሁለቱን ሴት ልጆቹን በጣም ይወዳቸው የነበረውን አባት በሀዘን ለማኮማተር በማሰብ በሁለቱ ወጣት ሴት ልጆች ላይ የፈጸመችው ግድያ…በችጋጎ፣ በዴትሮይት፣ በሜምፊስ፣ በኦክላንድ፣ በቅዱስ ሉዊስ፣ በሎስ አንጀለስ፣ እና በሌሎች በርካታ ቦታዎች በየዓመቱ በሚገደሉ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ሰዎች ጥልቅ ሀዘን ይሰማኛል፡፡

በእነዚህ ዜጎች መሞት ታላቅ ሀዘን ይሰማኛል ምክንያቱም ለሰብአዊ ፍጡር ታላቅ ርህራሄ አለኝና፡፡

ፕሬዚዳንት ኦባማ እንዲህ በማለት ሲናገር በእርግጥም ትክክል ነበር፣ “ምንም ዓይነት ጥቁር አሜሪካ እና ነጭ አሜሪካ የለም፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ላቲኖ እና የኢስያ አሜሪካ የለም –  ያለችው የተባበረች ዩናይትድ ስቴትሰ አሜሪካ ብቻ ናት“ ነበር ያለው፡፡

እንደ አሜሪካውያን ሁሉ እኛም አንድ ህዝብ እና አንድ ሀገር ነን፡፡ በወገኖቻችን ላይ የእልቂት ግድያ በፈጸሙት ስሜትየለሽ ወሮበላ ዘራፊ አምባገነኖች የጭካኔ አገዛዝ በመገዛት ላይ እንገኛለን፡፡

እንዲህ በሚሉት የጆን ዶኔ፣ የማርቲን ሉተር ኪንግ እና የማህተመ ጋንዲ ቃላት የጽሁፌን ዳህራ ልቋጨው፡

“ማንም ሰው እራሱን ከሁሉም ያገለለ ደሴት አይደለም፣ እያንዳንዱ ሰው ዋና የሆነው የዓለም አካል ነው፡፡ አንድ የመሬት አካል በውኃ ቢጥለቀለቅ እና አውሮፓ [አሜሪካ] ከባህር ወጣ ብሎ የሚታይ የመሬት አካል ቢኖራቸውም እንደዚሁም ሁሉ ጓደኞቻቸው ወይም የመሬት ከበርቴዎች ጥንት በውርስ የያዙት መሬት ቢሆንም ያው የዓለም አንድ አካል ነው፡፡ በማንም ሰው መሞት ታላቅ ሀዘን ይሰማኛል ምክንያቱም ለሰብአዊ ፍጡር ታላቅ ርህራሄ አለኝና… “ (ጆን ዶኔ፣ Devotions Upon Emergent Occasions, Meditation XVII.)

“ጨለማን ጨለማ ሊያስወግደው አይችልም፣ ይህንን ማድረግ የሚችለው ብርሀን ብቻ ነው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ጥላቻን ጥላቻ ሊያስወግደው አይችልም፡፡ ይህንን ማድረግ የሚችለው ፍቅር ብቻ ነው፡፡“ – ማርቲን ሊተር ኪንግ

“ጥንካሬ ከአካላዊ የብቃት አቅም የሚመጣ አይደለም፡፡ ይልቁንም ከማይበገረው የመንፈስ ጥንካሬ የሚመጣ ነው፡፡“ – ማህተመ ጋንዲ

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!  

ሀምሌ 5 ቀን 2008 ዓ.ም