ፕሬዚደንት ሬጋን ሲያራምዱት በነበረው በስደተኝነት እና በፖለቲካ ጥገኝነት ፖሊሲ ላይ ትክክል ነበሩን?

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም    

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

Reaganከቅርብ ጊዜ ወዲህ ስለሬፐብሊካኖች እና ስለሚያራምዷቸው ድምጸቶች ስናገር ቆይቻለሁ፡፡ አንዳንዶች በሬፐብሊካኖች እና በሬፐብሊካን ፓርቲ ላይ ከፍተኛ የሆነ ንዴት ያደረብኝ እንደሆነ አድርገው ሊገምቱ ይችላሉ፡፡

እኔ ስለእዚህ ጉዳይ ብዙም አልጨነቅም፡፡ ይልቁንም ከዚያ በበለጠ መልኩ በመጋዘኔ ውስጥ የ”ዴሞክራሲ አይጦች” አገዛዝ ተንሰራፍቶ ይገኛል፡፡

ሆኖም ግን በአሁኑ ጊዜ ለዕጩ ፕሬዚዳንታዊነት ምርጫ በመወዳደር ወደ ኋይት ሀውስ ለመግባት አሰፍስፈው የሚጠባበቁትን 17 (?) የሬፐብሊካን ፓርቲ ስብስቦች ዶናልድ ትሩምፕን እና ቤን ካርሰንን ጨምሮ በምመለከትበት ጊዜ ሁሉም ስብስቦች “5150’d“ የተባለው የእመሮ ህከምና እንዲሰጣቸው ሀሳብ አቀርባለሁ፡፡ (ይህም ማለት የካሊፎርኒያ የደህንነት እና የተቋሞች ድንጋጌ ክፍል በሆነው ሕግ እራሱን መቆጣጠር ለማይችል የአዕምሮ በሽተኛ ሆኖ በእራሱ ወይም ደግሞ በሌሎች ሰዎች ላይ አደጋ ሊያስከትል ለሚችል ዕብድ መቆጣጠሪያ እንዲሆን የወጣ የሕግ ሰነድ ነው፡፡)

አንድ ችግር ብቻ አለ፡፡ ይኸውም፡ እንዴት አንድ “5150“ የተባለው ኮድ ዓለም አቀፋዊ የነርቭ ቀዶ ጠጋኝ ሐኪም ሊሆን ይችላል? (ዶ/ር  ቤን  ካርሶንን ማለት ነው።)

ቀልደኛው እና አስቂኙ ትሩምፕ (ቂሉ አላልኩም) ያልተጠበቀው የሬፐብሊካን ፓርቲ የምርጫ ካርድ ሊሆን አይችልምን?

እውነት ለመናገር ትሩምፕ ለሬፐብሊካን የውሸት እጭ ማስረጃ ሊሆን አይችልምን?

ትሩምፕ ስለኋይት ሀውስ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንቅስቃሴ ከማወጁ በፊት ከታላቁ ቢል ክሊንተን ያነጋገራል።

ታላቁ ቢል ክሊንተን ሲጠየቅ እንዲህ አለ፣ “እኔ ከዚያ ሰው ጋር የፖለቲካ ግንኙነት የለኝም፡፡“

ትሩምፕ ሬፐብሊካንን በተወሰኑ በሂላሪ ክሊንተን ቡድን አባላት ከመመታት የሚያድን የሬፐብሊካን ታላቁ ተስፋ (ታላቁ ቂል አላልኩም) ነውን? ወይም ደግሞ ቤርኔ ነውን?

በቀጥታ በመናገር የሚታወቀውን አጎት ጆ ባይደንን እመርጣለሁ፡፡

የኦባማ የጤና ክብካቤ ሕግ በተፈረመበት ወቅት ጆ ለኦባማ እንዲህ በማለት በጆሮው ሹክ ብሎት ነበር፣ “ይኸ ታላቅ ነገር እኮ ነው“ አለው በዘይቤ።

ይኸ ግዙፍ ለሕዝብ ጠቃሚ ድንጋጌ ነው፡፡ የኦባማን የጤና ክብካቤ ስምምነት መቀበል! (ኦባማ ማለፍያ ነገር አድርግዋል፡፡ )

ያም ሆነ ይህ…

አሁን ስለዚያ እርባናየለሽ ነገር ለማውራት አይደለም የምጽፈው ያለሁት፡፡ ያ ባለፈው ሳምንት ተግባራዊ ሆኗል፡፡

ስለኦባማ ለበርካታ ዓመታት ተናግሪያለሁ፡፡

ስለሂላሪ ክሊንተን? ገና አለ ብዙ የሚወጣ!

ሁልጊዜ ስለው እንደነበረው…

ሬፐብሊካኖች ትርጉም ያለው ንግግር ባንድ ጊዜ በማድረግ የአነጋገር ለዛን የተላበሰ ዲስኩር ሲያሰሙ የነበረበትን ጊዜ አስታውሳለሁ፡፡

እ.ኤ.አ በ1988 ሞስኮ ላይ ተደርጎ በነበረው የዩኤስኤስአር- ዩኤስኤ ጉባኤ ላይ ሮናልድ ሬጋን የዓለም አቀፉን ፖለቲካ አቀራረብ ግልጽ በሆነ መልኩ እንዲህ በማለት ተናግረው ነበር፡ “ስለቀዝቃዛው ጦርነት የእኔ ስትራቴጂ ይህ ነው፡ እናሸንፋለን፣ እነርሱ ይሸነፋሉ፡፡“

እ.ኤ.አ በ1991 “አሸነፍን! አሸነፍን“ በማለት ደረታቸውን ደለቁ፡፡

ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በቤል ኤር ካልፎርንያ ነበር የሚኖሩት፡፡

ለዚህ አባባል የሚካኤል ጎርባቾቭ ምላሽ እንዲህ የሚል ነበር፡ “የሶቬት ህዝቦች የተሟላ እና ጊዜ ሳይወስድ አሁኑ ዴሞክራሲን ማጣጣም ይፈልጋሉ፡፡ ዓለም በአሁኑ ወቅት አምባገነንነትን ወይም የበላይነትን አትፈልግም፡፡“

የእኔ ጀግና!

ይቀጥሉ ጎረባቾቭ ይቀጥሉ!

ጎረባቾቭ የማርክሲስቶችን ካባ የደረቡ ሬፐብሊካን ነበሩን?

ለግንዛቤ ያህል፤ 

እኔ በቀዝቃዛው ጦርነት ጊዜ ሬጋን ስለተቀዳጁት ድል ለመናገር ፍላጎቱ የለኝም፡፡

እኔ ለመናገር የምፈልገው ስለሬጋን የስደተኞች እና ስለፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎች ፖሊሲ ጉዳይ ነው፡፡

እ.ኤ.አ በ1981 የነበረውን ሁኔታ መለስ ብለን ስናስበው ሬጋን ስለስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎች የነበራቸው ፖሊሲ ትክክል ነበርን?

(በአሁኑ ጊዜ ለባራክ ኦባማ ስለዚሁ ፖሊሲ ጉዳይ ትክክል ስለመሆን አለመሆኑ ጉዳይ የማቀርበው ጥያቄ የለም፡፡)

21ኛው ክፍለ ዘመን የዓለም አቀፍ ሰላም የሚከበርበት፣ በህዝቦች መካከል መግባባት የሚደረግበት እና የፍቅር ዘመን እንደሚሆን ተስፋ አረግ ነበር።

በ20ኛው ክፍለ ዘመን ህልቆ መሳፍርት በሌላቸው ጦርነቶች ምክንያት በርካታ ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎች የፖለቲካ ጥገኝነትን በመጠየቅ እየተሰቃዩ እና ሰብአዊ መብቶቻቸውን ተገፍፈው ከቆዩ በኋላ በ21ኛው ክፍል ዘመን መግቢያ ላይ ነገሮች ሁሉ እየተቀየሩ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብዬ አስባለሁ፡፡

ዓለም እንዴት ባለ የተሳሳተ መንገድ ላይ ትጓዝ እንደነበር እገነዘባለሁ፡፡

ከዚያ ወዲህ የማውቀው ነገር ምንድን?

ሀሳባዊ ኢትዮጵያዊ! እኔ!

በአሁኑ ጊዜ ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ መልኩ እኔ የማውቀው ነገር ቢኖር የ21ኛው ክፍለ ዘመን የመጀመሪያዎቹ ሁለት አስርት ዓመታት የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎች ዘመን፣ የስደተኞች፣ የተፈናቃዮች፣ የመርከብ አደጋ ሰለባዎች፣ የብቸኞች፣ የጀልባ ሰዎች፣ የተነቀፉ፣ የመንግስት አልባዎች እና የስደተኛ ሰራተኞች ዓመታት መሆናቸዉን ነው።

በየዕለት በሺዎች ባይሆንም በመቶዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን በመካከለኛው ምስራቅ እና በአውሮፓ የተለያዩ ሀገሮች ጥገኝነት ለመጠየቅ በባህር ላይ እያቋረጡ ይጓዛሉ፡፡

ይኸ ድርጊት ልቤ እንዲሰበር እና ስሜቴም እንዲጎዳ አድርጓል!

በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ዜጎች እራሳቸውን “የአፍሪካ መሪዎች” እያሉ ከሚጠሩ ደም በጠማቸው ወሮበላ ዘራፊ አምባገነኖች መዳፍ ስር ከመኖር ይልቅ በባህር ውስጥ የመስመጥ አደጋን መርጠዋል፡፡

ምን ዓይነት አሳፋሪ ነገር ነው ወገኖቼ!

ምን ዓይነት አሳፋሪ ጉድ ነው!

እ.ኤ.አ ሚያዝያ 2015 30 ሰላማዊ ወጣት ኢትዮጵያውያን ሊቢያ ጥገኘነት ጠይቀው ባሉበት ሁኔታ አይኤስአይኤል/ISIL በተባለው ጨካኝ አሸባሪ ቡድን አንገታቸውን እየተቀሉ እንዲያልቁ ተደርገዋል፡፡

እ.ኤ.አ ሕዳር 2013 ወደ 150 ሺ አካባቢ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን ስደተኛ ሰራተኞች በሳውዲ አረቢያ ፖሊሶች፣ የደህንነት ኃላፊዎች፣ ዱርየዎች እና ወሮበሎች እንደ ዱር አራዊት እየታደኑ ሰብአዊ መብቶቻቸው እንዲደፈጠጡ እና ግድያም እንዲፈጸምባቸው ተደርገዋል፡፡ አብዛኞቹ ድብደባ እና የማሰቃየት ድርጊቶች ተፈጽመውባቸዋል፣ ጥቂቶች ደግሞ ተገድለዋል፡፡ ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ ከሳውዲ አረቢያ እንዲባረሩ ተደርገዋል፡፡

ስለእነዚህ ዜጎች ማንም ብዙ ሲናገር የሰማሁት የለም፡፡

ለዚህም ነው መሰለኝ ስለእነዚህ ወገኖቻችን እኔ ከእራሴ እየተናገርሁ ያለሁት፡፡

የሳውዲ አረቢያ መንግስት በወገኖቻችን ላይ ግፍ ሲፈጽም በተጨባጭ እያዬ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ጠቅላይ ሚኒስትር በመብት ረጋጩ የሳውዲ መንግስት ላይ ምንም ነገር አላለም፡፡ (የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ እንደ መርግ ተጭኖ በመግዛት ላይ የሚገኘው እና እራሱን ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ እያለ የሚጠራው ወሮበላ ስብስብ ነው፡፡)

ምን ዓይነት ሰይጣን ነገር ነው!!! (ይቅርታ!)

እውነታው ፍርጥርጥ ብሎ ሲታይ የአል አሳድ ኃይሎች እና የአይኤአይኤል/አይኤስአይኤስ (ISIL/ISIS) አሸባሪ ቡድኖች እ.ኤ.አ ከ2011 ጀምሮ በመቶዎች እና በሺዎች የሚቆጠሩትን የሶርያ እና የኢራቅን ህዝቦች በመፍጀት ላይ ይገኛሉ፡፡

በአሁኑ ጊዜ በሁለቱ ሀገሮች መንግስታት እና በአሸባሪ ኃይሎች ጥቃት ምክንያት ከ7 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ከቤታቸው የተፈናቀሉ ተራ የሶርያውያን እና የኢራቃውያን ዜጎች አሉ፡፡

ባለፉት ሁለት ሳምንታት ስለሶርያ ተፈናቃይ ዜጎች እና ዩናይትድ ስቴትስ እንዴት አድርጋ መርዳት እንዳለባት ለሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች ተናግሪያለሁ፡፡

ሶርያውያን ኢትዮጵያውያን እንዳልሆኑ አውቃለሁ፡፡

እኔን የሚያሳስበኝ የዜግነት ብሄራዊነት ጉዳይ አይደለም፡፡ እኔን የሚያሳስበኝ እና የሚያስጨንቀኝ ስለሰው ልጆች የስብእና ጉዳይ ነው፡፡

ለእኔ የበሻር አል አሳድ መንግስት በሶርያ ህዝብ ላይ እያካሄደ ባለው ስቃይ፣ እንደዚሁም የኢራቅ እና የሶርያ አሸባሪ እስላማዊ መንግስት እና የኢራቅ እና የሌባንት  አሸባሪ መንግስት/Islamic State of Iraq and Syria and Islamic State of Iraq and the Levant (ISIS-ISIL በኢራቅ እና በሶርያ ህዝቦች ላይ እያካሄደ ባለው እና የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በኢትዮጵያውያን ዜጎች ላይ እየፈጸመ ባለው ዕልቂት እና የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ መካከል ምንም ዓይነት ልዩነት የለም፡፡

ሁሉም ሰላማዊ ዜጎችን የጥቃት ሰለባ ያደረጉ አሸባሪ ቡድኖች/ገዥዎች ናቸው፡፡

በሶርያ ስደተኞች ላይ እየተፈጸመ ስላለው አሰቃቂ ሁኔታ የማያውቅ ሰው ይኖራልን?

ያ አሰቃቂ ድርጊት ሁሉንም የሶርያውያንን ማህበረሰብ ጓዷ ዳስሷል፡፡

አብዛኞቹ ሶርያውያን ሙስሊሞች ናቸው፣ ሆኖም ግን ወደ 10 በመቶ በላይ የሚሆኑት ዜጎች ደግሞ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡

የሶርያ የእርስ ብርስ ጦርነት ለሁሉም ሶርያውያን ዜጎች አደጋ ሆኖ ዘልቋል፡፡

የሶርያውያን የእርስ በእርስ ጦርነት የሶርያውያን ወይም ደግሞ የመካከለኛው ምስራቅ ችግር ብቻ አይደለም፡፡

ጉዳዩ በእያንዳንዱ ሰው ጣልቃ በመግባት ንግዳቸውን ለሚያጧጡፉ ኃይሎች የጂኦፖለቲካ ችግር ብቻ አይደለም፡፡

በሶርያ ያለው ጦርነት በቀላሉ ሊተነበይ የማይችል ባህሪ ያለው እና በሰው ልጆች ላይ ሰብአዊ ቀውስን እያስከተለ የሚገኝ በመሆኑ ምክንያት ይህ ችግር በአሁኑ ጊዜ ዓለም አቀፋዊ ችግር ነው፡፡

የሶርያ ስደተኞች ችግር ያለምንም ጥርጥር ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ በግዙፍነቱ የመጀመሪያውን ደረጃ የያዘ የግዳጅ ስደት ነው፡፡

ሆኖም ግን ሊነሳ የሚችለው ጥያቄ ዩኤስ አሜሪካ በፋይናንሻል ችግር እየተሰቃዩ ያሉትን ሶርያውያን የመርዳት የሞራል ግዴታ ያለባት መሆን ካለመሆኑ ጋር እና የበለጠ ደግሞ የፖለቲካ ጥገኝነት እና የኗሪነት መብቶችን ከመስጠት ሁኔታ ጋር ነው፡፡

ዩኤስ አሜሪካ እንደዚህ ያሉ ግዴታዎች የሚኖሩባት ከሆነ ይህን ከባድ ኃላፊነት እንዴት ነው በአግባቡ ልትወጣው የምትችለው?

የሶርያ የእርስ በእርስ ጦርነት እ.ኤ.አ በ2011 በበጋው ወራት የአረብ የጸደይ አብዮት ተቃውሞ እየተካሄደ በነበረበት ጊዜ ነው የተጀመረው፡፡

የሶርያ ፕሬዚዳንት በሆነው በባሻር አል አሳድ መንግስት ላይ ሀገር አቀፍ የሆነ ተቃውሞ በፍጥነት እና ስፋቱን ባጠናከረ መልኩ በሀገሪቱ ውስጥ መዛመት ጀመረ፡፡

የአሳድ አባት እና ልጅ ቡድን አሳድ  ላለፉት 40 ዓመታት በስልጣን ላይ የሙጥኝ ብሎ ቆይቷል፡፡

የሶርያ ኃይሎች እየተደረገ ላለው ጭቆና ጠንካራ የሆነ ምላሽ በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህም በመሆኑ ግጭቱ ቀስ በቀስ በሀገሪቱ ውስጥ ወደ ትጥቅ አመጽ ተለውጧል፡፡

በአሁኑ ጊዜ ሶርያ በአውዳሚ እና ማለቂያ በሌለው የእርስ በእርስ የጦርነት አዘቅት ውስጥ ተዘፍቃ ትገኛለች፡፡

በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ በአሁኑ ጊዜ ተወሳስቦ የሚገኘውን ውስብስብ ሁኔታ የበለጠ ውስብስብ ለማድረግ ISIS እና ISIL ሁለቱም ጃሃዳዊ ወታደራዊ ቡድኖች የእርስ በእርስ ጦርነቱን በመቀላቀል የሶርያን ሉዓላዊ ግዛት በመውረር ላይ ይገኛሉ፡፡

ባለፉት 4 ዓመታት ወደ 5 ሚሊዮን የሚሆኑ ሶርያውያን ስደተኞች በሶርያ የመንግስት ኃይሎች እጅ ወይም በISIS/ISIL የሚደርሱ አደጋዎችን እና ሞትን በመፍራት ሀገራቸውን ለቅቀው ተሰደዋል፡፡

ከ3 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ኢራቅያውያን በአሁኑ ጊዜ አብዛኛውን የኢራቅ እና የሶርያ ግዛት ተቆጣጥሮት የሚገኘውን የISIS/ISIL የጭፍጨፋ እልቂት በመፍራት ተሰደዋል፡፡

የሶርያውያን አሀዛዊ መረጃ በጣም አስደንጋጭ ሁኔታ ነው፡፡

እ.ኤ.አ በ2013 ሶርያ 22 ሚሊዮን ገደማ የሚገመት ህዝብ ነበራት፡፡ ከዚህ ውስጥ 5 ሚሊዮን ወይም ደግም 22 በመቶ የሚሆኑት ዜጎች ወደ መንግስት አልባ ስደተኝነት ተቀይረው  ይገኛሉ፡፡ እንደዚሁም ደግሞ 57 በመቶ የሚሆኑት የሶርያ ስደተኛ ዜጎች እድሚያቸው ከ17 ዓመት በታች የሆኑ ናቸው፡፡ ወደ 2 ሚሊዮን ገደማ የሚሆኑ ስደተኛ ሶርያውያኖች በቱርክ፣ 1.1 ሚሊዮን በሊባኖስ፣ 700 ሺ በዮርዳኖስ እና 150 ሺ በግብጽ ውስጥ ጥገኝነት ጠይቀው በስደት ላይ ይገኛሉ፡፡

በሚያስገርም ሁኔታ ሀብታሞቹ የገልፍ ሀገሮች ባህሬንን፣ ኩዌትን፣ ኦማንን፣ ካታርን፣ ሳውዲ አረቢያን እና የተባበሩት ኤምሬትን ጨምሮ ይህንን ቀውስ ለማቃለል በሚል በብዙ ቢሊዮን ዶላር እርዳታ ይሰጣሉ፡፡ ሆኖም ግን የሶርያንን ስደተኞች ለማስተናገድ እና ወደ ሀገሮቻቸው እንዳይገቡ በሮቻቸውን ክርችም አድርገው ዘግተው ይገኛሉ፡፡

በርካታ የአውሮፓ ሀገሮች ጥቂት ሶርያውያን ስደተኞችን ለመቀበል ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል፡ ግሪክ 250 ሺ ስደተኞችን ተቀብላለች፡፡

ጀርመን 1.5 ሚሊዮን ሶርያውያን ስደተኞችን ለመቀበል እንደምትችል ትናገራለች፡፡ ይህም የህዝቧን ጠቅላላ ብዛት 5 በመቶ የሚሆነውን ያህል ይሸፍናል!

ጀርመን ይህንን እርምጃ የምትወስደው ለምንድን ነው?

ይኸ ጉዳይ ከጀርመን ብሄራዊ ጥቅም ጋር የተያያዘ ነው፡፡

ስዊድን 64 ሺ፣ ቡልጋሪያ 15 ሺ፣ ኔዘርላንድ 14 ሺ፣ ፈረንሳይ 7 ሺ፣ እንግሊዝ 7 ሺ፣ ዴንማርክ 11 ሺ እና ሀንጋሪ 19 ሺ ስደተኞችን ተቀብለዋል፡፡

ዩኤስ አሜሪካ 1500 ስደተኞችን ተቀብላለች፡፡

ዩኤስ አሜሪካ በሶርያ ሰደተኞች ቀውስ ውስጥ በዚህ ዓመት ብቻ 600 ሚሊዮን ዶላር በመለገስ ትልቁን እርዳታ ያደረገች ብቸኛዋ ሀገር ናት፡፡ ይህም እርዳታ በለጋሽ ድርጅቶች የተሰጠውን የጠቅላላውን እርዳታ አንድ ሶስተኛ የሚሆነውን ይሸፍናል፡፡

እ.ኤ.አ ከ2011 ጀምሮ ዩኤስ አሜሪካ ለሶርያ ቀውስ 4 ቢሊዮን ዶላር በመለገስ ከለጋሽ ድርጅቶች ከፍተኛውን የሰብአዊ እርዳታ በማድረግ የቀዳሚነቱን ቦታ ይዛለች፡፡

ዩኤስ አሜሪካ በአሁኑ ጊዜ በርካታ ሶርያውያን ስደተኞችን መቀበል እንድትችል ዓለም አቀፋዊ ተጽዕኖ አየተደረገባት ነው፡፡

በቅርቡ ፕሬዚዳንት ኦባማ ዩኤስ አሜሪካ በሚቀጥለው ዓመት ቢያንስ 10 ሺ ሶርያውያንን እንደምትቀበል ተናግሯል፡፡

አስተዳደሩ ስደተኞቹ በተባበሩት መንግስታት የመቀበያ መስፈርት መሰረት በጥንቃቄ የመቀበል ሂደት ስራው እንደሚካሄድ ማረጋገጫ ሰጥቷል፣ ሆኖም ግን በጣም ጠንካራ በሆነ የደህንነት ጥበቃ ሂደት ውስጥ ትኩረት በማድረግ የሚሰራ ይሆናል፡፡ ይህ ስራ በብሄራዊ የጸረ ሽብር ማዕከል፣ በኤፍ.ቢ.አይ/F.B.I፣ በሀገር ውስጥ ደህንነት እና በዩኤስ አሜሪካ በበርካታ የስለላ ማህበረሰቦች አማካይነት በምርመራ የሚጣራ ይሆናል ፡፡

ዩኤስ ስንት ሶርያውያን ስደተኞችን መቀበል እንዳለባት ክርክሩ ተጀምሯል፡፡

10 ሺ የሚለው በባልዲ ውስጥ አንድ ጠብታ ውኃ የማፍሰስ ያህል ነው፡፡ ከዚህ በላይ መቀበል እንደምንችል አቅሙ አለን እና መቀበልም አለብን፡፡

ሌሎች ደግሞ ዩኤስ አሜሪካ በርካታ የሆኑ ስደተኞችን ከመቀበሏ በፊት በመጀመሪያ ደረጃ የእራሷን ቤት ማጽዳት አለባት ይላሉ፡፡

ይህ የሞቀ ክርክር ጣትን በመቀሰር እና በመጠቆም ተጧጥፎ ይገኛል፡፡

የኮኔክቲከት ግዛት ሴናተር የሆኑት እና የዴሞክራት የውጭ ግንኙነት ኮሚቴ አባል የሆኑት ክሪስ ሙርፊ እንዲህ ይላሉ፣ “የሶርያ ቀውስ እንዲጀመር እና በቀጣናው አለመረጋጋት እንዲኖር ያደረገው የቡሽ አስተዳደር አመራር ነው፡፡ በኢራቅ ላይ ጦርነት ባይከፈት እና ባትወረር ኖሮ የአሁኑ የሶርያ ቀውስ አይኖርም ነበር ብዬ አላስብም፡፡ ሆኖም ግን ሀገሪቱን በመያዛችን፣ በእኛ ወረራ ምክንያት ከበርካታ ነገሮች በኋላ ISIS እንዲመሰረት በማድረግ በእርግጠኝነት በአሁኑ ጊዜ በቀጣናው እና በሶርያ ውስጥ ተንሰራፍቶ ለሚገኘው ቀውስ የእራሱን ድርሻ አበርክቷል ብዬ አስባለሁ…ኃላፊነት አለብን ብዬ አስባለሁ፡፡” በማለት ትችታቸውን ያቀርባሉ፡፡ ሙርፊ 50 ሺ ሶርያውያን ስደተኞችን መቀበል እንደሚያስፈልግ ይናገራሉ፡፡

የሬፐብሊካን ኮንግረስ የኒዮርክ ግዛት አባል እና የሀገር ውስጥ የጸረ ስለላ እና ሽብር የደህንነት ንኡስ ኮሚቴ ሊቀመንበር የሆኑት ፔተር ኪንግ ማንኛውንም ሶርያውያን ስደተኞችን በመቀበሉ ረገድ ጽኑ እምነት አላቸው፡፡ ኪንግ “የአሜሪካውያን ህይወት በአደጋ ላይ ወድቆ እያለ” ቢያንስ 10 ሺ ሶርያውያን ስደተኞችን መቀበል የሚለውን የፕሬዚዳንት አቦማን ዕቅድ ይተቻሉ፡፡

ኪንግ ስለፕሬዚዳንቱ ውሳኔ እንዲህ ብለዋል፣ “ውሳኔው ከሕግ ማስፈጸሚያው እና በአስተዳደሩ ካለው የስለላ ኃላፊዎች ሀሳብ ጋር በተቃራኒው በኩል የቆመ ስለሆነ እነዚህን ባለስልጣኖች የምናስገድድበት ወይም ደግሞ በሚቀጥሉት 12 ወራት ውስጥ መፈጸም ስለመቻሉ የምናረጋግጥበት መንገድ የለም፡፡ አስተዳደሩ የጀርባ አጥንት የሆነው አስፈላጊ የሆነው የደህንነት ጉዳይ ፈር ባልያዘበት እና መሰረቱን ባልጣለበት ሁኔታ በሙሉ እቅሙ ወደፊት እየተጓዘ ነው፡፡“ እንዲህ በማለትም አስጠንቅቀዋል፣ “10 ሺ የሚሆኑ ማንነታቸው ያልታወቁ ሰዎችን ወደ ሀገር ውስጥ ማስገባት ማለት ሌላ የቦስተን ማራቶን ቦምብን መጋበዝ ማለት ነው፡፡“

ኪንግ በሶርያውያን ስደተኞች ስም ተደብቀው የእስልምና አክራሪዎች እና አሸባሪዎች ወደ አሜሪካ በመግባት ጉዳት ያመጣሉ የሚለውን የህዝቡን ፍርኃት በመጋራት ችግሩን ለማስወገድ እንዲቻል ጥንቃቄ እንዲደረግ ለማድረግ የሚያደርጉት ጥረት ነው፡፡

በሀገር ውስጥ ካለው ፖለቲካዊ ነባራዊ ሁኔታ እና እ.ኤ.አ በ2016 ስለሚካሄደው የዕጩ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ አንጻር ዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ስደተኞችን ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት ምን ምን አማራጮች አሏት?

እውነታው ፍርጥርጥ ብሎ ሲታይ አሜሪካ ወይም ደግሞ ሩሲያ ጣልቃ ገብተው ታላቅ ምስቅልቅል ያለ ሁኔታ ከሚያመጡ ይልቅ እራሳቸው የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች እንደባህላቸው እና እንደ አካባቢው ተጨባጭ ሁኔታ በማገናዘብ የሶርያውያንን ቀውስ እልባት ለመስጠት ቢችሉ የተሻለ ነው፡፡

ሆኖም ግን የተወሳሰቡት የመካከለኛው ምስራቅ ችግሮች ለዘመናት መፍትሄ አጥተው ተቀምጠዋል፡፡

ስለሆነም የሚቻል ከሆነ ለዩኤስ አሜሪካ ላቀርበው የምፈልገው ጥያቄ ተግባራዊ የሚሆን የፖሊሲ ማዕቀፍ እንድታቀርብ እና የሶርያውያንን ስደተኞች ሰብአዊ ቀውስ ለማስወገድ ተጨባጭነት ያለው የስደተኞች ፖሊሲ በመቅረጽ የችግሩ ሰለባ የሆኑትን ሶርያውያን ዜጎች መርዳት ይኖርባቸዋል የሚል ጥያቄ ለማቅረብ እወዳለሁ፡፡

ሌላው አማራጭ ደግሞ የተጠናከረ ድርጅታዊ አሰራር ባይኖርም ቀውሱ ስኬታማ ሆኖ ሲሻሻል ለማየት ተስፋን መሰነቅ እና ከጊዜ ጋር አብሮ መሄድ ምርጫችን ሊሆን ይገባልን?

በመጀመሪያ ደረጃ ዩናይትድ ስቴትስ ጭቆናን፣ ስቃይን እና ጦርነትን ፈርተው ለሚሸሹ ዜጎች ከለላ የመስጠት የረዥም ጊዜ ልምድ አላት፡፡

እ.ኤ.አ ከ1975 ጀምሮ ዩናይትድ ስቴትስ በቬትናም ጦርነት የተፈናቀሉ 1.5 ሚሊዮን የሚሆኑ የቬትናም ስደተኞችን በኢንዶ-ቻይና የስደተኞች ግብረ ኃይል አማካይነት ተቀብላ መጠለያ ሰጥታለች፡፡

እ.ኤ.አ ከ1979-1980 ባለው ጊዜ ውስጥ ለ32,000 ቬትናማውያን ስደተኞች ከለላ መጠለያ ሰጥታለች፡፡

እ.ኤ.አ ከሚያዝያ – ጥቅምት 1981 ባሉት ወራት ብቻ ከ250,000 በላይ ኩባውያን ስደተኞችን በአንድ ወር ውስጥ ከ80,000 በላይ ስደተኞችን የመርከብ ማጓጓዣ አገልግሎት ጭምር በማቅረብ ተቀብላ ጥገኝነት ሰጥታለች፡፡

በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ እና እስከ 150 ሺ የሚደርሱ የሶማሌ ስደተኞች   ባለፉት ሶስት አስርት ዓመታት ውስጥ በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ውስጥ እንዲሰፍሩ ተደርገዋል፡፡

ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ከቀድሞዋ ሶቬት ህብረት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ውስጥ እንዲሰፍሩ ተደርገዋል፡፡

ዩናይትድ ስቴትስ በርካታ የሆኑ ስደተኞችን ለመቀበል አዲስ አይደለችም፡፡

በቅርቡ በጠቅላላ ከሀገሪቱ የተውጣጡ 18 ከንቲባዎች ማለትም ኒዮርክ ከተማ፣ ሎስአንጀለስ፣ ጭጋጎ፣ ባልቲሞር፣ ሚኒያፖሊስ፣ ፒተስበርግ፣ ሲራኪዩስ፣ ደይተን፣ እና ሌሎች ከተሞችን ጨምሮ ተሰባስበው በመገናኘት የኦባማ አስተዳደር በዕቅድ ከያዘው የስደተኞች ብዛት በላይ ተጨማሪ ስደተኞችን መቀበል እንዳለበት ጥሪ አቅርበዋል፡፡

እ.ኤ.አ በ1981 ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬጋን “ስለዩናይትድ ስቴትስ የኢሚግሬሽን እና ስደተኞች መግለጫ ፖሊሲ“ በሚል ርዕስ እንዲህ በማለት ተናግረው ነበር፡

ሀገራችን የስደተኞች ሀገር ናት፡፡ ከማንኛውም ሀገር የበለጠ ከእኛ ስደተኞች ጠንካራ ቅርስ እና አቅም አንጻር ከሌሎች ሀገሮች ስደተኞችን እንቀበላለን፡፡ ማንም ነጻ የሆነ እና ሀብታም ሀገር በእራሱ የተሻለ የኑሮ ዘይቤን ለሚፈልጉ ወይም ደግሞ በሀገራቸው ውስጥ ከሚደርስባቸው ስቃይ ለማምለጥ ሲሉ የሚሰደዱ ስደተኞችን አያስተናግድም፡፡ ይህንን ጉዳይ ከሌሎች ሀገሮች ጋር በመሆን በጋራ ኃላፊነታችንን መወጣት አለብን፡፡

በዚህ መግለጫ ለዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ለሶርያውያን ስደተኞች ሰብአዊ ቀውስ እና  ለእራሳችን ስደተኞች ችግር ምላሽ ለመስጠት እንዲቻል እንደ የፖሊሲ ማዕቀፍ ሀሳብ ለመስጠት እፈልጋለሁ፡፡

አንዳንድ ዜጎች ሮናልድ ሬጋን እንደ መልካም የፖሊሲ ምንጭ ይሆናሉ የሚለውን ነገር ለመቀበል የጥርጣሬ ችግር እንደሚስተዋልባቸው እገምታለሁ፡፡

እኔ የሮናልድ ሬጋን ጥሩንባ ነፊ አይደለሁም፡፡

ለሮናልድ ሬጋን ድምጽ አልሰጠሁም፣ ወይም ደግሞ እርሳቸው በስልጣን በነበሩበት ጊዜ ምንም ዓይነት ድጋፍ አልሰጠሁም፡፡

ሮናልድ ሬጋንን በአንድ በተወሰነ የርዕዮት ዓለም መነጽር ነው የምመለከታቸው (በርዕዮት አውዳሚ መነጽር አላልኩም) እናም ከእርሳቸው ፖሊሲዎች ጋር ምንም ዓይነት ጉዳይ እንዲኖረኝ አልፈልግም ነበር፡፡

ሆኖም ግን የዩናይትድ ስቴትስን የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኞችን ጉዳዮች በምመረምርበት ጊዜ ከሮናልድ ሬጋን ጋር ከማንም ሰው የበለጠ የምስማማ መሆኔን አረጋግጫለሁ፡፡

ሮናልድ ሬጋን ልዩ ለሆነ ብሩህ የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኞች ፖሊሲን የሚሰብኩ እና የሚከተሉ ሰው ነበሩ፡፡

(እ.ኤ.አ በ1981 በሮናልድ ሬጋን ከወጡት የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኞች የፖሊሲ መግለጫ የተሻለ በመረጃ የዳበረ፣ ስብዕናን የተላበሰ እና ተግባራዊነትን ያካተተ የፖሊሲ ሰነድ ያዘጋጀ ማንም ካለ ግልጽ የክርክር መድረክ በመክፈት ለመሞገት ዝግጁ መሆኔን ላረጋግጥ እወዳለሁ፡፡)

አዎ የሬጋንን ጠንካራ የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኞች የፖሊሲ ሰነድን ትሩፋት በመያዝ አድናቆቴን እገልጻለሁ፣ እንዲሁም ለፖሊሲው በጎነት አጥብቄ ለመከላከል ያለኝን ዝግጁነት ላረጋግጥ እወዳለሁ፡፡

“ለውጥ ከሌለ እና የእራሳቸውን አስተሳሰብ መለወጥ የማይችሉ ሰዎች ምንም ዓይነት ለውጥ ለማምጣት ስለማይችሉ ዕድገት ሊኖር አይችልም“ ብለው የተናገሩት ጆርጅ በርናርድ ሻው እንደነበሩ አምናለሁ፡፡

ወደ ኋላ መለስ ብሎ ሳይቃኝ እና ካለፈው ክስተት ትምህርት ሳይቀሰም፣ አንድ ሰው የንቀት መንፈስ ከሚያሳይበትም ሰው ቢሆን ትምህርት ካልተወሰደ ዕድገት በምንም ዓይነት ሁኔታ ሊኖር አይችልም ማለት እችላለሁን? ማናቸውም ቢሆኑ ያለፈውን ክስተት ዞረው የማያዩ እና ከዚህም ድርጊት ትምህርት የማይወስዱ ሰዎች ምንም ዓይነት ነገር ሊለውጡ አይችሉም፡፡

እውነቱን መመስከር!

እ.ኤ.አ በ1981 ሮናልድ ሬጋን ለኩባ ስደተኞች በማሪያል የጀልባ ማጓጓዣ አገልግሎት በመስጠት ፕሬዚዳንታዊ መግለጫ ሰጥተው ነበር፡፡

በዚያ መግለጫ ፕሬዚዳንት ሬጋን የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኞች ጠንካራ የቅርስ ሀገር ነን በማለት ዕውቅና ሰጥተዋል፡፡

ሆኖም ግን ከዚህም በተጨማሪ የተሻለ ኑሮን ፍለጋ እና ስቃይን አምልጠው ወደ ሀገራችን የሚመጡትን ሁሉንም ማስተናገድ አንችልም፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን ለተሻለ ኑሮ ፍለጋ እና ስቃይን አምልጠው ድንበራችንን አቋርጠው ለሚመጡ ዜጎች ወሰናችንን አንዘጋም በማለት ጉዳዩን ግልጽ አድርገውታል፡፡

እንደዚሁም ደግሞ አሜሪካ የነጻነት አየርን ለመተነፍስ ለሚናፍቁ እና ለእራሳቸው የተሻለ ኑሮን ፍለጋ የሚመጡትን ዜጎች ሁሉ መቀበል እንደማትችል  አስምረውበታል፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን ለኩባውያን ስደተኞች ስለሰብአዊ ቀውስ እርዳታ ብቻ አይደለም ያደረጉት፣ ሆኖም ግን ይህንን ከማድረግም በተጨማሪ ትልቅ ዓላማን የሰነቀ ማለትም የበለጠ ውጤታማ የሆነ የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኞች ፖሊሲዎችን እነዚህን ፖሊሲዎች የሚደግፉ የሕግ ማዕቀፎችን የማውጣት ዕድሎችንም በማመቻቸታቸው ጭምር ነው፡፡

እ.ኤ.አ በ1981 ፕሬዚዳንቱ ፍትሀዊ እና ውጤታማ የሆነ የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኞች ፖሊሲ ለመንደፍ እንዲቻል ሁሉንም ባለድርሻ አካላት በመጋበዝ እንዲሳተፉ አድርገዋል፡፡

የኮንግረስ አባላትን፣ እንደዚሁም የአካባቢ አመራሮችን፣ የመንግስት አካላትን እና በጉዳዩ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ሊያርፍበቸው የሚችሉትን አካባቢዎች አሳትፈዋል፡፡

ሬጋን በስምንት መርሆዎች ላይ በመመስረት የሕግ የፖሊሲ ማዕቀፍ ሀሳብ ይፋ አድርገዋል፡፡

እነዚህ መርሆዎች የአሜሪካንን የተከበሩ እንግዳ የማስተናገድ ተሞክሮዎች በከፍተኛ ችግር ውስጥ እና ባልተደራጀ መልኩ ተሰባስበው ከሚገኙት የዓለም ህዝቦች ጋር ለማስታረቅ የሚፈልጉ ናቸው፡፡

የመጀመሪያው መርህ፣ 

o   አሜሪካ እንደሀገር ከሌሎች ሀገሮች የሚመጡትን ዜጎች እንደ አሜሪካ የእንግዳ ተቀባይነት ባህል እና ተሞክሮ መቀበሏን ትቀጥላለች፡፡ እንደዚሁም ጭቆናን በመፍራት ሀገራቸውን ለቀው ለሚሰደዱ ዜጎች ሁሉ ከሌሎች ሀገሮች ጋር በመሆን የመቀበል እና የማስፈር ኃላፊነቷን ትጋራለች፡፡

ይኸ መርሆ ማለት ስቃይን በመፍራት ሀገራቸውን ለቀው የሚሰደዱ ዜጎችን የመቀበል፣ የማስፈር እና የማገዝ እኩል የሆነ ኃላፊነት መኖር አለበት የሚል እምነት አለኝ፡፡ ሆኖም ግን አሜሪካ ሁሉንም ወይም ደግሞ ከፍተኛውን ኃላፊነት መሸከም እንደሌለባት አስምሮበታል፡፡

ሌሎች ሀገሮች ፍትሀዊ የሆነ ድርሻቸውን ማበርከት አለባቸው፡፡ ሀብታሞቹ የገልፍ መንግስታት ባህሬን፣ ኩዌት፣ ኦማን፣ ካታር፣ ሳውዲ አረቢያ እና የተባበሩት የዓረብ ኤምሬትስ የኪሶቻቸውን ደብተሮች መክፈት ብቻ ሳይሆን ለሶርያውያን ስደተኞች ወሰኖቻቸውንም ወለል አድርገው በመከፈት የቀውሱ ሰለባ የሆኑትን ስደተኛ ዜጎች መቀበል አለባቸው፡፡

ሁለተኛው መርህ፣ 

o   ከዚህ ጎን ለጎን ሕጋዊ ስደተኞችን ለመቆጣጠር የሚያስችል በቂ የሆነ የሕግ ማዕቀፍ ማዘጋጀታችንን ማረጋገጥ አለብን፡፡ ይህም የሚሆነው፡ ከፍተኛ የሆነ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ የውጭ ዜጎች ፍልሰት ሲከሰት፣ ለማን ምን ዓይነት ደረጃ ያለው የስደተኛ ወይም የፖለቲካ ጥገኝነት መሰጠት እንዳለበት፣ የጠረፍ ወሰኖቻችንን መሻሻል ለመቆጣጠር፣ በሕገወጥ መልክ ወደ ሀገር ውስጥ በሚገቡት ዜጎች ላይ የሚኖሩንን አሰራሮቻችንን ለማሳለጥ (ከፍትሀዊ የአሰራር ስርዓቶች እና ከሕገ መንግስቱ ጋር በሚጣጣም መልኩ የተቃኙ)፣ ፍትሀዊ የሰራተኛ እና የሕግ ማዕቀፎችን ተፈጻሚነት ለማጠናከር እና ሕጎቻችንን እያወቁ ሕጉን በሚጥሱት ተገቢውን ቅጣት ለመስጠት የሚሉት ናቸው፡፡ ሆኖም ግን እነዚህን ዓላማዎች ለማራመድ ከግል እሴቶቻችን እና ነጻነቶች ጋር የሚጣጣሙ መሆን አለባቸው፡፡

ሁለተኛው መርህ ማለት ዓለም አቀፍ የስደተኞች ቀውስ የተነጠለ ብቸኛ ችግር አይደለም፡፡ ይህ ችግር ውጤታማ የሆነ የስደተኞች ፖሊሲ ከማውጣት ትልቅ ጉዳይ ጋር የተያዘ ነው፡፡ ለፖለቲካ ጥገኝነት ብቁ ለመሆን ስርዓት ባለው ሂደት ማን መሆን እንዳለበት ግልጽ እና ትክክለኛ የሆነ የአሰራር ሂደት መኖር አለበት፡፡ ውጤታማ የወሰን ተፈጻሚነት መኖር ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በሕገ ወጥ መልክ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ዜጎችን ለማስተናገድ ውጤታማ፣ ፍትሀዊ እና ስብዕናን የተላበሰ የሕግ ማዕቀፍ ሂደት መኖር አለበት፡፡

ሶስተኛው መርህ፣ 

o   ቅርብ ከሆኑ ጎረቤቶቻችን ጋር ማለትም ከካናዳ እና ከሜክሲኮ ጋር ልዩ የሆነ ግንኙነት አለን፡፡ የስደተኞች ፖሊሲያችን ይህንን ግንኙነት ማንጸባረቅ አለበት፡፡

ዶናልድ ትሩምፕ በደቡብ በኩል ባለው የሀገሪቱ ወሰን ላይ የግንብ አጥር መገንባት በማለት በመናገር ላይ ይገኛል፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን “ቅርብ ከሆኑ ጎረቤቶቻችን ጋር ልዩ የሆነ ግንኙነት አለን፣“ ሲሉ ትክክል ናቸው፡፡

በአሁኑ ጊዜ የሰሜን አሜሪካ ነጻ ንግድ ድርጅት/North America Free Trade Agency (NAFTA)ን በመመስረት ከጎረቤቶቻችን ጋር የምጣኔ ሀብት ማህበረሰብ መፍጠር ችለናል፡፡

ልዩ በሆኑ ጎረቤታሞች መካከል መሰናክል የሚሆን የወሰን ድንበር ግንብ አጥር መገንባት የምንችል ለመሆናችን እርግጠኛ አይደለሁም፡፡

ሆኖም ግን መልካም ጎረቤቶች ስለጋራ ችግሮች እና እነዚህን ችግሮችም በጋራ ለመፍታት ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት ይናገራሉ ለማለት አይቻልም፡፡ ሌላው አማራጭ በጎረቤታሞች መካከል የጥላቻ መንፈስ መኖር እና ይህ ክስተት እንዲያውም ችግሩን ወደ ባሰ ቀውስ ውስጥ የሚጨምር ይሆናል፡፡

አራተኛው መርህ፣ 

o   ዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ እና ሜክሲኮ ሁለቱም ሀገሮች ታሪካዊ በሆነ መልኩ ሚክሲኮውያን በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ውስጥ የስራ ዕድል ጥቅም የሚያገኙ ለመሆናቸው እውቅና መስጠት አለብን፡፡ በርካታዎቹ ግዛቶቻችን ልዩ ልዩ የሰው ጉልበት የሚጠይቁ ስራዎች ሰራተኞችን ይፈልጋሉ፡፡ ስለሆነም እነዚህን ነገሮች ከግንዛቤ ውስጥ ማስገባት ይኖርብናል፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን የተወሰኑ ግዛቶችን የሰው ኃይል ፍላጎት በእርግጠኝነት ያውቃሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡

እ.ኤ.አ በ1942 ኮንግረሱ በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ በግብርና እና በኢንዱስትሪ ዘርፎች ሊሰሩ የሚችሉ ጊዚያዊ የሜክሲኮ ስደተኛ ሰራተኞች መግባት እንዲችሉ እንዲፈቀድላቸው የብራሴሮ ፕሮግራም እየተባለ የሚጠራውን የአስቸኳይ ሰራተኛ ፕሮግራም ድንጋጌን አጸደቀ፡፡

በአሁኑ ጊዜ የካሊፎርኒያ ግብርና በብዙ መልኩ በስደተኛ ሰራተኞች ላይ ጥገኛ ነው፡፡

በሰከነ መልኩ የስደተኞች ፖሊሲያችንን በምናሻሽልበት ጊዜ እነዚህ ጉዳዮች ከግንዛቤ ውስጥ መግባት አለባቸው፡፡

አምስተኛው መርህ፣ 

o   በርካታ የሆኑ ሕገወጥ ስደተኞች የማህበረሰባችን ዋና አምራች ኃይሎች እና የሰራተኞቻችን መሰረታዊ አካሎች ናቸው፡፡ በዩናይትድ ስቴትስ ሀብት ያፈሩ ዜጎች እውቅና ያገኛሉ እንዲሁም ሀብታቸው በሕጋዊ ማዕቀፍ ይታቀፋሉ፡፡ ከዚህም ጎን ለጎን ይህንን ስራ ከመስራት ውጭ ሕገ ወጥ ስደተኝነትን ማበረታታት የለብንም፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን በዩኤስ አሜሪካ የሚገኙ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሕገ ወጥ ስደተኞች በቀላሉ ሊወገዱ አይችሉም ሲሉ በግንዛቢያቸው ላይ ግልጽነት የሚታይበት ለመሆኑ እምነት አለኝ፡፡ በዩናይትድ ስቴትስ የሚገኙትን ወደ12 ሚሊዮን አካባቢ የሚሆኑ መረጃ የሌላቸውን ስደተኛ ዜጎች ወደ ሀገራቸው መመለስ አይቻልም፡፡

አንድ በቅርቡ በተካሄደ ጥናት መሰረት “ሁሉንም 11.2 ሚሊዮን የሚሆኑትን በአሜሪካ የሚኖሩትን ማስረጃ የሌላቸውን ስደተኞች በኃይል እና በግል ወደመጡበት ሀገር የመመለስ ፖሊሲ በሁለቱም መንገዶች እንዲመለሱ ማድረግ 20 ዓመታትን ያህል ጊዜ የሚፈጅ ሲሆን ከወጭ አኳያ ሲመዘን ደግሞ መንግስትን ከ400 – 600 ቢሊዮን ዶላር ሊያስወጣው ይችላል፡፡ በአጠቃላይ ከምጣኔ ሀብት አኳያ ሲታይ የበለጠ ግዙፍ የሆነ ተጽዕኖ ያሳድራል…“

ፕሬዚዳንት ሬጋን በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሕገ ወጥ ስደተኞችን በጅምላ ወደመጡበት ሀገር በመመለስ እርምጃ ላይ እምነት የላቸውም፣ ሆኖም ግን በጊዜ ሂደት በሀገሪቱ ውስጥ ሀብት ያፈሩትን ስደተኞች ያለውን የሕግ ማዕቀፎች ከግንዛቤ በማስገባት በጥንቃቄ እና ፍትሀዊ በሆነ መልኩ በመገምገም የሚፈጸም እንደሚሆን እምነት አላቸው፡፡

በሀገሪቱ ውስጥ ከባድ ወንጀል የፈጸሙትን እና የሕዝቡን ደህንነት ከአደጋ ላይ የሚጥሉ ስደተኞች ግን መልካም መስተንግዶ ሊደረግ አይችልም፡፡

ስድስተኛው መርህ፣ 

o   በሀገራችን ላይ አሉታዊ እንደምታ ሊያስከትል የሚችለውን የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂ ዜጎች በተለያዩ አካባቢዎች እና ግዛቶች ፍትሀዊ በሆነ መልኩ እንዲከፋፈል በማድረግ ከዚህ ጉዳይ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያላቸውን የፌዴራል መንግስት አካሎች ብቃት ለማሻሻል ጥረት ማድረግ ይኖርብናል፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን ብሄራዊ ውሳኔዎችን ማስተላለፍ እና እነዚህን ውሳኔዎች ከሀገር አቀፍ የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂ ስደተኞች ፖሊሲ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት ወደሌላቸው ወደ አካባቢያዊ አስተዳደሮች መጫን ፍትሀዊነት የጎደለው ብቻ አይደለም፡፡ ሆኖም ግን በአካባቢው ማህበረሰቦች፣ በስደተኞች እና በሌሎች ተፈናቃይ ዜጎች ላይ ከፍተኛ የሆነ ጫናን ይፈጥራል፡፡

ስለሆነም የሚከተሉትን ነገሮች መፈጸም በጣም ጠቃሚ ነገር ነው፡

1ኛ) የስደተኞችን መስፈሪያ ቦታዎች በሀገሪቱ ውስጥ ባሉ አካባቢዎች ፍትሀዊ በሆነ መልኩ እንዲራጩ እና እንዲደለደሉ ማድረግ፣

2ኛ) የአካባቢ መንግስታትን እና ማህበረሰቡን ከረዥም ዕቅድ እይታ አንጻር አዲሶቹን ስደተኞች በሀገሪቱ የምጣኔ ሀብት ስርዓት ውስጥ እንዲካተቱ በማድረግ ምርታማ የሆኑ ዜጎች እንዲሆኑ ማድረግ ማስቻል ነው፡፡

ሰባተኛው መርህ፣ 

o   ስደተኞች ደህንነትን በሚያሰጠብቁ አገልግሎቶች ላይ ብቻ ጥገኛ ሆነው ከመኖር በተላቀቀ መልኩ በሀገራችን ካለው ማህበረሰብ ጋር ተቀላቅለው አምራች ዜጋ ሆነው ሊኖሩ የሚችሉባቸውን አዳዲስ የአሰራር ዘዴዎች መቀየስ እና ተግባራዊ ማድረግ፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን ይህንን ማለታቸው አብዛኞቹ ስደተኞች ወደ አሜሪካ የሚመጡት እርዳታን ለመጠየቅ ብቻ ለምጽዋዕትነት ብቻ መሆን የለበትም ለማለት ነው፡፡

አብዛኞቹ ስደተኞች የግላቸውን ጥረት በማድረግ እና ጠንክረው በመስራት የአሜሪካንን ህልም ለማሳካት ትኩረት አድርገው መንቀሳቀስ እንዳለባቸው አምናለሁ፡፡ መልካም አጋጣሚዎችን መፈለግ እንጅ በምጽዋዕት ላይ ጥገኛ የሆነ አስተሳሰብን ማራመድ እንደሌለባቸው አምናለሁ፡፡

ሆኖም ግን ፕሬዚዳንት ሬጋን ስደተኞች በሁለት እግሮቻቸው መቆም እንዲችሉ ማንኛውንም ዓይነት ጥረት እና ድጋፍ ማድረግ አለብን እንጅ በሕዝቡ እርዳታ እና በመንግስት ተመጽዋችነት ላይ ብቻ ጥገኛ መሆን የለባቸውም በማለት ማስጠንቀቂያ ሲሰጡ በእርግጥም ትክክል ናቸው፡፡

ስምንተኛው መርህ፣

o   በመጨረሻም የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኝነት ችግሮች ዓለም አቀፍ መፍትሄዎችን ይሻሉ፡፡ ስደተኞችን ለማስፈር ዓለም አቀፋዊ ትብብርን መሻት ይኖርብናል፣ እናም በካሪቢያን ተፋሰስ ላይ ስደተኞችን ለማስፈር ፈጣን እና ዘላቂነት ያለው ፈጣን ዕድገት ለማስመዝገብ እና የሕገ ወጥ ስደተኞችን ተነሳሽነት ለመቀነስ የዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ትብብር አስፈላጊ ነው፡፡

ፕሬዚዳንት ሬጋን ስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂ ዜጎች ፖሊሲ አንድ ሀገር የቱንም ያህል ጠንካራ እና በሀብት የበለጸገች ብትሆንም ባትሆንም የአንድ ሀገር ኃላፊነት ብቻ ጉዳይ አይደለም በማለት ዕውቅና ሲሰጡ በእርግጥም ትክክል ናቸው፡፡

ችግሩ ዓለም አቀፋዊ መፍትሄዎችን ይሻል፡፡

አሜሪካ እነዚህን መፍትሄዎች ለመሻት የዓለም አቀፉን ጥረት በበላይነት መምራት ያለባት ቴክኖሎጂው እና ችግሮችን ለመፍታት የሚችሉ የፖሊሲ አመንጭዎች ያሉን በመሆኑ ምክንያት አይደለም፡፡ ሆኖም ግን ይህንን ኃላፊነት መሸከም ካልቻልን ሌላ ማንም ሊያደርገው ስለማይችል ነው፡፡

ሬጋን ሕጋዊ ማስረጃ የሌላቸው ስደተኛ ዜጎች ቀና መንገድን እንዲከተሉ ይሰብካሉ፡፡ ሬጋን እ.ኤ.አ በ1984 ለፕሬዚዳንታዊ የምርጫ ቅስቀሳ በተሰማሩበት ወቅት እንዲህ ብለው ነበር፣ “ ለብዙ ጊዜ እዚህ ለቆዩት እና መሰረት ላላቸው ስደተኞች ከጥቂት ጊዜ በፊት በሕገ ወጥ መንገድ የገቡ ስደተኞች ቢሆኑም እንኳ ጥገኝነቱን እንዲያገኙ እኔም የሚለውን ሀሳብ እደግፋለሁ፡፡“

እ.ኤ.አ በ1986 2.7 ሚሊዮን ሕጋዊ ማስረጃ ለሌላቸው ስደተኞች ሬጋን የስደተኞች ማሻሻያ እና የቁጥጥር ድንጋጌን ፈረሙ፡፡

እ.ኤ.አ በ2016 በሚደረገው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሬጋን ከዚህ ቀደም አንድ ጊዜ ተመርጠው ያገለገሉ ቢሆንም አሁን ደግመው ከመመረጥ የሚከለክላቸው ነገር የለም፡፡

ፕሬዚዳንት ኦባማ እና ዴሞክራቶች እና ሬፐብሊካኖች የኮንግረስ አባላት እ.ኤ.አ በ1981 ሬጋን አውጥተውት የነበረውን የስደተኞች እና የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎች የፖሊሲ ሰነድ እንደ አንድ የመጀመሪያ እርምጃ በመውሰድ የስደተኞችን ችግር አጠቃላይ በሆነ መልኩ ለመፍታት እንዲቻል በምክር ቤቱ አጸድቀው ፖሊሲውን እንዲጠቀሙበት በማሳሰብ ለተግባራዊነቱ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

እኔ የሬጋን ትሩፋት ጠባቂ አይደለሁም፡፡

ሆኖም ግን 17ቱን እርባየለሽ የሬፐብሊካንን ወሮበሎች ንግግር በምሰማበት ጊዜ የሬጋንን የስንብት እና ስለሀገራቸው ያላቸውን እንዲህ የሚለውን ተስፋ አስታወሰኝ፡

ረዥም ዕድሜ ያላት እና የኮራች ከተማ ከውቅያኖሶች የበለጠ ጠንካራ በሆኑ አለቶች የተገነባች፣ በነፋስ የማትገለበጥ፣ በእግዚአብሔር ቸርነት የታደለች፣ ሁሉንም የሰው ልጅ ዝርያ ሁሉ የምታለምድ፣ ዜጎች በሰላም እና በፍቅር ተሳስበው የሚኖሩባት፣ ንግድን የፈጠራ ስራን ያካተተች ነጻ ወደብ ያላት ከተማ እንዲኖር እመኛለሁ፡፡ እናም የከተማው ህንጻ የሚኖር ከሆነ እና ህንጻውም በሮች የሚኖሩት ከሆነ እንደሁም እነዚህ በሮች ለሁሉም ክፍት የሚሆኑ ከሆነ ማንም ቢሆን ፍላጎቱ ያለው ሰው እዚህ ለመኖር ይፈልጋል፡፡ እንግዲህ እኔ ሳየው የቆየሁት  እንደዚህ ነው፣ እስከ አሁንም ድረስ እያየሁት ያለሁት እንደዚህ ነው፡፡

ይህንን በማለቴ ምንም ዓይነት የሚያሳፍረኝ ነገር የለም፡፡ እ.ኤ.አ በ1970 ወደ አሜሪካ ከመጣሁ ጀምሮ ሳየው የቆየሁት እና አሁንም ቢሆን እያየሁት ያለው ነገር እንደዚህ ነው፡፡

ብቸኛው ጥያቄ ግን እንዲህ የሚል ነው፡ በአሁኑ ጊዜ ያሉት የሬፐብሊካን አባላት ሬጋን ሲያዩት የነበረው ረዥም፣ ከውቅያኖስ በጠነከረ አለት የተገነባች የኮራች ከተማ…እግዚአብሔር የቀደሳት ሀገርን ያያቷልን…?

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

ጥቅምት 1 ቀን 2008 .