ኦባማ ከትክክለኛው የ(ኢትዮጵያ)ታሪክ ምዕራፍ ጎን ተሰልፈዋልን?

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም 

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

የታሪክ ሸፍጥ

ፕሬዚዳንት ኦባማ “በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ” መሰለፍ አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦ ሰጥተው በመግለጽ እራስን በሚያወድስ መልኩ በተግባር ሳይሆን በንግግር ብቻ በማነብነብ እርሳቸው “በተሳሳተው የታሪክ ምዕራፍ” ተሰልፈዋል ብለው የፈረጇቸው ሰዎች አቋማቸውን እንዲያስተካክሉ በነገር ሸንቁጠዋቸዋል፡፡ እ.ኤ.አ በ2012 በተደረገው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ተቀናቃኛቸው ከነበሩት ከሚት ሮምኔይ ጋር ባደረጉት ክርክር ፕሬዚዳንት ኦባማ የእራሳቸውን ክብር ለመጠበቅ ሲሉ እንዲህ ብለው ነበር፣ “…ያሜ ሪካን መንግስትና ያሜሪካ ፕሬዝደንት በታሪክ ቀኝ ምዕራፍ ቆመዋል ብለው አስረዱ፡፡ “በብዙ አጋጣሚዎች ፕሬዚዳንት ኦባማ “በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ” ላይ መሰለፍ የሞራል ልዕልናን የሚጠይቅ እንደሆነ በተደጋጋሚ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን በተለዬ መልኩ አሜሪካ በሰብአዊ መብት ጥበቃ መስክ ላይ ትኩረት ከማድረግ አንጻር ብቸኛዋ ልዕለ ኃያል እንደሆነች ተናግረዋል፡፡ እ.ኤ.አ በ2009 የኢራን ተቃዋሚዎች ወደ መንገዶች ሰልፍ ለማድረግ በወጡበት ጊዜ ኦባማ እንዲህ ብለው ነበር፣ “ለፍትህ በጽናት የቆሙ ሁሉ በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ የተሰለፉ ናቸው፡፡“ የተባበሩት መንግስታት ጠቅላላ ጉባኤ ከተካሄደ ጥቂት ዓመታት በኋላ ኦባማ ባደረጉት ንግግር እንዲህ የሚል ጥያቄ አቅርበው ነበር፣ “ማንኛችሁ ናችሁ በዚህ የስብሰባ አዳራሽ የተገኛችሁ ተሳታፊዎች መጭው ጊዜ ህዝቡን ነጻ ከሚያወጡት ይልቅ ሀሳብን ወይም ለውጥን የሚያፍኑ ይሆናል ብላችሁ የምትከራከሩ? ዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ በየትኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ እንደምትሆን አውቃለሁ፡፡“  በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ ነውን?!

ፕሬዚዳንት ኦባማ በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ ባልተሰለፉት ላይ ጩኸታቸውን አሰምተዋል፡፡ ቭላድሚር ፑቲን ክሪሚያን በመውረር እና የሶሪያን አምባገነን መሪ የሆኑትን ባሽር አላሳድን እየደገፉ ስለሆነ “በተሳሳተ የታሪክ ምዕራፍ ላይ ናቸው”፡፡ አላሳድ በእራሳቸው ህዝቦች ላይ አሰቃቂ የሆነ ግፍ እየፈጸሙ ስለሆነ በተሳሳተው የታሪክ ምዕራፍ ላይ ናቸው፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ የአረብ አገሮች የሚገኙ ሁሉም አምባገነኖች ፕሬዚዳንት ኦባማ ወደ ትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ እንዲሰለፉ እስከሚነግሯቸው ድረስ ለአጭር ጊዜም ቢሆን በተሳሳተው የታሪክ ምዕራፍ ላይ ነበሩ፡፡“ ዩናይትድ ስቴትስ ከቀጥታው እና ከጠባቡ ትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ ያላትን አቋም በፍጹም አታለሳልስም፡፡ “በአሁኑ ጊዜ በሁሉም የመካከለኛው የአረብ አገሮች ላይ ያለን አቋም በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ መሆናችንን ያመላክታል ምክንያቱም ንጹሀንን በአሰቃቂ እልቂት ከመታረድ እየጠበቅናቸው እና ለሁሉም ህዝቦች ሰብአዊ መብቶቻቸው እንዲጠበቁላቸው እምነት ይዘን አቋማችንን እያራመድን ስለሆነ ነው፡፡“ በማለት ፕሬዚዳንት ኦባማ ንግግር አድርገዋል፡፡ ተቃዋሚዎች ቀስ እያሉ በአረብ ከተሞች ወደ መንገዶች ለአመጽ በወጡ ጊዜ በብርሀን ፍጥነት ተገልብጠው የአረብ አገር አምባገነኖችን በመቀላቀል በተሳሳተው የታሪክ ምዕራፍ እረድፍ ላይ ሰልፋቸውን አስተካክለዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት ኦባማ ባለው ዓመት በግብጽ የተካሄደውን  መፈንቅለ መንግስት ተከትሎ የዩናይትድ ስቴትስ ወታደራዊ እርዳታ ላይ የዓመቱን ግማሽ እርዳታ በመልቀቅ “በዓለም ላይ በጣም ጠንካራ የሆኑ ተዋጊ ሄሊኮፕተሮችን“ በትዕዛዝ ማስተላለፍ እንዲቆም በከፊል ማዕቀብ ጣሉ፡፡ የኦባማ አስተዳደር ከግብጽ ጋር እንደ ቀድሞው ሁኔታ መሞዳሞዱን በቀጠለበት ጊዜ የግብጽ ወታደራዊ ጦር የሙስሊም ወንድማማቾችን ይደግፋሉ ብሎ የወነጀላቸውን 683 ዜጎች በይስሙላው ፍርድ ቤት የሞት ቅጣት እንዲበየንባቸው አድርጓል፡፡ ከዚህ አንጻር ሲገመገም በእርግጥ ኦባማ በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ነው ወይስ ደግሞ በተሳሳተው የታሪክ ምዕራፍ ላይ ነው የተሰለፉት?!

“ስለታሪክ” ማስመሰያነት እየተነገረ ያለው የተገላቢጦሽ ሁኔታ የሚያስገርም ነገር ነው፡፡ ማርክስ በማኒፌስቷቸው ላይ እንዲህ ብለው ነበር፣ “እስከ አሁን ድረስ ያለው የህብረተሰብ ትግል የመደብ ትግል ነው፡፡“ ሄግል የታሪክ ሂደት በፍጹም ሊገለበጥ አይችልለም ብለው ነበር፡፡ ማህተመ ጋንዲ በዚህ ጉዳይ ላይ የማይስማሙ መሆናቸውን በመግለጽ እንዲህ ብለው ነበር፣ “በጣም ውሱን የሆኑ ጽናት ያላቸው ያልተገደቡ መንፈሶች እና እምነቶች የታሪክን ሂደት ሊቀይሩ ይችላሉ፡፡“ ዱራንት “ከታሪክ ስህተቶች ትምህርት የማንቀስም ከሆነ እነርሱን ባሉበት ሁኔታ እንደግማቸዋለን“ ብለው ነበር፡፡ ናፖሊዮን “ታሪክ ምንም ነገር ሳይሆን ሰዎች በመግባባት የፈጠሩት አፈ ታሪክ ነው“ ብለው ነበር፡፡ ያም ሆነ ይህ ናፖሊዮን እና ከእርሳቸው በኋላ የመጡት ሌሎች ሁሉም አምባገነኖች ተጠራርገው በታሪክ የቆሻሻ ማስቀመጫ ውስጥ ለዘላለም ይኖራሉ፡፡

ኦባማ እና ኬሪ የአፍሪካን አምባገነኖች ተሸክመዋል፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ በትክክለኛው ወይስ በተሳሳተው የታሪከ ምዕራፍ ላይ ነው ተሰልፈው ያሉት? 

እ.ኤ.አ በ2009 ፕሬዚዳንት ኦባማ በጋና አክራን ሲገበኙ ያሉት ታሪክ በጀግኖች አፍሪካውያን ላይ የሚኖር ነው፡፡ ለጀግና አፍሪካውያን/ት ያስተላለፉት መልዕክት የሚያበረታታ፣ በብሩህ ተስፋ የሚያስሞላ እና ጠንካራ ስሜትን የሚፈጥር ነበር… መሪዎቻችሁን ተጠያቂ እንዲሆኑ እና ህዝቡን ለማገልገል የሚያስችሉ ተቋማትን ለማቋቋም ስልጣን አላችሁ፡፡ በሽታን ልታሸንፉ ትችላላችሁ፣ የእርስ በእርስ ግጭቶችን ማቆም ትችላላችሁ፣ እናም ለውጥን ከታች ጀምሮ ማምጣት ትችላላችሁ፡፡ ይህንን ማድረግ ትችላላችሁ፡፡ አዎ ትችላላችሁ፡፡ ምክንያቱም በአሁኑ ጊዜ ታሪክ በእንቅስቃሴ ላይ ነው፡፡ ኦባማ ቦቅቧቃዎቹን የአፍሪካ መሪዎች በአጽንኦ እስጠንቅቀዋቸዋል፡፡ “…ምንም ዓይነት ስህተት እንዳትሰሩ፣ ታሪክ በእነዚህ ጀገኖች አፍሪካውያን/ት ጎን ናት እናም መፈንቅለ መንግስት በሚያደርጉ ወይም በስልጣን ላይ እንደ መዥገር ተጣብቀው ለመቆየት ሲሉ ህገመንግስትን በሚያሻሽሉ አምባገነኖች ጎን አይደለችም፡፡ አፍሪካ ጠንካራ ግልሰቦችን አትፈልግም፣ የምትፈልገው ጠንካራ ተቋማትን ነው…የዜጎቻቸወን ፍላጎት የሚያከብሩ መንግስታት የበለጸጉ የበለጠ የተረጋጉ እና የበለጠ ስኬታማ ናቸው…“

እ.ኤ.አ ጁን 2013 “የአፍሪካን አምባገነኖች መንከባከብ“ በሚል ርዕስ ትችት አቅርቤ ነበር፡፡ በዚህ ትችት ላይ የአሜሪካ “ዲፕሎአገዛዝ” እና “ዲፕሎቀውስ” (በእራሴ አባባል የአሜሪካንን መንታ ምላስ የሰብአዊ መብት አስመሳይ ዲፕሎማቶችን አመለካከቶች፣ ድርጊቶች እና ባህሪያት ለመግለጽ የተጠቀምኩበት) ነበር፡፡ በዚያ ትችቴ ላይ የአሜሪካው የመንግስት መምሪያ ጸሐፊ ኬሪ በጸሐፊነት ዘመናቸው ብዙም የማይጠቅሙ እና በደንብ ጎልተው የማይታዩ የሰብአዊ መበት አጠባበቅ በኢትዮጵያ እንዲሁም በመላው አፍሪካ የሚያራምዱ መሆናቸውን ለመተንበይ ሞክሬ ነበር፡፡ “የኬሪ የዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ በአፍሪካ የሰብአዊ መብት ፖሊሲ“ ላይ በአስመሳይነት በባዶ ቃላት ታጅቦ የሚሽከረከር ምናባዊ እንጂ “ትርጉም ያለው የሰብአዊ መብት ፖሊሲ ሽግግር በኢትዮጵያ በማድረግ ላይ ያተኮረ አይደለም፡፡“ በኬሪ የዉጭ ጉዳይ አስተዳደር ዘመን ቀደም ሲል ከነበሩት ከሂላሪ ክሊንተን በኢትዮጵያ እና በአፍሪካ የተለየ ፖሊሲ እንደማያራምዱ እና ተመሳሳይ እንደሚሆን ለፖለቲካ መድረክ ትወና ምቹነት እና “በሽብርተኝነት ላይ ዓለም አቀፍ ጦርነት” ለማካሄድ በሚል  ማካካሻ የተረሳ እንደሆነ ትንበያ ሰጥች ነበር፡፡ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ህልውናቸው በአምባገነኑ ገዥ አካል ሲሸበብ፣ በጠራራ ጸሐይ የህዝብ ድምጽ ሲዘረፍ፣ ሰላማዊ አመጸኞች መብቶቻቸው ሲደፈጠጡ፣ እና የተቃዋሚ ኃይሎች ሀሳቦቻቸውን እንዳይገልጹ ሲታፈኑ፣ የፕሬስ እና የኢንተርኔት ገደብ ሲጣል እንዲሁም ሙስና በኢትዮጵያ እንደ ካሰንሰር እየተስፋፋ የአገሪቱን ሀብት እያሽመደመደ ባለበት ሁኔታ የኦባማ አስተዳደር ለሁኔታዎች አይቶ እንዳላየ እያለፈ ነው፣ ለጉዳዩም ምንም ትኩረት ባለመስጠት ጆሮ ዳባ ልበስ ብሏል፣ ከንፈር ከመምጠጥ ያለፈ ተጨባጭነት ያለው ስራም አልሰራም፡፡ ቃል እና ተግባር ለየቅል ሆነዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የኦባማ የአፍሪካ ፖሊሲ የሰብአዊ መብት ጥበቃን አያካትትም፡፡

ኬሪ ባለፈው ሰኔ ኢትዮጵያን በጎበኙበት ጊዜ በሰቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ላይ እየተደረገ ያለውን የኃይል እርምጃ እዲቆም፣ ሁሉም የፖለቲካ አስረኞች እንዲፈቱ እንዲሁም ነጻውን የመገናኛ ብዙሀን መጨቆኑን እንዲያቆም፣ ነጻ ጋዜጠኞችን፣ ሰላማዊ አመጸኞችን እና የተቃዋሚ ፖለቲካ አመራሮችን ማሸማቀቁን እና ወደ እስር ቤት ማጋዙን እንዲያቆም ይማጸ ናሉ ወይም ደግሞ እንዲያቆም ያደደርጋሉ የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ ይህንን ትንበያ በዘፈቀደ ወይም ደግሞ ከእውነታው በራቃ መልኩ ተምኔታዊ የሆነ አስተሳሰብም አልነበረም፡፡ ኬሪን እና ኦባማን በተናገሩት ቃላት ብቻ ነው እየመዘንኳቸው ያለሁት፡፡ እ.ኤ.አ በ2008 ዕጩ ተመራጮች የነበሩት ኦባማ እና ጆይ ቢደን የሚከተለውን ቃል ገብተው ነበር፣ “የታሰሩ ምሁራን፣ አክቲቪስቶች እና በግብጽ እንደ አይማን ኑር ያሉት የፖለቲካ የተቃዋሚ የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ እንሰራለን፡፡” እ.ኤ.አ ጃንዋሪ 24/2013  በድምጽ ማሰባሰብ ሂደታቸው ላይ ኬሪ እንዲህ ብለው ነበር፣ “አንድ ወይም ሌላ አገር በምጎበኝበት ጊዜ ያለንን ቀዳሚ ዓላማ እና ይህም ተግባራዊ እንዲሆን በሚሉት ላይ አንዳንድ ጊዜ እጋፈጥ ነበር፣ ሆኖም ግን የሰብአዊ መብትን ጉዳይ በተለይም በእስር ቤት የሚገኙ ግለሰቦች እንዲለቀቁ ያላነሳሁበት ጊዜ አልነበረም፣ ይህንንም አቋሜን አጠናክሬ እቀጥልበታለሁ…“

ሴክሬታሪ ኬሪ  እ.ኤ.አ በጁን 2013 ኢትዮጵያን በጎበኙበት ጊዜ በዲፕሎማክራሲያዊነት ጸጥ የማለት መብታቸውን ተጠቅመዋል፡፡ ኬሪ ለአምባገነኖቹ ስለሰብአዊ መብት ጥበቃ አንዲትም ቃል ትንፍሽ አላሉም፡፡ “የታሰሩ ምሁራን፣ አክቲቪስቶች እና የተቃዋሚ የፖለቲካ እስረኞች ማለትም እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ ውብሸት ታዬ፣ አንዷለም አራጌ፣ ኦልበና ሌሊሳ፣ በቀለ ገርባ፣ አቡባከር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ካሚል ሸምሱ እና ሌሎችም በርካቶች እንዲፈቱ እንሰራለን፡፡” የሚለው ይቅር እና ስለሰብአዊ መብት ጥበቃ አንዲትም ቃል ትንፍሽ አላሉም፡፡

በኦባማ አስተዳደር የሰብአዊ መብት ዲፕሎክራሲ ይዞታ፣

ኬሪ ባለፈው ሳምንት ኢትዮጵያን በጎበኙበት ጊዜ የእርሳቸው አስተናጋጆች አሸርጋጅ የገዥው አካል አዲስ በቁጥጥር ስር ያዋሏቸውን እና ወደ እስር ቤት የወረወሯቸውን የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን እና አባላትን፣ ነጻ ጋዜጠኞችን እና ጦማሪስቶችን እንዲሁም የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን በጥይት እየቆሉ የመቀበያ ስጦታ አድርገው ሰላምታ አቅርበውላቸዋል፡፡ ይኸ በእውነቱ ታላቅ ዘለፋ ነው፡፡ በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ያሉት ወሮበሎች በኦባማ የማስመሰያ አስተዳደር ላይ ምን ያህል መተማመን እንዳለባቸው የሚያመላክተው ተጫባጭ የግድያ እና የዘፈቀደ የእስራት ወንጀለኝነት መረጃ በመያዝ ኬሪ ከአውሮፕላን ሲወርዱ አቅርበውላቸዋል፡፡ “እህስ ኬሪ እንግዲህ ምን ይፈጠር!?“

ኬሪ “የደህንነት ጉዳዮችን” ለመወያየት ኢትዮጵያ ውስጥ ነበሩ፡፡ ሆኖም ግን በዘፈቀደ እየተጋዙ በእስር ቤት ስለሚማቅቁት እና የዘፈቀደ ግድያ ስለሚፈጸምባቸው የኢትዮጵያ ዜጎች ደህንነት ጉዳይ እልነበረም፡፡ ኬሪ ከእራሳቸው ፍላጎት ውጭ በተጽዕኖ ባለፈው ሳምንት በሸፍጥ ክስ ተመስርቶባቸው በእስር ቤት የሚገኙትን የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮቸን እና ደጋፊዎችን በማስመልከት የይስሙላ ንግግር አድርገዋል፡፡ የእስር ቤቱ ሰለባ ከሆኑት ከብዙዎቹ ጥቂቶች መርከቡ ኃይሌ፣ ሶሎሞን ፈጠነ፣ ዘሪሁን ተስፋዬ፣ አናኒያ ኢሳያስ፣ ፋሲካ ቦንገር፣ ጀሚል ሽኩር፣ ሰይፈ ጸጋየ፣ የሽዋስ አሰፋ፣ እመቤት ግርማ፣ ዮናስ ከድር፣ እየሩሳሌም ተስፋው፣ አበራ ኃይለማርያም፣ አበበ መከተ፣ ብሌን መስፍን፣ አስናቀ በቀለ፣ መስፍን፣ ተስፋዬ አሻግሬ፣ እዮብ ማሞ፣ ኩራባቸው፣ ተዋቸው ዳምጤ፣ ፍቅረማርያም አስማማው፣ እያስፔድ ተስፋዬ፣ ጋሻው መርሻ፣ ተስፋዬ መርኔ፣ ሀብታሜ ደመቀ፣ ጌታነህ ባልቻ፣ ንግስት ወንድይፍራው፣ ሜሮን አለማየሁ የሚባሉ ለሀገራቸው ብሩህ ራዕይ ያላቸው ወጣቶች ይገኙበታል፡፡

“ከውጭ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ጋር በመገናኘት እና የማህበራዊ መገናኛዎች ዘዴዎችን በመጠቀም በአገሪቱ ውስጥ አለመረጋጋትን ለመፍጠር“ በሚል ሰበብ ገዥው አካል በሸፍጥ ያሰራቸውን ጋዜጠኞች እና ጦማሪስቶች እንዲፈታ ኬሪ የተማጽዕኖ ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ከእነዚህ ከታሰሩት ውስጥ አስማማው ኃይለጊዮርጊስ፣ ተስፋለም ወልደየስ፣ ኤዶም ካሳዬ፣ አቤል ዋቤላ፣ አጥናፍ ብርሀኔ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ ዘላለም ክብረት እና በፈቃዱ ኃይሉ ይገኙበታል፡፡

ስለአዲሶቹ ታሳሪዎች አዲስ ዜና ከአሜሪካ የመንግስት መምሪያ ምላሽ የሚጠበቅ ነበር፡፡ ኦህ እንዴት ያሰለቻል! የመንግስት ቃል አቀባይ የሆኑት ጄን ሳኪ በዲፕሎክራሲያዊ መልኩ እንዲህ በማለት ገልጸው ነበር፣ “የኢትዮጵያ መንግስት ለእስር የዳረጋቸውን እስረኞች ጉዳይ እንደገና እዲመረምር እና በአስቸኳይ እንዲፈታቸው እንጠይቃለን፡፡ ይህንን ጥያቄ በቀጥታ ለኢትዮጵያ መንግስት ያቀረብነው በተጨባጭ በመሬት ላይ ያለውን እውነታ ከግንዛቤ በማስገባት ካለን አሳሳቢ ሁኔታ በመነሳት ነው፡፡ እናም በእርግጥ እኛ ከረዥም ጊዜ ጀምሮ በኢትዮጵያ ስለፕሬስ ነጻነት እና ሀሳብን በነጻ መግለጽ መከልከል ያለንን ስጋት በተደጋጋሚ በመግለጽ የኢትዮጵያ መንግስት የእራሱን ህገመንግስት ሙሉ በሙሉ እንዲያከብር ተማጽዕኖ ስናደርግ ቆይተናል፡፡“

እ.ኤ.አ ጁን 2012 የኢትዮጵያ ነጻ ጋዜጠኞች በይስሙላው ፍርድ ቤት ክስ በተመሰረተባቸው እና የረዥም ጊዜ እስራት በተፈረደባቸው ጊዜ ቃል አቀባይ ቪክቶሪያ ኑላንድ እንደዚሁ ተመሳሳይ ንግግር በማድረግ እንዲህ ብለው ነበር፣ “የኢትዮጵያ መንግስት በበርካታ ጋዜጠኞች እና በተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አባላት ላይ የጸረ ሽብር አዋጁን በመጠቀም የመሰረተው ክስ አሳስቦናል…የነጻ ጋዜጠኞች መታሰር በመገናኛ ብዙሀን እና ሀሳብን በነጻ በመግለጽ መብት ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ይኖረዋል፡፡ በኢትዮጵያ ስላለው የሰብአዊ መብት አያያዝ ሁኔታ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የውይይት መድረክ በመክፈት ሀሳብን በነጻ የመግለጽ እና የመገናኛ ብዙሀን ነጻ ማድረግ የዴሞክራሲያዊ ማህበረሰብ ግንባታ ወሳኝ ሚና የሚጫወቱ መሆናቸውን በማስመልከት ሀሳባችንን ግልጽ አድርገናል፡፡“ እንግዲህ እንደዚህ ባለ የሰብአዊ መብት ሁኔታ ነው በኦማ አስተዳደር በተግባር እየተተረጎመ ያለው፡፡

ፕሬዚዳንት ኦባማ ከተሳሳተው የአሜሪካ ታሪክ ምዕራፍ የጎን ተሰልፈዋልን?

ኦባማ መጀመሪያ ፕሬዚደንት ሲሆኑ የስልጣን የመክፈቻ ንግግራቸው እንዲህ ብለው ነበር፣ “አሜሪካ በከፍተኛ የስልጣን እርከን ላይ ያሉ ባለስልጣኖች እውቀቱ ወይም ደግሞ ራዕይ ስላላቸው  ብቻ አይደለም የምንተገብራቸው ሆኖም ግን የእኛ ህዝቦች የአያት ቅድመ አያቶቻችን መርሆዎች ታማኞች ሆነን ለመቀጠል ካለን ጽኑ ፍላጎት አንጻር ነው፡፡“ “ኦባማ ከአፍሪካ አምባገነኖነች ጎን በሚቆሙበት ጊዜ ከአያት ቅድመ አያቶቻችን መርሆች እና ከመመስረቻ ሰነዶች ተግባራዊ መሆን ጋር በጽናት ቆመዋልን?” የአሜሪካ ታላቁ የነጻነት አዋጅ የመመስረቻ ሰነድ የሚከተለውን ይላል፣

…መንግስታት ትክክለኛውን ስልጣን ከህዝቦች ፈቃድ በማግኘት የተዋቀሩ የሰዎች ስብስቦች ናቸው፡፡ የትኛውም ዓይነት መንግስት ለዓላማዎች ጎጅ ሆኖ ከተገኘ ይህንን መንግስት ለመለወጥ ወይም ደግሞ ለማስወገድ እና  ደህንነታቸውን እና ደስታቸውን ለማረጋገጥ የሚያስችል  በእነዚህ መርሆዎች ላይ በመመስረት የመንግስትን ኃይል ማዋቀር የሰዎች መብት ነው፡፡ ተከታታይ የሆኑ የመብት ረገጣዎች መፈጸም እና ከመብት ውጭ መሄድ እንዲሁም ባልተለያየ መልኩ አንድን ነገር በተግባር ማሳየት እራሳቸውን የለየላቸው አምባገነኖች በሚሆኑበት ጊዜ እንደዚህ ዓይነት መንግስታትን ከጫንቃቸው ላይ አሽቀንጥረው ለመጣል እና ለእነርሱ የሚስማሙ መንግስታትን ለወደፊቱ ደህንነታቸው ሲባል መመስረት የህዝቡ ስራ ነው…”

ኦባማ ስልጣንን ከጠብመንጃ አፈሙዝ በመያዝ ትክክለኛውን የህዝብ ይሁንታ ሳያገኙ በጉልበት ስልጣንን ጨብጠው ህዝብን በማሰቃየት ላይ ከሚገኙ የአፍሪካ ወሮበላ ገዥዎች እና አምባገነኖነች ጎን በሚቆሙበት ጊዜ ከነጻነት አዋጁ ጎን ቆመዋል ማለት ይቻላልን?

የአሜሪካን ነጻነት የሚያውጀው ታላቁ የሰብአዊ መብት ጥበቃ ሰነድ የሚከተሉትን ኃላፊነቶች ይሰጣል፣

…ኃይማኖትን የማያከብር ወይም ደግሞ እምነትን ለማራማድ ክልከላ የሚጥል፣ በዚህም ሳቢያ ሀሳብን በነጻ የመግለጽ መብትን የሚሸብብ ወይም ደግሞ ነጻውን ፕሬስ የሚገድብ እና በነጻነት መሰብሰብን የሚከለክል እና ቅሬታን ለማቅረብ የሚከልክል መንግስት ህግ ሆኖ ሊወጣ አይችልም…ማንም ሰው ቢሆን ህይወትን፣ ነጻነትን ወይም ደግሞ ንብረትን ከህግ አግባብ ውጭ ሊያጠፋ ወይም ሊገድብ አይችልም፡፡

በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር የእራሳቸውን ዜጎች ለሚፈጁ የአፍሪካ አምባገነኖች (ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል 47 የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን መግደሉን መዘገቡን ልብ ይሏል)፣ ነጻ ጋዜጠኞችን በእስር ቤት ለሚያማቅቁ የእምነት ነጻነትን ለሚያፍኑ፣ ዜፈጎች ሀሳባቸውን በመግለጻቸው ምክንያት የሚሰቃዩበት፣ በነጻ የሚሰበሰቡ ዜጎችንን የሚያስፈራሩበት እና የሚያሸማቅቁበት ያለምንም ተጠያቂነት ዜጎቻቸውን በሙስና ከሚዘርፉ ሌቦች ጎን ነው ኦባማ በትክክለኛ ምዕራፍ ተሰለፍኩ የሚሉት?

አብርሀም ሊንከን በጌቲስበርግ ንግግራቸው ላይ እንዲህ ብለው ነበር፣ “በእግዚአብሄር ፈቃድ ይህች አገር አዲስ የውልደት ነጻነትን የሚያጎናጽፍ  የህዝብ መንግስት፣ ለህዝብ የቆመ ከመሬት አይጠፋም“ ብለው ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ ይህንን ሲሉ በአፍሪካ እጃቸው በደም ከተጨማለቀ ወሮበላ መንታፊ ገዥዎች ለመንታፊዎች ከተቋቋሙት “አዲስ የውልደት ነጻነት” ጎን መሰለፋቸውን ያመላክታልን?

የታሪክ ክስና ዳኝነት በኦባማ ላይ፣ 

ታሪክ ትክክለኛ የሆነ፣ ትክክለኛ ያልሆነ እና ውጣውረድ የሞላበት ከሆነ ታሪክም መክሰስም መዳኘትም ይቻላለል፡፡ የታሪክ ዳኝነት ሊሆን የሚችለው ኦባማ በትክክለኛው የታሪክ ምዕራፍ ላይ አልተሰለፉም፣ እናም ታሪክ እራሱ ከኦባማ ጎን አይደለም፡፡ ኦባማ ሁልጊዜ ከትክክለኛው የታሪክ ምዕርፍ ጎን እንደሚሰለፉ ይናገራሉ፣ ሆኖም ግን እውነታው ሲመዘን በተሳሳተው የታሪክ ምዕራፍ ጎን ከተሰለፉት ጋር አብረው ተሰልፈው ይገኛሉ፡፡ ተግባር በተለይም የተሻለ ተግባር ከመናገር የበለጠ ይናገራል እናም በኦባማ ላይ የቀረበው ክስ በአፍሪካ ላይ በተሳሳተው የታሪክ ምዕራፍ ላይ በመሰለፋቸው የተመሰረተ ክስ ነው፡፡

በኦባማ ላይ የቀረበው ክስና ዳኝነት በአፍሪካ ከእርሳቸው በፊት ካገለገሉት ከጆርጅ ቡሽ ያነሱ ተግባራትን ነው ለአፍሪካ ያከናወኑት የሚል ነው፡፡ (ጆርጅ ቡሽን አልመርጣቸውም ወይም ደግሞ አልደግፋቸውም፡፡ ሆኖም ግን ስልጣን ለመስጠት ብቻ እውነታውን መናገር የለብኝም፡፡ በአሁኑ ጊዜ በስልጣን ላይ ሆነው ስልጣናቸውን እንዴት እየተጠቀሙበት እንዳሉ፣ የዜጎችን መብት በምን ዓይነት ሁኔታ እየደፈጠጡ እንዳሉ፣ ስልጣናቸውን ያለአግባብ እየተጠቀሙ እንዳሉ እና በአጭሩ ስልጣናቸውን ለበጎ ነገር መጠቀም ያለመቻላቸውን ያመላክታል፡፡) ቡሽ ገንዘባቸውን አፋቸው በተናገረው ቦታ ላይ ያስቀምጡ ነበር እናም በቢሊዮኖች የሚቀጠሩ ዶላሮች ኤች አይቪ ኤድስን ለመዋጋት እና በአፍሪካ የበሽታው ሰለባ የሆኑትን ወገኖች ለማገዝ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ ኦባማ በግንባር ቀደምትነት ለዓለም አቀፍ የኤድስ ፕሮግም የሚውል በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ቅነሳ አድርገዋል፡፡ እንደ ዋሽንግተን ፖስት ዘገባ ከሆነ እ.ኤ.አ በ2012 በጠቅላላ 214 ሚሊዮን ዶላር ቅነሳ አድርገዋል፡፡ ይህም “በአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ይህንን ቀሳፊ የሆነውን እ.ኤ.አ በ1980ዎቹ በሬጋን አስተዳደር ጊዜ የተከሰተውን በሽታ ለማስወገድ አሜሪካ ተጨባጭነት ያለው ትግል ስታደርግ የቆየችበትን“ ኦባማ እ.ኤ.አ በ2014 ተጨማሪ 50 ሚሊዮን ዶላር ለመቀነስ ሀሳብ አቅርበው ነበር፡፡ የታሪክ ዳኝነት ሲመዘን ቡሽ በአፍሪካ የመጀመሪያ ገዳይ የነበረውን ወባን ከአፍሪካ ምድር ለማስወገድ አመርቂ የሆነ አስተዋኦ አድርገዋል፡፡ ቡሽ ለአፍሪካ ደኃ አገሮች የእዳ ቅነሳ አድርገዋል፡፡ ኦባማስ የፈየዱት ነገር ይኖር ይሆን?!? ካለስ እስቲ እንስማው፣ እንየው፡፡

ባለፈው ጁን ኦባማ አፍሪካን በጎበኙበት ጊዜ የጨለመውን የአፍሪካ አህጉር ለማብራት በሚል በርካታ የኤሌክትሪክ ፕሮጀክቶች ግንባታ ለማከናውን ተነሳሽነትን አሳይተዋል፡፡ “አፍሪካን በኃይል ለማጎልበት” በሚል መርህ ለሚቀጥሉት አምስት ተከታታይ ዓመታት በስራ ላይ የሚውል 7 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር እንዲሁም ከዚሁ በተጨማሪ የግል ዘርፉን ለማጠናከር በሚል 9 ቢሊዮን ዶላር በተጨማሪነት ለመመደብ ቃል ገብተው ነበር፡፡ እስከ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ግን ኦባማ ያጠናከሩት የወታደራዊ እና የገንዘብ ድጋፍ በማድረግ የአፍሪካን ወሮበላ ገዥዎች ኃይል ማጠናከር ብቻ ነው፡፡ እነዚህ ቃል የተገባለቸው በቢሊዮን የሚቆጠሩ ዶላሮች በባዶ ተስፋ በጆንያ ታጭቀው ለጨለማው አፍሪካ ወሮበላ አምባገነኖች የሚደርሱ ከሆነ ለመንታፊ የአፍሪካ አምባገነኖች በውጭ አገር ለከፈቷቸው የሂሳብ አካውንቶቻቸው እንደ ገና ዛፍ መብራት ከመስጠት ያለፈ ለብዙሀኑ የአፍሪካ ህዝብ የሚፈይዱት አንዳች ነገር አይኖርም፡፡

የታሪክ ዳኝነት ሲመዘን ኦባማ ለአፍሪካ ባዶ የተስፋ ቃላትን እና በማነብነብ ላይ ያነጣጠረ ባዶ ተስፋ ሆኖ ይገኛል፡፡ ላለፉት የመከኑ ቃል ኪዳኖች እንደገና ሌላ አዲስ ቃል ኪዳኖችን ይገባሉ፡፡ “በሺዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን/ት ወደ ዩናይትድ ስቴትስ በመምጣት በምርጥ ዩኒቨርስቲዎቻችን በመግባት እውቀታችሁን ማበልጸግ የሚያስችል አዲስ ፕሮግራም ተመቻችቷል“ የሚል አዲስ ቃል ኪዳን ገብተዋል፡፡ በአፍሪካ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን/ት በወሮበላ አምባገነኖች ስቃያቸውን የሚያዩት ወጣቶች የወደፊተ ዕጣ ፈንታ ሲተን ምን ምን ማድረግ ይቻላል?

የታሪክ ዳኝነት ሲመዘን ኦባማ በአፍሪካ የሚኖሩ ህዝቦች በእርሳቸው ቃል ኪዳን “ተስፋ እና ለውጥ” የወደፊት ጥሩምባ ጥሪ እምነት ጥለው የነበሩት ተስፋቸው ሲሟጠጥ ማየት አሳዛኝ ሁኔታ ነው፡፡ የኦባማ “የተስፋ መጠናከር” ምንም ያለማድረግ ተስፋ እና በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን/ት የባዶ ተስፈኛነት ምዕናባዊ ድርጊት ነው፡፡ የታሪክ ክሱ “ምንም የተደረገ ለውጥ እንደሌለ እናምናለን፡፡!“ በአፍሪካ ከወሮበላ አምባገነኖች እና ከእነርሱ ግብረበላ ሎሌዎቻቸው በስተቀር ማንም ቢሆን በኦባማ ላይ እምነት የለውም፡፡ የኦባማ “አዎ እንችላለን“ በተግባር ሲመነዘር “በአፍሪካ ውስጥ የሰብአዊ መብቶችን ሁኔታ ለማሻሻል ምንም ነገር ማድረግ አንችልም“ የሚል ግልባጭ ትርጉም ይዞ እናገኘዋለን፡፡

በአፍሪካ የተስፋ መጠናከር፣

ኦባማ እንዲመረጥ ሽንጤን ገትሬ ስታገል እና ሌሎችም ለኦባማ ደምጽ እንዲሰጡ ድጋፍ ሳሰባስብ ነበር፡፡ ይህንን ጉዳይ ግልጽ ላድርገው፡፡ ኦባማን በመደገፌ መቆርቆር ስሜት አይሰማኝም፡፡ አ..ኤ.አ በ2008 በተደረገው ምርጫ ኦባማ እንዲመረጡ ድጋፍ ባደረግሁ ጊዜ ያ ድርጊት ቆንጆ ሀሳብ ሆኖ ይታየኝ ነበር፡፡ እ.ኤ.አ. በ2012 ምንም ምርጫ የሌለው ሆንኩ፡፡ ስለሚት ሮምነይ ምን ማለት እችላለሁ?! ጆን ሁንትስማን በሬፐብሊካን የምርጫ ዝርዝር ውስጥ አልነበረም፡፡ ምናልባትም እ.ኤ.አ በ2016 ሊሆን ይችላል፡፡

እ.ኤ.አ በ2008 ኦባማን ለመምረጥ የእኔ ውሳኔ የተመሰረተው ፍላጎታዊ እና የመጀመሪያው አፍሪካዊ አሜሪካ በመሆናቸው ብቻ አልነበረም፡፡ ኦባማ በህዝብ ላይ ያላቸውን አስተዋጽኦ ሪከርድ በማየት የተደረገ ጥንቃቄ የተሞላበት ምርጫ ነበር፡፡ ከዩናይትድ ስቴትስ ሴኔት የህግ አገልግሎት ፋይላቸውን አጥንቻቸዋለሁ፣ እዲሁም ኦባማ HR 2003ን (ኢትዮጵያ ዴሞክራሲ እና ተጠያቂነት አዋጅ 2007) የሚያደንቁት እና ድጋፍም የሚያደርጉበት ስለነበር ነው፡፡ በኢሊኖይስ ህግ በደህንነት ፕሮግራሞች እና ዝቅተኝ ገቢ ላላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ድጎማ እንዲሰጣቸው እንዲሁም የቤተሰብ ሰራተኞች ከታክስ ነጻ እንዲደረጉ ሲያደርጉ የነበሩትን አስተዋጽኦ ከግንዛቤ በማስገባት ነበር ምርጫየን ያደረግሁት፡፡ በኢሊኖይስ ግዛት ሰራተኞች ከስራ እንዳይባረሩ እና ትላልቅ የምርት ተቋማትም እንዳይዘጉ ሲያደርጉት የነበረውን ጥረት አደንቃለሁ፡፡ እንዲሁም በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲያደርጓቸው የነበሩት መሳጭ እና ተያያዥ ንግግሮች እና በሚያቀርቧቸው በመረጃ ላይ በተመሰረቱ ጭብጦች እና የፖሊሲ መርሆዎች እገረም ነበር፡፡ “የአባታቸው ህልሞች” የሚለውን መጽሀፋቸውን በአንድ ቅምጥ በማንበብ፣ ሌሎችን መጣጥፎች እና ንግግሮቻቸውን በማዳመጥ እደሰት ነበር፡፡ በሀርቫርድ የህግ ትምህርት ቤት በነበራቸውን የአመራር ብቃት እና አካዳማያዊ ጥረት፣ በችካጎ የህግ ትምህርት ቤት በማስተማር ብቃታቸው ላይ ኩራት ይሰማኝ ነበር፡፡ እንደ መምህር እና የህገ መንግስት ባለሙያነቴ በሚያሳዩት አጋራዊ መንፈስ ኦባማ ጥሩ ብቃት ያላቸው ሰው አድርጌ እቆጥራቸው ነበር፡፡

ኦባማ የመጀመሪያው አፍሪካዊ አሜሪካ ፕሬዚዳንት መሆን በመቻላቸው ተጨማሪ እሴታቸው ነበር፣ ሆኖም ግን ይህ ለእኔ ወሳኙ ነገር አይደለም፡፡ እ.ኤ.አ በ1968 ሮበርት ኬኔዲ ያደረጓቸው ነብያዊ ንግግሮች ለእኔ እና ለሌሎቸ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ዜጎች አስገራሚዎች ነበሩ፡፡ እንዲህ ብለው ነበር፣ “እ.ኤ.አ በሜይ 1968 በሚቀጥሉት 40 ዓመታት ውስጥ እኔ የያዝኩትን ተመሳሳይ ስልጣን ጥቁር ሊይዘው ይችላል…“ “የኦባማ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሆነው መመረጥ በዓለም ላይ በሚገኙ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ሁሉ በተለይም በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ እና በአፍሪካውያን/ት “የተስፋን መጠናከር” በአሜሪካ በእራሷ በጉልህ እየታየ ስለሆነ የኦባማ ዕጩ ፕሬዚዳንት ሆነው መመረጥ ተቀባይነትን አግኝቷል– በአሜሪካ የማይቻለው የሚቻል ሆኖ ታይቷል፡፡ የኦባማ አባት ግንድ ከኬንያ መሆን በብዙ ሚሊዮን ለሚቆጠሩ አፍሪካውያን/ት ተስፋ የሰጠ ክስተት ስለነበር ኦባማ አፍሪካን በዩናያትድ ስቴትስ የውጭ ፖሊሲ ማውጣት እና በሰብአዊ መብት አያያዝ ላይ ጠንካራ ሚና በመጫወት የአፍሪካን ቦታ ከፍ ያደርጋሉ የሚል ግምትን አሳርፎ ነበር፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች በኦባማ ላይ እምነት የመጣል የተስፋ ጥንካሬ ነበረኝ፡፡

የተስፋ ውሸት፣

ባለፉት ጥቂት ዓመታት ከኦባማ ያልተከበሩ ቃል ኪዳኖች እና በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን/ት ባዶ ተስፋዎች ምክንያት ከተስፋ ውሸቶች ጋር ግብግብ ገጥሜ እገኛለሁ፡፡ ሴናተር ኦባማ “የተስፋ መጠናከር“ በሚለው መጽሀፋቸው ላይ የአሜሪካንን የውጭ ፖሊሲ በሰብአዊ መበቶች ጥበቃ ላይ የተመሰረተ መሆኑን በመግለጽ ጆን ኬኔዲን በመጥቀስ እንዲህ የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፣

በመንደሮች እና በጎጆዎች ያላችሁ በዓለም ላይ ግማሹን የምትይዙት የብዙሀኑን የመሰቃየት ማሰሪያ ገመድ ለመበጠስ የምትታገሉ ያለንን መልካም አጋጣሚ ሁሉ በመጠቀም የፈለገውን ያህል ጊዜ ቢወስድም እንኳ እራሳቸውን እንዲያግዙ ለማስቻል እንደግፋቸዋለን፣ ይህንን የምናደርገው ኮሚኒስቶች ስለሚያደርጉት ሳይሆን ወይም ድግሞ ድምጻቸውን ለማግኘት አይደለም፣ ሆኖም ግን ፍትሀዊ እና ትክክለኛ ስለሆነ ብቻ ነው፡፡ ነጻ የሆነ ህብረተሰብ ሌሎችን ደኃ የሆኑ ዜጎችን መርዳት ካልቻል ጥቂት ሀብታም የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችንም ማገዝ አይችልም፡፡

ለለውጥ አስፋለጊነት በሚያወሳው ንግግራቸው ሴናተር ኦባማ እንዲህ የሚል ጽሁፍ አቅርበው ነበር፣ “ባለፈው ምዕተ ዓመት በተደረገው  ከእንግሊዞች አገዛዝ ነጻ ለመውጣት ጋንዲ ባደረጉት ዘመቻ፣ በፖላንድ የተደረገው የጋራ እንቅስቃሴ፣ ከጸረ አፓርታይድ ጋር በደቡብ አፍሪካ የተደረገው የነጻነት ዘመቻ ስኬታማ ስራ ምክንያት ዴሞክራሲ የአካባቢ መነቃቃት ውጤት ነው፡፡ ሌሎች ሰዎች የእራሳቸውን ነጻነት ለመቀዳጀት እንዲችሉ ማደፋፈር እና ልናግዛቸው ይገባል…መብቶቻቸው እንዲከበሩላቸው መብታቸው የተረገጡትን በአካባቢ አመራሮች ስም ልንናገርላቸው እንችላለን፣ የእራሳቸውን ህዝቦች መብት በተደጋጋሚ በሚደፈጥጡ አምባገነኖች ላይ  የኢኮኖሚ እና የዴፕሎማሲ ጫና መጣል ይኖርብናል…“

“መብቶቻቸውን በተነጠቁ ዜጎቻችን ስም እንዲናገሩላቸው እና ነጻነታቸውን እንዲያስመልሱ“  ፕሬዚዳንት ኦባማ ለሚከተሉት ጀግና ኢትዮጵያውያን/ት ጥቂት ቃላትን ሊናገሩላቸው ይገባል፡ እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ ዉብሸት ታዬ፣ አንዷለም አራጌ፣ ኦልባና ሌሊሳ፣ በቀለ ገርባ፣ አቡባከር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ መርከቡ ኃይሌ፣ ሶሎሞን ፈጠነ፣ ዘሪሁን ተስፋየ፣ አናንያ ኢሳያስ፣ ፋሲካ ቦንገር፣ ጀሚል ሽኩር፣ ሰይፈ ጸጋየ፣ የሽዋስ አሰፋ፣እመቤት ግርማ፣ ዮናስ ከድር፣ እየሩሳሌም ተስፋው፣ አበራ ኃይለማርያም፣ አበበ መከተ፣ ብሌን መስፍን… አስማማው ኃይለጊዮርጊስ፣ ተስፋለም ወልደየስ፣ ኤዶም ካሳዬ፣ አቤል ዋቤላ፣ አጥናፍ ብርሀኔ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ ዘላለም ክብረት እና በፈቃዱ ኃይሉ…?  ከዚህ የተስፋ ጥንካሬ ማህጸን ውስጥ የወጣ የውሸት ተስፋ ነው! “ኦ በመጀመሪያ ጊዜ ማታለል በጀመረንበት ጊዜ ምን ዓይነት የተወሳሰበ ድር እያደራን ነው”

የተስፋ እጥረት፣ 

ኦባማ በኢትዮጵያ እና በአፍሪካ ላሉ አምባገነኖች እያዩ ያላዩ ያሉ በመምሰል እየተመለከቱ ነው፡፡ ለዓመታት ፕሬዚዳንት ኦባማ ለፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬጋን ከበሬታን ሰጥተዋል፡፡ ምናልባትም ከሮናልድ ሬጋን ታሪክ መማር ይችላሉ፡፡ “እያንዳንዱ መንግስት የራሱ የሆነ ልዩ ባህሪ አሉት እናም ያ ባህሪ ከጠፋ መንግስቱም ይወድቃል፡፡ አምባገነናዊነት በተንሰራፋበት ስርዓት ፍርሀት አንዱ ነው፡፡  ህዝቡ አምባገነኑን መፍራት ባቆመ ጊዜ አምባገነኑ ስልጣኑን ያጣል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ አገር ወካይ መንግስት በተዋቀረበት አገር ትልቅ ክብር እና ሞገስ ነው፡፡ ክብር እና ሞገስ በሌለበት ጊዜ መንግስቱ ይወድቃል፡፡ የፖለቲካ ጥርጣሬ እና የሞራል ጥያቄ ያለባቸውን መንገዶች እንመርጣለን? ክብር እና ሞገስን በመተው በእውነታ ላይ ብቻ እንኖራለን?… ይህ ከሆነ ከምናውቀው በላይ ለታሪክ ቆሻሻ መጣያ እየቀረብን ነው፡፡“ የታሪክ መጨረሻው በምጻት ቀን እና በሰው ልጅ ክብር እና ሞገስ መካከል ስልጣንን አላግባብ መጠቀም ሊሆን ይችላልን?

የታሪክ ዳኝነት ፕሬዚዳንት ኦባማ ለሚመጣው ትውልድ የአፍሪካ ዋና አባካኝ ተብለው የሚታወቁበት ይሆናል፡፡ እኛ አፍሪካውያን/ት በኦባማ ላይ ያለንን ተስፋ አቁመናል፡፡ ከባርነት በማምለጥ የነጻነት ሻምፒዮን የሁኑትን ታላቁን አሜሪካዊ የፍሬድሪክ ዳጉላስን ወርቃማ ቃላት በመዋስ፣ ”ማንኛውም ሰው በዝግታ ለምን ግድየለሽ እንደሚሆን እስቲ ተመልከቱ፣ እናም በእነርሱ ላይ የሚጫኑትን የኢፍትሀዊነትን እና ስህተትን ትክክለኛ መለኪያ ታያላችሁ፣ እናም ይህ ጉዳይ በቃላት፣ ወይም በኃይል ወይም በሁለቱም እስካልተወገደ ድረስ ድርጊቱ ይቀጥላል፡፡ የአምባገነኖቹ ወሰን በተጨቆኑት የዝምታ ጽናት ደረጃ ይገለጻል፡፡“

የኢትዮጵያ ህዝብ ጽናት ወሰኑ እስከምን ድረስ ነው?  የአፍሪካ ህዝብስ?

ኦባማ ለኢትዮጵያ ደንታ አላቸውን? ለአፍሪካስ? ኦባማ ለማናቸውም ደንታቸው የላቸውም!

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

ሚያዝያ 28 ቀን 2006 ዓ.ም

 

 

 

 

Leave a Reply