ለኢትዮጵያውያን ምንም የሚቀር ሀገር የላቸውምን?

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም    

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

የደራሲው ማስታወሻ፡ የዚህ ሳምንት ትችቴ በኢትዮጵያ በጋምቤላ ካራቱሪ አግሮ ፕሮዳክትስ ፒኤልሲ የተባለው ድርጅት መውደቁን ተከትሎ ባለፈው ሳምንት ያቀረብኩት ትችት ተከታይ ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ2010 ዘ-ህወሀት 100 ሺ ሄክታር ለበጥባጩ የመሬት ተቀራማች ለሳይ ካራቱሪ ካስረከበ በኋላ በዚህ ወር መጀመሪያ አካባቢ የኮንትራት ውሉን ሰርዟል፡፡

ከካራቱሪ አስደንጋጭ ውድቀት በኋላ ዘ-ህወሀት በአሁኑ ጊዜ 725 ከ/ሜ ርዝመት ያለውን፣ እንዲሁም 250 ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት ያለውን እና 600 ሺ ሄክታር ለም መሬት የሆነውን የኢትዮጵያን አንጡራ የግዛት ሉዓላዊነት ለሱዳን ለመስጠት ዝግጅቱን አጠናቅቋል፡፡ (ለሱዳን ይሰጣል ተብሎ የሚጠበቀውን የመሬት ስፋት ካርታ ለማየት ከዚህ ጋ ይጫኑ፡፡)

ዘ-ህወሀት ለሱዳን፣ ለካራቱሪ ወይም ደግሞ ለማንኛውም መሬት ተቀራማች ሸፍጠኛ ስለሚሰጠው የመሬት ድንበር የሕግ ጉዳይ ውጤት ትኩረት የለኝም፡፡ (ይቅርታ የድንበር ማመላከት ማለቴ ነው፡፡) ዘ-ህወሀት ለካራቱሪ ከ300 ሺ ሄክታር በላይ ሲሰጥ ምንም ዓይነት ጉዳይ አድርጌ አልወሰድኩትም ነበር፡፡ ካራቱሪ እ.ኤ.አ በ2011 ውድቀት እንደሚደርስበት እና እ.ኤ.አ በ2016 በአስገራሚ ሁኔታ እንደሚወድቅ ትንበያ ሰጥቸ ነበር፡፡

አሁንም ቢሆን ዘ-ህወሀት 600 ሺ ሄክታር መሬት ዛሬ ለሱዳን ቢያስረክብ የሚያሳስበኝ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ይህ ስምምነት እንደ ካራቱሪ ሁለተ ጊዜ በአስገራሚነት ወድቆ እንደሚንኮታኮት መተንበይ እችላለሁና፡፡ የመሰረት ድንጋይ የሆነውን የዓለም አቀፍ የሕግ ስምምነት (ማንም የሌለውን ሊሰጥ አይችልም) የሚለውን መርህ አምናለሁና፡፡ እራሱን ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ እያለ የሚጠራው ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የኢትዮጵያን መሬት አሳልፎ ለባዕድ ለመስጠት ስልጣኑ እና መብቱ የለውም፡፡ የሌለውን ሊሰጥ አይችለም፡፡ ዘራፊ ወሮበላ የዘረፈውን ህጋዊ ለማድረግ በሌላ በማንኛውም ሰው ወይም ድርጅት ስም ማስተላለፍ አይችልም፡፡

በአሁኑ ጊዜ ዘ-ህወሀት በኢትዮጵያ ላይ የሚያደርገው ነገር ሁሉ ነገ ምንም ዓይነት ነገር እንደማያመጣ ነገ ጸሐይ ትወጣለች የሚለውን ያህል እርግጠኛ ነኝ፡፡ ዘ-ህወሀት ከነፋሱ ጋር ብቻ በኖ የሚጠፋ ይሆናል፣  ዘ-ህወሀት እራሱ ጉምን ይዘግናል!

ሆኖም ግን ቶማስ ጃፈርሰን ለአሜሪካ እንዳደረገው ሁሉ እኔም ለኢትዮጵያ እንዲህ በማለት እጨነቃለሁ፡ “አምላክ ትክክል ነው ብዬ እስካመንኩ ድረስ ለሀገሬ እጨነቃለሁ፡ የእርሱ ፍትህ ለዘላለም የሚያንቀላፋ አይደለም፡፡“

የአምላክ ፍትህ በሚያነቃኝ ጊዜ ለኢትዮጵያ እጨነቃለሁ!

ሁሉም ኢትዮጵያውያን በሙሉ በብድር በተገኘ መሬት ላይ ነው የሚኖሩት? በእርግጥ!

Eth Map 11 AAባለፈው ሳምንት ሱዳን ትሪቡን እንዲህ የሚል ዘገባ አቀረበ፡ “በሱዳን እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን ድንበር የማከለል ስራ የሚሰራ የቴክኒክ ኮሚቴ በዚህ ዓመት በመሬት ላያ ያለውን ስራ በሙሉ ያጠናቅቃል፡፡“ እንደ ዘገባው ከሆነ የድንበር ማካለሉ ስራ የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አምባገነኑ መለስ ዜናዊ ሞትን ተከትሎ ተቋርጦ ነበር፡፡ የድንበር ማካለሉ ስራ 72 ኪ/ሜ ርዝመት ባለው እና በሱዳን ደቡባዊ ክፍል የሱዳን ምስራቃዊ ግዛት ከሆነው ከጋዳሪፍ በአል ፋሻጋ አካባቢ ባለው ይጀምርና እስከ 250 ኪሜ ርቀት የሚሸፍነውን እና 600 ሺ ሄክታር ለም መሬት ያለውን ያካትታል፡፡ አትባራ፣ ሴቲት እና ባስላም ወንዞች ወደዚህ አካባቢ ይፈስሳሉ፡፡

የድንበር ማካለል የቴክኒክ ኮሚቴ ኃላፈው አብደላ አል ሳዲቅ እንዲህ ብሏል፡ “ለሁለቱ ህዝቦች ትብብር ያግዝ ዘንድ የሱዳን መንግስት የኢትዮጵያ ገበሬዎች የእራሱን መሬት እንዲያርሱ ፈቅዷል፡፡ ሆኖም ግን ኢትዮጵያ አል ፋሺጋ በሱዳን ሉዓላዊ ግዛት ውስጥ መሆኑን በጽናት በማመን እውቅና ትሰጣለች፡፡“

አወዛጋቢው መሬት የአማራ ክልል ነው፡፡ የህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ (ዘ-ህወሀት) ስለድንበር ማካለሉ ወይም ደግሞ ለሱዳን ስለሚመለሰው መሬት ጉዳይ ምንም ዓይነት ዝርዝር መግለጫ አልሰጠም፡፡

እኔ መጠየቅ የምፈልጋቸው ጥቂት ጥያቄዎች እነሆ፡

1ኛ) የሱዳን መንግስት የኢትዮጵያ ገበሬዎች ለአስርት ዓመታት ያህል ሲያርሱት እንዲቆዩ የፈቀደው ለምንድን ነው?

2ኛ) የሱዳን መንግስት ምንም ዓይነት የለውጥ ጠቀሜታ ለሌለው ነገር 600 ሺ ሄክታር ለም መሬት ለኢትዮጵያውያን የሰጠው ለምንድን ነው?

3ኛ) ኢትዮጵያ አል ፋሻጋ  የሱዳን ሉዓላዊ ግዛት ነው ብላ በጽናት የምታምን እና እውቅናም የምትሰጥ ከሆነ (የተበላ እቁብ) የቴክኒክ ኮሚቴ እየተባለ የሚዘመረው እና የሚደነሰው እንዲሁም እ.ኤ.አ በ2016 ውይይት እና ስምምነት እየተባለ ሽር ጉድ የሚባለው ለምንድን ነው?

4ኛ) አል ፋሻጋ የተባለው የኢትዮጵያ ግዛት ለሱዳን መሰጠት ማለት የድንበር ኮሚሽን እየተባለ በሚጠራው እንደ ሽልማት የኢትዮጵያ አንጡራ ግዛት ለኤርትራ መሰጠት ይኖርበታልን?

5ኛ) ዘ-ህወሀት የኢትዮ-ኤርትራን ቀያጁን የድንበር ኮሚሽን ውሳኔ በመቃወም አሻፈረኝ ብሎ ከተቀመጠ በኋላ ለምንድን ነው አሁን በፈቃደኝነት የኢትዮጵያን ግዛት 600 ሺ ሄክታር ለም መሬት ለሱዳን የሚሰጠው?

6ኛ) የዘ-ህወሀት ህገ መንግስት አንቀጽ 48 ለአባል ሀገሮች ውስጣዊ ሉዓላዊነትን ይሰጣል፣ እናም የድንበር ውዝግብ በሚነሳበት ጊዜ አባል ሀገራት በሰላማዊ መንገድ ውዝግቡን በመወያየት ይፈታሉ፡፡ ዘ-ህወሀት የችግሩ ሰለባ ለሆኑት የአማራ ህዝቦች መሬቱ በህዝበ ውሳኔ ለሱዳን መሰጠት አለመሰጠቱ እንዲወሰን አድርጓልን?

7ኛ) ዘ-ህወሀት እና ሱዳን ኢትዮጵያን እንደገና ያታልላሉ (ያጭበረብራሉ አላልኩም)?

በዘ-ህወሀት ህገ ወጥ ጋራዥ ውስጥ ብዙም የማይነገርለት የኢትዮጵያ ታሪክ፣

አሁን በህይወት የሌለውን አምባገነኑን የመለስ ዜናዊ የኢትዮጵያን ሉዓላዊ ግዛት እ.ኤ.አ በ2008 ለሱዳን አሳልፎ መስጠቱን በጽናት ተቃውሜ የነበረ መሆኑን የረዥም ጊዜ አንባቢዎቸ ያስታውሱታል፡፡ ከዚያም በኋላ “ጋሻ ለኢትዮጵያ” ከሚል የሲቪክ ማህበረሰብ ፊት በመቅረብ ንግግር በማድረግ መለስ ዜናዊ በድንበር ማመላከት ሰበብ በጣም ግዙፍ የሆነ የኢትዮጵያን የግዛት መሬት ለሱዳን ለመስጠት ሚስጥራዊ ስምምነት ማድረጉን ተችቼ ነበር፡፡ ዜናዊ ከህዝብ በመደበቅ ከሱዳኖች ጋር ባደረገው ስምምነት ላይ ህዝብ ሳይመክርበት እና ሳይወያይበት የግል ስምምነት ማድረጉን ሞግቸ ነበር፡፡

ለታሪክ ታላቅ ትኩረት የሚሰጡ ሰዎች የዘ-ህወሀት ብቸኛው ተልዕኮ ከዚህ ቀደምም ሆነ በአሁኑ ጊዜ ሀገሪቱን ሙሉ በሙሉ መከፋፈል እና ማውደም መሆኑን ያስታውሳሉ፡፡

የዘ-ህወሀት ታላቁ ዕቅድ ኢትዮጵያን የተለያዩ ዘዴዎችን በመጠቀም እስክትደርቅ ድረስ ለረዥም ጊዜ መምጠጥ እና ወደ ትንንሽ ቁርጥራጭነት በመከፋፈል እንድትጠፋ ማድረግ ነው፡፡

የዘ-ህወሀት ታላቁ ስልት በመጥበሻ ላይ ባለው እንቁራሪት ተምሳሌትነት ይመሰላል፡፡ እንቁራሪት የፈላ ውኃ በያዘ ማሰሮ ውስጥ ብትጣል ወዲያውኑ ከመቅጽበት ዘላ ትወጣለች፡፡ ሆኖም ግን በቀዝቃዛ ውኃ ውስጥ እና ቀስ በቀስ እየሞቀ በሚሄድ ውኃ ውስጥ ብትጣል አደጋውን በግልጽ ስለማትገነዘበው እስከምትሞት ድረስ ልተቀቀል ትችላለች፡፡

ባለፉት 25 ዓመታት ውስጥ ዘ-ህወሀት ያደረገው ይህንኑ ነው፡፡ ሌቦች በመኪና ህገወጥ የመለዋወጫ ጋራዥ ውስጥ ስልታዊ በሆነ መልኩ በመነጣጠል፣ በመለያየት እና ኢትዮጵያን ቅርጫ በቅርጫ በመበጣጠስ ለከፍተኛ እና ዝቅተኛ ተጫራጮች መሸጥ ነው፡፡

የዘ-ህወሀት ገዥዎች በኢትዮጵያ ያላቸው ፍልስፍና በሚከተለው ግልጽ እሳቤ ሊቀመጥ ይችላል፡ ከዘ-ህወሀት በኋላ የጥፋት ውኃ ይምጣ ፡፡ ኖህ እና የጥፋት ውኃ እንደሆኑት ሁሉ፡፡ (ዘ-ህወሀት እርሱ ከተወገደ በኋላ የጥፋት ወኃ እንደማይኖር አያውቅም፡፡ እንዲህ ይላሉ፣ “እግዚአብሄር ለኖህ የቀስተ ደመና ምልክት ሰጠው፡ ምንም ዓይነት ውኃ የለም፡፡ በቀጣይ እሳት መጣ!“

ወይም ደግሞ በኢትዮጵያ አፈታሪክ አህያዋ እንዲህ ብላለች፡ “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል፡፡“ የዘ-ህወሀት አህዮች እነርሱ ከተወገዱ በኋላ ኢትዮጵያ ብትጠፋ ደንታ የላቸውም፡፡ ሆኖም ግን እነርሱ እንደሚጠፋ ነገ ጸሐይ ትወጣለች የማለትን ያህል እርግጠኛ ነኝ፡፡ ይህንን በሚገባ ያውቃሉ፡፡ የመለያያ ጊዜው እየተቃረበ በመጣ ቁጥር በድን ሆነው ሌሊት በነጭ ላብ ተዘፍቀው ከእንቅልፋቸው ብንን ይላሉ፡፡ በሌሊት በድብቅ ባልተጠበቀ መልኩ እንደሚመጣ ሌባ የእነርሱም የመወገጃ ቀን ሳይታሰብ ይመጣል፡፡

የዘ-ህወሀት ወንጀለኞች ከተወገዱ በኋላ ምን ሊከተል ይችላል?

ለኢትዮጵያ እጨነቃለሁ…

መሬቷን በመስጠት ኢትዮጵያን መከፋፈል፣ ዘ-ህወሀት የአሰብን ወደብ በመስጠት ኢትዮጵያን ወደብ አልባ ሀገር አደረጓት፡፡ የአሰብ ወደብ የኢትዮጵያ አካል እንዲሆን እ.ኤ.አ በ1991 የለንደን ኮንፈረንስ እየተባለ በሚጠራው ጉባኤ እና ዘ-ህወሀት እንዲመሰረት ባፋጠነው ጉባኤ ላይ አምባገነኑ መለስ ዜናዊ አሰብ አያስፈልግም በማለት ተቃውሟል፡፡

እ.ኤ.አ በ1998 የኢትዮጵያ ግዛት ከተወረረ እና ከተያዘ በኋላ በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ተዋጊዎች ህይወታቸውን በመገበር ወራሪውን ኃይል ወሳኝ በሆነ መልኩ ድል በመቀዳጀት በኃይል ከያዙት መሬት እንዲወጡ አድርገዋል፡፡

እ.ኤ.አ ታህሳስ 2000 አሁን በህይወት የሌለው ከሀዲው የዘ-ህወሀት መሪ የኢትዮጵያን የጦርነት ድል በዴፕሎማሲ እና በህግ በመሸነፍ ግዙፍ የሆነውን የኢትዮጵያን ግዛት የድንበር ኮሚሽን እተባለ ከሚጠራው ድርጅት ፊት በመቅረብ ለመስጠት ስምምነት አድርጓል፡፡ (ገጽ 96 ላይ ካርታውን ይመልከቱ፡፡)

ያ ክስተት በዘመናዊ የዓለም ታሪክ ውስጥ አንድ ሀገር ግዛቱን የወረረውን ኃይል ከፍተኛ መስዋዕትነት በመክፈል አንጸባራቂ ድል ከተቀዳጀ በኋላ ወዲያውኑ ያገኘውን ድል ወደ ጎን በመተው ያንኑ ግዛት አስገዳጅ ባልሆነ ዓለም አቀፋዊ እርቅ ሰበብ መልሶ ለጠላት በመስጠት የመጀመሪያ ነው፡፡

በጎሳ ፌዴራሊዝም ኢትዮጵያን በፖለተካ መከፋፈል፣

የጎሳ ፌዴራሊዝም እየተባለ የሚጠራው የዘ-ህወሀት ስልት ኢትዮጵያን ትንሽ በትንሽ እየነጣጠሉ ባንቱስታኒዝምን በመፍጠር የተሸረበ የፖለቲካ ሸፍጥ ነው፡፡ ክራይሲስ ግሩፕ የተባለው ዓለም አቀፍ ድርጅት ባካሄደው ጥናት ላይ የዘ-ህወሀትን የጎሳ ፌዴራሊዝም በጎሳ ማንነት ላይ የተመሰረተ እና በጎሳ፣ በዘር እና በቋንቋ ላይ መሰረት ያደረገ ስርዓት መሆኑን ግልጽ አድርጓል፡፡

ዘ-ህወሀት 100 ሚሊዮን የሚሆነውን ህዝብ ክልል የሚባል ስርዓት በመፍጠር ምንም ዓይነት ብሄራዊ ስሜት እንዳይኖር በማድረግ ኋላቀር ብሀረተኝነትን በማራመድ ህዝቡን ከፋፍሎ ለመግዛት ታስቦ ነው፡፡ የጎሳ ፌዴራሊዝም ህዝቡን በጎሳ ለመከፋፈል አሳሳች እና ቅን የሚመስል የፖለቲካ እና የህግ ሀረጎችን አካትቶ የያዘ ነው፡፡ ይህ እንደ አሮጌዋ ደቡብ አሜሪካ የጅም ክሮው ህጎች እየተካሄደ ያለ ዘመናዊ ልዩነት ነው፡፡ ክልል እየተባሉ የሚጠሩት በጎሳዎች የበላይነት ላይ መሰረት አድርገው በህገ መንግስቱ የተዋቀሩ ናቸው፡፡ በአካባቢው ያሉት የጎሳ ቡድኑ አባላት የእራሳቸውን የፖለቲካ እና የህግ ተቋሞች እንደዚሁም ሌሎች ኢትዮጵያውያን ለጎሳ ቡድኑ አባላት ያልሆኑ የአካባቢውን ህግ ያከብራሉ አለዚያም ለቅቀው እንዲሄዱ ይገደዳሉ፡፡ (በእርግጥ ይህ ህግ በዘ-ህወሀት አባላት ላይ ተግባራዊ አይሆንም፡፡)

ኢትዮጵያውያንን በማህበራዊ ህይወት በመከፋፈል ኢትዮጵያን መከፋፈል፣

ዘ-ህወሀት በጥላቻ ዓይን መተያየትን፣ ጥላቻን እና የኃይማት ጽንፈኝነትን በኢትዮጵያውያን ውስጥ እና መካከል በመዝራት የዕኩይ ድርጊት ስርዓትን ለመፍጠር ሞክሯል፡፡ ኢትዮጵያዊነት የሚለው ቃል ወይም ደግሞ የአማራን ስም ጥላሸት በመቀባት እና የጥላቻ እና የፍርሀት ሰለባ እንዲሆኑ በማድረግ ሀገራዊ ስሜት እንዲጠፋ ከፍተኛ ጥረት አድርጓል፡፡ ዘ-ህወሀት የበርካታ የጎሳ ቡድኖችን ታሪካዊ ቅሬታ በመቆፈር በጎሳዎች መካከል ቅራኔ እና አለመተማመን እንዲፈጠር አድርጓል፡፡ ዘ-ህወሀት እንዴት አድርጎ እንደሚያታልል እና የተማሩ ኢትዮጵያውያንን ሳይቀር መጀመሪያ የጎሳ ቡድናቸውን አባላት ከዚያም ኢትዮጵያዊነትን ማስከተልን እንዲማሩ ማድረጉ ለማመን የሚያስችግር ጉዳይ ነው፡፡ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ሁለተኛው አስርት የአንድን ሰው ዓለም አቀፋዊ አስተሳሰብ በማጥበብ በጎሳ ፖለቲካ አስተሳሰብ እንዲሸበብ ማድረግ ከእኔ አስተሳሰብ ውጭ ነው፡፡ ታላቅ ስኬት ነው፡፡ ዘ-ህወሀት በቀላሉ የሚሞኙትን ብቻ ሳይሆን የሚበክለው ከዚህም በተጨማሪ መንፈሰ ጠንካራ እና በቀላሉ ለመለወጥ የሚያስቸግሩትን በቀላሉ ሊድን በማይችል በሽታ እንዲለከፉ በማድረግ ሰው ከመሆናቸው እና ከብሄራዊ ስሜታቸው በላይ ለጎሰኝነት ታላቅ ትኩረት እንዲሰጡ በማድረግ የመበከል ስራውን ያከናውናል፡፡

የክልል ጎሳ መስመሮችን በማስመር ኢትዮጵያን መገነጣጠል፣

ዘ-ህወሀት የጎሳ ወሰንን በመላዋ ሀገሪቱ አስምሮ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ በቅርቡ በጎንደር እና በትግራይ እንዲሁም በተለያዩ የኦሮሞ ግዛቶች ተሰምረው በነበሩ ወሰኖች ተቃውሞዎች እና ከባድ ግጭቶች ተከስተው ነበር፡፡ ዘ-ህወሀት የእራሱን ታላቅ የከፋፍለህ ግዛ እና የብዝበዛ ዕቅዱን ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፣ አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ሁሉንም መሬት ጠቅልሎ በመያዝ ኢትዮጵያን መገነጣጠል፣

እ.ኤ.አ በ1995 የዘ-ህወሀት ህገ መንግስት እንዲህ በማለት አውጇል፣ “የገጠር እና የከተማ መሬት ባለቤትነት እንዲሁም ሁሉም የተፈጥሮ ሀብቶች በመንግስት እና በህዝቡ ቁጥጥር ስር የተያዙ ናቸው፡፡ እናም መሬት የብሄር ብሄረ ሰቦች እና የኢትዮጵያ ህዝቦች የጋራ ሀብት ነው፡፡ እናም አይሸጥም አይለወጥም“ (አንቀጽ 40 (3)

በኢትዮጵያ ውስጥ መሬት በመንግስት ብቸኛ ቁጥጥር ስር የዋለ ከሆነ በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ብቸኛ የመንግስትነት ስልጣኑን የያዘው ማን ነው? ላለፉት 25 ዓመታት በኢትዮጵያ የመንግስትነት ስልጣኑን የያዘው ማን ነው?

መሬት በኢትዮጵያ ውስጥ ለሽያጭ የማይቀርብ ከሆነ ወይም ደግሞ ለሌላ በሽያጭ የማይውል ከሆነ ዘ-ህወሀት እንዴት አድርጎ ነው ግዙፍ የሆነውን መሬት ለሱዳን እና በመቶዎች እና በሺዎች የሚቆጠረውን ሄክታር መሬት በቁርጥራጭ ሳንቲም ለሚገዙ አታላይ ኢንቨስተሮች እና የመሬት ተቀራማቾች ሊሰጥ የሚችለው?

መሬት የብሄሮች ብሄረሰቦች እና ህዝቦች የጋራ ሀብት ከሆነ ለምንድን ነው መንግስት (ፌዴራል) የጋንቤላን መንግስት ስልጣን ወደ ጎን ብሎ እስከ 300 ሺ ሄክታር የሚሆን መሬት ለካራቱሪ የሰጠው?

ዘ-ህወሀት ብቻ በኢትዮጵያ ውስጥ መሬትን በብቸኝነት የመያዝ ስልጣን አለው ምክንያቱም ሁሉንም የኢትዮጵያ መሬት ተቆጣጥሯልና፡፡

በኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ማንም መሬት መያዝ ይችላል፣ ሆኖም ግን ከዘ-ህወሀት በስተቀር የመሬት ሀብት ባለቤትነት ያለው ማንም የለም፡፡

መሬትን በነጻ ለመገበያየት የማያስችል ከህጋዊ ባለቤትነት ውጭ የተያዘ መሬት የተውሶ ልብስ ማለት ነው፡፡ አዋሹ ልብሱን በሚፈልገው ጊዜ እና እንዲመለስ በሚጠይቅበት ጊዜ ተዋሹ እርቃኑን ይቀራል፡፡

ኢትዮጵያውያን የንብረት ባለቤትነት መብት አልባዎች ናቸው! የያዙት መሬት በዘ-ህወሀት የመሬት ከበርቴዎች የተያዘ ነው፡፡

ዘ-ህወሀት ብሄሮች ብሄረሰቦች እና ህዝቦች እና ሌላም በማለት ይጠራቸዋል፡፡ ማናቸውም ቢሆኑ መሬታቸውን በባለቤትነት የያዙ አይደሉም፡፡ ዘ-ህወሀት ግን ባለቤት ነው፡፡ መሬት አልባ፣ ሀብት የለሽ እና ከጥንታዊ ዘሮቹ መሬት የተፈናቀለ ምን ማለት እንደሆነ ለማወቅ ከፈለግህ መሬታቸው እየተነጠቀ ለዓለም አቀፍ መሬት ተቀራማቾች የሚሰጥባቸውን ጋምቤላውያንን ጠይቅ፡፡

ዘ-ህወሀት በኢትዮጵያ አዲሱ የመሬት ከበርቴ ነው፡፡

የዘ-ህወሀት ንጉሶች እና መኳንንት በኢትዮጵያ ሁሉንም መሬት ተቆጣጥረዋል፡፡ ይቅርታ አድርጉልኝ፣ ሆኖም ግን እኔ በማንኛውም መልኩ በብሄር ብሄረሰቦች እና ህዝቦች እንዲሁም በሌላ እርባና የለሽ የመሬት የቂል ንግግር አልሞኝም፡፡

የመሬት ጉዳይ ሲመጣ ዘ-ህወሀት ወርቃማውን ህግ በተለያየ መልኩ በስራ ላይ ያውላል፡፡ (ወርቁን የተቆጣጠረ ይገዛል፡፡ ለዘ-ህወሀት መሬትን እና ወርቁን የያዘ ይገዛል፡፡

ሁሉም ኢትዮጵያውያን እነርሱን ከሚመግቧቸው ከዘ-ህወሀት ልሂቃን፣ ግብረ አበሮች እና ሌሎች ጥገኞች በስተቀር የገጠር የእህል ምርት ባለቤቶች ወይም የከተማ ህገወጥ ንብረት ባለቤቶች ናቸው፡፡ ከዘ-ህወሀት በስተቀር ሌላ ምንም የንብረት ባለቤትነት የለውም፡፡ ይህ የማይካድ እውነታ ነው!!! ከዚህ ጋር ስምምነት አድርጉ!!!

የዘ-ህወሀትን የሰይጣናዊ የቢዝነስ ግዛት በማስፋፋት እና ማንኛውንም አካባቢያዊ ተቃውሞ የጎሳ ግጭት በማለት ኢትዮጵያን መገነጣጠል፣

ዘ-ህወሀት በቅርቡ የአዲሰ አበባ ማስተር ፕላን እያለ በሚጠራው አካሄድ የእራሱን ቢዝነስ በወረራ፣ በመሬት ነጠቃ እና አርሶ አደሮችን በኃይል በማፈናቀል ለማስፋፋት ጥረት በሚያደርግበት ጊዜ ጣቱ በእሳት ተቃጥሎ አገኘው፡፡

ከአንድ ተኩል አስርት ዓመታት በላይ ዘ-ህወሀት ወደ 200 ሺ የኦሮሞ አርሶ አደሮችን ከመናገሻ ከተማዋ ዳርቻ አካባቢ አፈናቅሏል፡፡ በዚህ ምክንያትም ነው በቅርቡ በተቀሰቀሰው ተቃውሞ ዘ-ህወሀት በደርዘን የሚቆጠሩ መሳሪያ ያልታጠቁ ወጣት አማጺዎችን ለእልቂት የዳረጋቸው፡፡ ሂዩማን ራይትስ ዎች የተባለው ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት በተፈጸመው እልቂት ላይ ትችት በማቅረብ እንዲህ የሚል ዘገባ አውጥቷል፣ “ለኦሮሚያ ተቃውሞ የኢትዮጵያ መንግስት የሰጠው ምላሽ በርካታዎቹን ለሞት የዳረገ እና ከፍተኛ ለሆነ የእልቂት አደጋ የሚጋብዝ ነው፡፡“

ዘ-ህወሀት ያፈናቀላቸው አርሶ አደሮች ለመሬታቸው ቁርጥራጭ ገንዘቦች ይሰጣቸው እና በጥቂት ወራት ውስጥ ገንዘባቸው ያልቅና አርሶ አደሮቹ መሬታቸውን ለያዙት ለዘ-ህወሀት ጌቶች አሽከሮች እና የቀን ሰራተኞች ይሆናሉ፡፡

ዘ-ህወሀት በኦሮሚያ ክልል የሰራው የኢኮኖሚ ዘር የማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ ወንጀልን የመፈጸም ዓይነት ስራ ነው፡፡

በተባበሩት መንግስታት የምግብ እና የእርሻ ድርጅት (FAO)፣ በግብርና ልማት ዓለም አቀፍ ፈንድ (IFAD) እና በዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ልማት ተቋም (IIED) ጥናት መሰረት፡

“በኢትዮጵያ ውስጥ ለምሳሌ በመንግስት ደረጃ ለሚፈለግ ነገር የኦሮሚያ ኢንቨስትመንት ማስፋፊያ ኤጀንሲ ወደ 22 የሚሆኑ ሀሳብ የቀረበባቸው ወይም ደግሞ በእርግጠኝነት ስምምነት የተደረገባቸው ከእነዚህም ውስጥ 9 የሚሆኑት ከ1000 በላይ ሄክታር እና ከዚህም በተጨማሪ 148 የሚሆኑት በብሄራዊ ኢንቨስትመንት ማስፋፊያ ኤጀንሲ የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በመንግስት ደረጃ ያሉ በሌሎች የኢትዮጵያ ግዛቶች የሚገኙ ተጨማሪ ፕሮጀክቶች ምዝገባ የተካሄደባቸው ሲሆኑ ሌሎች ጥቂት የተገኙ መሬቶች ደግሞ ምንም ዓይነት ምዝገባ ያልተካሄደባቸው ናቸው…ለምሳሌ በኢትዮጵያ ስለመሬት መጠን መረጃ ለማግኘት የበርካታ ስምምነቶች ሀሳቦች ይቀርባሉ ወይም ደግሞ እ.ኤ.አ በ2008 የተጠናቀቀው ጠፍቷል…“

ትክክለኛውን የግብይት ባህሪ ለመደበቅ በማሰብ ዘ-ህወሀት ሊዙን እና ሽያጩን አሳንሶ ይመዘግበዋል፣ እንዲሁም በተሳሳተ መልኩ ይመድበዋል፡፡

የተባበሩት መንግስታት የምግብ እና የግብርና ድርጅት (FAO/IFAD) ዘገባ እንዲህ በማለት ግልጽ አድርጓል፣ “በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኝ ፍሎራ ኢኮፓወር/Flora EcoPower የተባለ የጀርመን የኢንቨስትመንት ኩባንያ 13000 ሄክታር መሬት ይዞ እየተንቀሳቀሰ እያለ ይህንን ቁጥር በማሳነስ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ማስፋፊያ ኤጀንሲ 3,800 ሄክታር ብቻ ተብሎ ተመዝግቧል፡፡“

ከዚህም በላይ ዘ-ህወሀት ሆን ብሎ በሊዝ የተሰጠውን መሬት በተሳሳተ መልኩ ይመድበዋል ወይም ደግሞ ባዶ እና የባከነ መሬት (በማንም ሰው ያልተያዘ ወይም ደግሞ ጫካ) በማለት ህዝብ እየኖረባቸው ያሉትን መሬቶች ለውጭ ኢንቨስተሮች የሚሰጡ መሆናቸውን ለመደበቅ ሲሉ ይሸጣሉ፡፡ የFAO/IFAD ዘገባ በተለይ እንዲህ በማለት ሁኔታውን አመላክቷል፡

“በኢትዮጵያ ውስጥ ለምሳሌ ሁሉም የሚሰጡ መሬቶች በኢንቨስትመንት ማስፋፊያ ኤጀንሲ ይመዘገቡ እና ከዚያ በፊት ማንም የማይጠቀምባቸው የባከኑ መሬቶች ተብለው ይመደባሉ፡፡ ሆኖም ግን ይህ መደበኛ ምደባ ወደ 75 ሚሊዮን የሚደርስ ህዝብ አብዛኛውም በገጠር አካባቢ የሚኖር ህዝብ ባለባት ሀገር ውስጥ እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ መፈጠሩ ለጥያቄ ክፍት ያደርገዋል፡፡ በአንድ በሀገር ውስጥ በተደረገ ጥናት በተሰበሰበ መረጃ መሰረት በቤንሻንጉል ጉሙዝ እና በአፋር ክልሎች ለኢንቨስተሮች የተመደበው መሬት ቀደም ሲል እንደቅደም ተከተላቸው ለተለዋዋጭ እርሻ/shifting cultivation እና የበጋ ወቅት የከብት ግጦሽ በማለት ተመድቦ ነበር፡፡“

እንግዲህ ለማወቅ ለሚፈልጉ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የዘ-ህወሀት የመሬት ባለቤትነት እውነታ እነዚህን የመሳሰሉ ነገሮችን ይይዛል፡፡

ሆኖም ግን ይህ ዓይነት ሁኔታ በጣም የሚያበሳጭ ነገር ነው!!! ዘ-ህወሀት ለደኃ የኢትዮጵያ ገበሬዎች እያደረገ ያለው እንደዚህ ያለ አሳፋሪ ቆሻሻ ስራ ነው፡፡ ሰዎችን ከመሬታቸው በማፈናቀል መሰረታዊ የሰው ልጆችን ክብር በመከልከል አሽከሮች እና የቀን ሰራተኞች በማድረግ የዕለት ጉርሳቸውን በማሳጣት እንቅስቃሴ ማድረግ ሙሉ በሙሉ ውዥንብር ውስጥ መግባት ማለት ነው!

ኢትዮጵያውያንን በማሰደድ ኢትዮጵያን መገነጣጠል፣

የዘ-ህወሀት ቁልፍ ስትራቴጂ የዘ-ህወሀት አባል ያልሆኑ ዜጎች ህይወት በኢትዮጵያ ውስጥ በመከራ የታጀበ እንዲሆን ማድረግ እና የቻሉ እና አቅሙ ያላቸው በሀገር ውስጥ እና በውጭ እንዲሰደዱ ማድረግ ነው፡፡

ዘ-ህወሀት በተለይም የአመራር ችሎታ ያላቸው፣ ምሁር፣ ወጣት እና ወደ መካከለኛው የአረብ ሀገሮች፣ አውሮፓ ወይም ደግሞ ሰሜን አሜሪካ በሚሰደዱ ሰዎች ላይ ዒላማውን ያነጣጥራል፡፡ ዘ-ህወሀት ሁሉንም የተማሩ እና የብሩህ አእምሮ ባለቤት የሆኑትን ኢትዮጵያውያን እና ሀገራቸውን ለቅቀው ለመሰደድ የማይፈልጉትን ኢትዮጵያውያን አስከፊውን የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ሬፐብሊክ እንዝላል ይጫንባቸዋል፡፡

ዘ-ህወሀት ተቀናቃኞቹን በእራሱ የማጎሪያ እስር ቤቶች እና የሚስጥር እስር ቤቶች በሀገር ውስጥ እንዲማቅቁ ያደርጋል፡፡ከያዝነው ወር ከሶስት ወራት በፊት አካባቢ ስደት እና የኢትዮጵያ የፖለቲካ እስረኞች በዘ-ህወሀት የማጎሪያ እስር ቤቶች በሚል ርዕስ ትችት አቅርቤ ነበር፡፡ የቀድሞው የዘ-ህወሀት የመከላከያ ሚኒስትር የነበረው ስዬ አብርሃ ሙስና በሚል የውንጀላ ክስ እ.ኤ.አ በ2008 በአምባገነኑ መለስ ዜናዊ ትዕዛዝ ለ6 ዓመታት በማጎሪያው እስር ቤት ገብቶ ሲማቅቅ የነበረው ከእስር ከተለቀቀ በኋላ በቪርጂኒያ ህዝብ በተሰበሰበበት አዳራሽ ተገኝቶ ባደረገው ንግግር እስር ቤቱ ኦሮምኛ (የኦሮሞ ቋንቋ) ይናገራል፣ እናም 99 በመቶ የሚሆኑት በቃሊቲ እስር ቤት ውስጥ የሚገኙት እስረኞች ኦሮሞዎች ናቸው በማለት ተናግሮ ነበር፡፡

በጎሳ ጥላቻ በሚነዳ የጎሳ ቡድን የአንድን የጎሳ ቡድን በጅምላ ማሰቃየት በሰው ልጆች ላይ ወንጀልን መፈጸም ማለት ነው፡፡

የዘ-ህወሀት መሬትን ለሱዳን መስጠት፣

የኢትዮጵያን ሉዓላዊ ግዛት በጠራራ ጸሐይ በሌብነት አሳልፎ ለባዕድ የመስጠት ታሪካዊ ቅሌት በሚገባ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡

እ.ኤ.አ ግንቦት 2008 አሁን በህይወት የሌለው አምባገነኑ መለስ ዜናዊ በጣም ግዙፍ የሆነ የኢትዮጵያን ሉዓላዊ የመሬት ግዛት ለሱዳን አሳልፎ ለመስጠት ዝግጅቱን በሚያደርግበት ጊዜ ታላቅ ተቃውሞ በማቅረብ ሞግቸው ነበር፡፡ (ለሱዳን ሊሰጥ ታስቦ የነበረውን አካባቢ እዚህ ጋ በመጫን መመልከት ይችላሉ፡፡) ዘ-ህወሀት ሊሰጥ የታሰበውን የሚስጥር መሬት ፍጹም በሆነ መልኩ በሚስጥር ስለሚይዝ የትኛው የመሬት ክፍል ለሱዳን እንደተሰጠ በእርግጠኝነት ለመወሰን አስቸጋሪ ነው፡፡

እ.ኤ.አ ግንቦት 11/2008 የዘ-ህወሀት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከኢትዮጵያ ተቆርሶ ለሱዳን የተሰጠ ምንም ዓይነት መሬት የለም በማለት ሙልጭ አድርጎ በመካድ መግለጫ ሰጥቶ ነበር፡፡ ያ መግለጫ ሜዲያውን እና ኃላፊነት የማይሰጣቸው ያላቸውን የውጭ ኃይሎች ፍርሀት በመፍጠር እና ያልሆነውን ነገር እንደሆነ አድርገው የሚያቀርቡ በማለት ከሷቸው ነበር፡፡ ሆኖም ግን የሱዳን ባለስልጣኖች ከኢትዮጵያ ሉዓላዊ ግዛት ያገኙትን መሬት በተናገሩ ጊዜ መለስ ዜናዊ በሚስጥር ስምምነቱ ላይ ክዳን ማስቀመጥ አልቻለም ነበር፡፡ እናም የእርሱ ግብርአበሮች በግንቦት ወር አጋማሽ አካባቢ ወደኋላ በመመለስ መተረክ ጀመሩ፡፡ በድንበሩ አካባቢ ድንበር የማመላከት የቅድመ ዝግጅት ስራ ብቻ ነው የተከናወነው በማለት ተናገሩ፡፡ እናም ምንም የተጠናቀቀ ነገር የለም ብለው ነበር፡፡ ይህን ባሉበት በቀናት ጊዜ ውስጥ አዲስ ውሸት ተፈበረከ፡፡ እናም ስምምነቱ በንጉሱ እና በደርግ ጊዜ ከሱዳን ጋር የተደረገውን ስምምነት ነው እየተገበርን በማለት ባልተለያያ መልኩ አመኑ፡፡

የኢትዮ-ሱዳን የድንበር ጉዳዮች ኮሚቴ ጉዳዩን ጠንካራ በሆነ መልኩ አንስቶ በእርግጠኝነት በወሰኑ አካባቢ ምን እየተደረገ እንዳለ እና በአምባገነኑ መለስ ዜናዊ መሬታቸውን ተነጥቀው በመሰቃየት ላይ ያሉ ዜጎችን ጉዳይ በአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው ፕሮግራም እና በሌሎች ዓለም አቀፍ የዜና አውታሮች ቃለ መጠይቅ በማድረግ ማጣራት በጀመረበት ጊዜ የመለስ ዜናዊ የግመዳ ማሽን እንደገና ድምጹን ቀይሮ ቀረበ፡፡ የጥቃቱ ሰለባ የነበሩ ሰዎች በሱዳን ኃይሎች እየተወረሩ ቀደምት አባቶቻቸው እና አያቶቻቸው ሲኖሩበት ከነበረው አካባቢ በኃይል እየተባረሩ መውጣታቸውን የሚገልጹ የመረሩ ቅሬታዎቻቸውን ማሰማት ጀመሩ፡፡ የእርሻ ማሽነሪዎች እና ሌሎች የመገልገያ መሳሪያዎቻቸው በሱዳኖች እንደተወረሱባቸው እና በርካታ ኢትዮጵያውያን በቁጥጥር ስር እየዋሉ በሱዳን እስር ቤቶች እንዲታሰሩ ተደርገዋል፡፡

እ.ኤ.አ ግንቦት 21/2008 መለስ ዜናዊ በይፋ ከሱዳኑ አል ባሽር ጋር ያደረገውን ስምምነት እንዲህ በማለት በይፋ ግልጽ አድርጓል፡

“እኛ፣ ኢትዮጵያ እና ሱዳን ከድንበር ማካለሉ ተጠቃሚ ለመሆን ከሁለቱም ወገን አንድም ሰው እንዳይፈናቀል ስምምነት ፈርመናል…እ.ኤ.አ በ1996 በወረራ የተያዘውን መሬት መልሰን ሰጥተናቸዋል፡፡ ይህ መሬት እ.ኤ.አ ከ1996 በፊት የሱዳን ገበሬዎች ይዞታ ነበር፡፡ በጥቂት መገናኛ ብዙሀን እንደሚናፈሰው ሳይሆን በድንበሩ አካባቢ አንድም የተፈናቀለ ሰው የለም“ ብሎ ነበር፡፡

በዊኪሊክስ ግንኙነት አምባሳደር ዶናልድ ያማማቶ የሰበሰቧቸውን መረጃዎች እና ስምምነት የተደረገ ስለመሆኑ እንዲህ የሚል ማጠቃለያ አቅርበው ነበር፣ “መረጃ ሰጨው ከዚህም በተጨማሪ የአማራ ክልል ግዙፍ የሆነ ግዛቱን በማጣቱ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ እና በሱዳን መካከል ውጥረቱ ቀጥሎ እንደሚገኝ፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ መንግስት ውጥረቱን ለማርገብ እየሰጠው ያለው መልስ ሌላ ውጥረቱን የሚያባብስ እና አመጸኞችን የሚገፋፋ ሆኗል“ (አጽንኦ ተጨምሯል፡፡)

እ.ኤ.አ በ2001 ለድንበር ማካለሉ የተሰጡት ምክንያቶች ፍጹም የተለዩ ነበሩ፡፡

በወቅቱ የነበረው የሱዳን አገዛዝ የድንበር ማካለሉ የአል ቃዳሪፍን እና በሰሜን ኢትዮጵያ የምትገኘውን የትግራይን ክልላዊ መንግስት ለማልማት እና ለማስተሳሰር ጠቃሚ ነበር በማለት ግልጽ አድርጎ ነበር…አል ቃዳሪፍ የሱዳን የዳቦ ቅርጫት በመሆን ሁለቱ ቀጣናዎች በግብርና ምርታማ ነበሩ…በአሁኑ ጊዜ ከአል ቃዳሪፍ እስከ መቀሌ ድረስ የተዘረጋው መንገድ እየተጠገነ እና ደረጃውም ከፍ እንዲል እየተደረገ ነው…የትግራይ ክልላዊ መንግስት ወደ ቀይ ባህር የሚያገናኝ መንገድ ስለሚኖር ተጠቃሚ የሚያደርጋት ሲሆን በአል ቃዳሪፍ የሚያልፈው መንገድ ደግሞ ከሱዳን ወደብ ጋር የሚያገናኛት ይሆናል፡፡ ከዚህ አንጻር ፖርት ሱዳን ከኤርትራው ወደብ ከአሰብ ወይም ደግሞ በሶማሌ ከሚገኛው የበርበራ ወደብ ይልቅ ለመቀሌ ቅርብ ይሆናል…”

ዓይን ያወጣ የመሬት ነጠቃ እንደ ቀጣና የኢኮኖሚ ልማት ዕቅድ በመውሰድ ድብቅ ሚናውን መጫወት ጀመረ፡፡ ዘ-ህወሀት ብቻ እንደዚህ ያለውን እርባናቢስ ትረካ በማቅረብ ለመታመን እንዲችል ይጠብቃል፡፡

እ.ኤ.አ ታህሳስ 2013 የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ካርቲ በኢትዮጵያ እና በሱዳን ያሉ አገዛዞች በድንበር ማካለሉ ጉዳይ ላይ ያላቸውን ስምምነት አጠናቀዋል በማለት እንዲህ ብሎ ነበር፡

“ሱዳን እና ኢትዮጵያ በፋሻጋ አካባቢ ያለውን ያለመስማማት ያጠናቀቁት መሆናቸውን የሱዳን ሚኒስትር አረጋግጧል፡፡ ሁለቱ ፕሬዚዳንቶች የመጨረሻውን ድንበር በማካለል ታሪካዊ የሆነ ሰነድ ይፈርማሉ፡፡ ሁለቱ ፕሬዚዳንቶች ከዚህም በተጨማሪ ሱዳን ቀደም ሲል ስትቃወመው መነበረው ባወዛጋቢው የህዳሴ ግድብ ላይ ስምምነት አድርገዋል፡፡“ (አጽንኦ ተደርጓል፡፡)

ስለሆነም አሁን እውነተኛውን ስምምነት አወቅን፡፡ ግርድፉ ስምምነት በዘ-ህወሀት አሳቢነት ለኢትዮጵያ ተሰጥቷል፡፡

እ.ኤ.አ በ2016 ዘ-ህወሀት ቀደም ሲል ተቃውሞ ስታሰማ ለነበረችው ለሱዳን የህዳሴ ግድቡን ግንባታ እንድትደግፍ ለዚህ ውለታዋ በለውጥ 725 ከ/ሜ ርዝመት ያለው 600 ሺ ሄክታር የኢትዮጵያን መሬት ያስረክባል፡፡

ይሁዳ ለ30 ዲናር ሲል ኢየሱስን ከድቷል፡፡ ኢትዮጵያም የህዳሴ ግድብ እየተባለ ለሚጠራ የቅንጦት ግድብ ተከድታለች፡፡

ዘ-ህወሀት ለሱዳን መሬት በማደል ያደረገው ድርጊት የዓባይን ወንዝ መሸጥ የሚል አዲስ የትርጉም ገለጻ ያሰጠዋል፡፡

ዘ-ህወሀት በዓባይ ወንዝ ላይ በሚቀዝፍ እና ምንም ዓይነት መሪ በሌለው በሚያፈስ ጀልባ ኢትዮጵያን ሸጣት፡፡ (ምንም ዓይነት ቀልድ አይደለም፡፡)

አምባገነኑ መለስ ዜናዊ እ.ኤ.አ በ2008 እና በአሁኑ ጊዜ ዘ-ህወሀት (ኃይለማርያም ደሳለኝ? ናሙናው: እርሱ ማን ነው?) በትክክል የተፈረመውን የሚስጥር ስምምነት ሚስጥር አድርገው ይዘዋል፡፡

ሆኖም ግን የመለስ ይፋ መግለጫ በመሰረታዊ ስምምነት ሁኔታ እና በስምምነቱ ሚስጥራዊ ባህሪ ላይ ጠቃሚ የሆነ መረጃ ይሰጣል፡፡

ከመለስ መግለጫ በኋላ በአሁኑ ጊዜ በእርግጠኝነት የተፈረመ ስምምነት እንዳለ አውቀናል፡፡ በግልጽ ለመናገር ይኸ ማለት ዝርዝር ጉዳዮችን እና ሁኔታዎችን የሚያመላክት ግልጽ የሆነ የስምምነት ሰነድ እንዳለ የሚያመላክት ነገር ነው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ስምምነቱ በእራሱ በመለስ ወይም ደግሞ በእርሱ ስም እንዲፈርም ስልጣን በተሰጠው ሚኒስትር እንደተፈረመ ለማወቅ እንችላለን፡፡

የስምምነቱን ዝርዝር የይዘት ሁኔታ ከማወቅ አንጻር ዜናዊ በርካታ ጉዳዮችን በካተተ መልኩ እንዲፈረም ተደርጓል፡፡ ይኸውም፡

1ኛ) በተሰጠው መሬት ላይ ያሉ ሰዎች ያለመፈናቀል ጥያቄ፤

2ኛ) በድንበር ማካለሉ ስራ ላይ ጉዳት የደረሰባቸው ጥቅሞች እንዲጠበቁ የማድረግ፣

3ኛ) ቀደም ሲል በኢትዮጵያ አርሶ አደሮች በህገ ወጥ መልክ ተይዟል በተባለው መሬት ላይ የሱዳን አርሶ አደሮች ይዞታ እንዲሆን እና የይዞታ መብታቸው እንዲጠበቅ ማድረግ፣ እና

4ኛ) እ.ኤ.አ በ1996 በኢትዮጵያ ተወስዶ የነበረውን መሬት እንደገና መልሶ ለሱዳን መስጠት የሚሉት ናቸው፡፡

ዜናዊ ከአል ባሽር ጋር የፈረመው ስምምነት እ.ኤ.አ በ1902 ከተፈረመው እና የግዌን ላይን እየተባለ ከሚጠራው ስምምነት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌለው መሆኑን መገንዘብ ጠቃሚ ነገር ነው፡፡ እንደዚሁም ሁሉ እ.ኤ.አ ከ1974 በፊት በንጉሱ ወይም ደግሞ እ.ኤ.አ በ1975 እና በ1991 መካከል በደርግ ከተረቀቁት ወይም ከተፈጸሙት የድንበር ማካለል ወይም ሰፈራ ስራዎች ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የለውም፡፡ የዜናዊ ስምምነት በተለይ እ.ኤ.አ ከ1996 ጀምሮ በዜናዊ አገዛዝ የሱዳን መሬት ላይ ወረራ ከተደረገ በኋላ ከድንበር ማካለል ጉዳዮች እና ከተዛማጅ ነገሮች ጋር የተያያዘ ነበር፡፡

በመለስ ዜናዊ የተፈረመው ስምምነት የኢትዮጵያን አንጡራ መሬት ለሱዳን ለመስጠት በእራሱ በመለስ ዜናዊ ብቻ የተደረገ ስምምነት ነው፡፡ ይኽ ቀላል እና ምንም ዓይነት ውዝግብ ሊፈጥር የማይችል እውነታ ነው!

እ.ኤ.አ ጥር 2016 በሱዳን እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን የድንበር ማካለል ስራ የካርታ ስራ መስራት እንዲችል የቴክኒክ ኮሚቴ የተቋቋ መሆኑ ተነግሮናል፡፡ በመሬት ላይ ያለውን ስራ በዚህ ዓመት ያጠናቅቀዋል ተብሏል፡፡

የዘ-ህወሀት የደናቁርት ስብስብ በዓለም ላይ ከማንም በላይ እነርሱ ብልሆች እንደሆኑ አድርገው እንደሚያስቡ እውነታውን አውቃለሁ፡፡ እነርሱ ከማንም የሚበልጡ፣ የሚያስቡ፣ የሚያታልሉ፣ የሚያጭበረብሩ እና ማንንም በዝረራ እንደሚያሸንፉ አድርገው ያስባሉ፡፡ ይህ ጉዳይ በእነርሱ የአስተሳሰብ ጓዳ ውስጥ እውነት ሊሆን ይችላል፡፡ ሆኖም ግን እንደምንመስላቸው ደደቦች አይደለንም፡፡

የዘ-ህወሀት መሪዎች የኢትዮጵያን መሬት ለሱዳን በመስጠት 100 ሚሊዮን የሚሆነውን ህዝብ እናታልላለን ብለው የሚያምኑ ከሆነ በእርግጠኝነት እንደገና ወደ ኋላ መለስ ብለው ማሰብ ይኖርባቸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የግዛት ሉዓላዊነት ላይ ስለሚፈጽሙት ወንጀል እስከ ንኡስ የአቶም ክፍል ድረስ ጠልቆ በሚደረግ የቀዶ ጥገና ምርመራ ያህል ለማሰብ እና ለመተግበር የተዘጋጀን መሆናችንን ሊገነዘቡት ይገባል!

ዘ-ህወሀት ከሱዳን ጋር የሚያደርገው ስምምነት ወይም ደግሞ አጋርነት ወረቀቱ የተጻፈበትን ያህል ዋጋ የማያወጣ እርባና ቢስ ጉዳይ ስለሆነ ስለህጋዊነት ቅድመ ሁኔታ የምደግመው ጉዳይ አይኖርም፡፡ 

ስለተወረሩት የምዕራብ ኢትዮጵያ ግዛቶች ጆሮ ዳባ ልበስ መባል እና ስለሕግ መከላከል የቀረበ የተማጽዕኖ ጥሪ፣

እ.ኤ.አ ወደ 2008 መለስ ብለን ስንመለከት ለኢትዮጵያ እናት ሀገር እጆቻችንን እንድናስተባብር ፍላጎት ላለን ለሁሉም የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያዎች፣ ምሁራን፣ ተመራማሪዎች እና ለሌሎች ለሁሉም ዜጎች የተማጽዕኖ ጥሪ አቅርቤ ነበር፡፡ ሰፊ መሰረት ያለው ስራ እንዲሰራ እና እውነታውን በሕግ ምርምር በማካሄድ ምንም ይሁን ምን የዜናዊን የሚስጥር ስምምነት ለማክሸፍ የሕግ መከላከል ኮሚቴ እንዲቋቋም ጥሪ አቅርቤ ነበር፡፡

ጥሪዬ ግን ጆሮዳባ ልበስ ተባለ፡፡

ይህንን ጥሪ ያስተላለፍኩት ከ8 ዓመታት በፊት ነበር፡፡ አሁንም እንደገና በድጋሜ እለዋለሁ፡፡ ሁሉም የድንበር ማካለል የሸፍጥ ስራ በአምባገነኑ መለስ እና በእርሱ ወሮበላ አጋሮች የተፈበረከ ነው፡፡ እውነተኛው ስምምነት እ.ኤ.አ በ2008 የተደረገ ነው፡፡ መለስ፣ ፈርሞ፣ አትሞ እና ግዙፍ የሆነውን የአማራ ክልል ግዛት መሬት ለሱዳን በመስጠት ምንም ነገር እንዳልተደረገ ለማስመሰል ጥረት ሲያደርግ እንደቆየ ምንም የሚያጠያይቅ ነገር የለውም፡፡ የኢትዮጵያን መሬት ለመውሰድ ዘ-ህወሀት እና ሱዳን ያደረጉትን የወንጀል ስምምነት ንቁ ሆነን በመዘጋጀት በሕግ፣ በፖለቲካ እና በማንኛውም ነገር ሁሉ የሸፍጥ ስምምነቱን መገዳደር ይኖርብናል፡፡

ዘ-ህወሀት በሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች ከሁሉም ዓይነት ጠንካራ ተቃውሞዎች እና መገዳደሮች የህዝቡን ቀልብ ለማስቀየስ በአሁኑ ጊዜ ከሱዳን ጋር ያደረገውን ስምምነት ሳይወድ በግድ ግልጽ ያደርጋል ብየ አስባለሁ፡፡

እ.ኤ.አ በ2016 ዘ-ህወሀት እና ሱዳን ድራማውን እንደገና ዝርዝር የፖለቲካ ድራማ ለመቀጠል በመድረክ ላይ ሆነው ሙዚቃውን እና ዳንሱን በማቅለጥ ላይ ይገኛሉ፡፡ ዘ-ህወሀቶች የህዝብን ቀልብ በማስቀየስ የተካኑ ናቸው፡፡

ለማለት የምፈልገው ነገር፣ ምንም ሆነ ምን…!

“ኢትዮጵያ ትነሳለች”

የዘ-ህወሀት አጉረምራሚ ድምጾች ሁልጊዜ እንዴት ዘ-ህወሀትን እንደምጠላ ወዘተ… ወዘተ… ለመባረቅ ከአፋቸው ላይ እንደደረሱ እርግጠኛ ነኝ፡፡

የነጻነት የስነ መለኮት እና የማህበራዊ አክቲቪስት ቶማስ ሜርቶን በአንድ ወቅት እንዲህ ብለው ነበር፣ “የእውነት ብርሀን በስሜታዊነት እና በፍርሀት ማዕበል ብትናወጥም በቤት ውስጥ ያለምንም ማቋረጥ በጥልቀት ብርሀኗን ትሰጣለች፡፡“

እውነታው ፍርጥርጥ ብሎ ሲታይ የዘ-ህወሀት ቤት በስሜታዊነት እና በፍርሀት ማዕበል በመናጥ ላይ ይገኛል፡፡

እነደዚሁም ሁሉ ምንም ዓይነት ጠቀሜታ የሌላቸው ጥቂት ነገሮች እንደሚኖሩ አምናለሁ፡፡

በስልጣን ላይ እውነትን እንዲናገሩ፣ ስልጣናቸውን ከሕግ አግባብ ውጭ እንዳይጠቀሙ እና በስጣን እንዳይባልጉ ከ10 ዓመታት በፊት ጀምሬ ስናገር ቆይቻለሁ፡፡ ይህንን ማድረግ አለብኝ ምክንያቱም ኤሊ ዌይሰል በአንድ ወቅት እንዲህ በማለት ተናግረዋልና፣ “ኢፍትሀዊነትን ለመከላከል ኃይል የለሾች የምንሆንበት ጊዜ አለ፣ ሆኖም ግን ለመቃወም ጊዜ የምናጣበት ሁኔታ በፍጹም ሊኖር አይገባም፡፡“

እውነት ተናጋሪነት ድምጽ ለሌላቸው የኢፍትሀዊነት ሰለባዎች የመቆም እውነተኛ ድርጊት ነው፡፡

ለዘ-ህወሀት ኢፍትሀዊነት ሰለባዎች ድምጽ ነኝ፡፡ እ.ኤ.አ በ2005 በአምባገነኑ መለስ እልቂት ለተፈጸመባቸው ወገኖቻችን እ.ኤ.አ በ2016 የሚናገርላቸው ማን ነው?

ሆኖም ግን ስለሰለባዎች ጉዳይ ብቻ አይደለም፡፡ ስለኢትዮጵያ የግዛት አንድነት መጠበቅ እና መከላከል ጉዳይ ብቻም አይደለም፡፡

ይልቁንም ጉዳዩ ስለሰው ልጆች ክብር እና ስለኢትዮጵያ ህዝብ ሰብአዊ መብት ጥበቃ ጉዳይ ነው፡፡

ይልቁንም ኢትዮጵያ ስለመነሳቷ ወይም ደግሞ ስለመውደቋ እና ለዘላለም በወሮበሎች መዳፍ ስር ወድቃ ስትደቆስ ስለመኖሯ ጉዳይ ነው፡፡

ክዋሜ ንክሩማህ ከበርካታ አስርት ዓመታት በፊት እንዲህ በማለት በግጥም ስንኞች አውጀው ነበር፣

ኢትዮጵያ ትነሳለች፣
ጠላቶቿን ታመክናለች፡፡

የአፍሪካዋ ቀንዲል፣
የብዙህን መድብል፣
የጀግናዎች አክሊል፣
የሰማዕታት ገድል፣

የታሪክ አሻራ፣
የስልጣኔ አውራ፣

የሰው ዘር መገኛ፣
የሌባ መጋኛ፣
የነጻነት ዳኛ፣
የደባ ቀበኛ፡፡

እማማ ኢትዮጵያ፣
እሳት የቀን ቋያ::

ኮርታ ተኮፍሳ፣
አረንጓዴ ለብሳ፣
በውበት ተነቅሳ፣
ለከፋው አልቅሳ፣

ለታረዘ አልብሳ፣
ለተራበ አቅምሳ፡፡

የዓባይ ወንዝ መመንጫ፣
የአራዊት መፈንጫ፣
የወፎች መንጫጫ፣
የባለጌ መቅጫ፣

የጨዋዎች ዋንጫ፡፡
ኢትዮጵያ ትነሳለች፣

ጠላቶቿን ታወድማለች፣
ወዳጆቿን ታኮራለች፣
ድህነትን ታጠፋለች፣
በሳይንሱ ትረቃለች፣

ወደ ህዋ ታመጥቃለች፡፡
የብልሆች ሀገር አንቺ ኢትዮጵያ፣

የደፋሮች ምድር የአናብስት መዋያ፣
የአፍሪካዋ ኩራት የጥቁሮች መታያ፣
የጥንታዊ ታሪክ ባለቤት መፍለቂያ፣
ምግባረ ጠንካራ ስምሽ አቢሲኒያ፡፡

በትምህርት የለማች፣
ባህል ያዳበረች፣
ላፍሪካ ያደረች፣
ብልኋ ኢትዮጵያ ነገ ትነሳለች፡፡

የአፍሪካዋ እመቤት፣
የተስፋ ባለቤት፣
ባለዕድል ነባቢት፣
ነገ ትነሳለች፡፡

ትግራውያን ከመሆናችን በፊት በመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ እንደሆንን አምናለሁ፡፡ ኦሮሞ ከመሆናችን በፊት በመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ነን፡፡ አማራ ወይም ደግሞ ሌላ የማንኛውም የጎሳ ቡድን አባላት ከመሆናችን በፊት ኢትዮጵያዊ ነን፡፡

ኢትዮ-አሜሪካዊ ወይም ደግሞ ኢትዮ-አውሮፓዊ ከመሆናችን በፊት ኢትዮጵያዊ ነን፡፡

እኛን በሰንሰለት አስተሳስሮ ለያዘን በጠንካራዎቹ እሴቶቻችን ማለትም- ለሰብአዊ መብት ጥበቃ፣ ለነጻነት ፍቅር፣ ለዴሞክራሲያዊ ተቋማት ግንባታ እና ከሁሉም በላይ ደግሞ ለእናት ሀገር ኢትዮጵያ የግዛት አንድነት እና በማይከፋፈለው የኢትዮጵያ ህዝብ ዙሪያ እንሰባሰብ

በእነዚህ እሴቶች አማካይነት ለመተባበር ስምምነት ካደረግን በምድር ላይ እኛን፣ ለመበታተን፣ ለማሸነፍ፣ ለመከፋፈል የሚችል ምድራዊ ኃይል ሊኖር ይችላልን?

ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሄር ትዘረጋለች እናም ጠላቶቿ ይወድቃሉ!

የእኔ መርህ ቀላል ነው፡ ዛሬ አንድ ኢትዮጵያ፡፡ ነገ አንድ ኢትዮጵያ፡፡ ለዘላለም አንድ ኢትዮጵያ፡፡

ይህንን ያለማቅማማት ተግብሩት!!!

=========================

ተዛማጅ ትችቶች፡

ኢትዮጵያ፡ ግዙፍ የሆነ ግዛቷን ያጣች ሀገር?

http://www.pambazuka.net/en/category.php/comment/76244

ኢትዮጵያን ከመክተፊያ ቢላዋ መጠበቅ http://ecadforum.com/2014/02/03/saving-ethiopia-from-the-chopping-block/

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!         

ጥር 30 ቀን 2008 ዓ.ም