የነጻ ፕሬስና የዝንጀሮ ፍርድ ቤት በእትዮጵያ

Click here for PDF

ከፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም
ትርጉም ከነጻነት ለሃገሬ

እውነት በሃሰት ዲል ሲመታ!

ላለፉት ስድስት ዓመታት ኢትየጵያ ውስጥ ያለውን የፐሬስ ነጻነት ለማስከበር በሚደረገው ግብግብ ውስጥ የትግሉ ደጋፊ በመሆን በርካታ ጦማሮችን ጽፌያለሁ፡፡ በ2009 ባቀረብኩት ርእስ ስር የሰፈረው፤‹‹በኢትዮጵያ ነጻ ፐሬስ አኳያ ያለው የጦርነት ጥበብ›› የሚል ነበር፡፡ በነጻው ፕሬስ ላይ ይዥጎደጎድ የነበረውን የግፍ ጡጫ በተመለከተ ያደረብኝን መገረም ያመላከተም ነበር፡፡ “አንዲት ቢራቢሮን ለመግደል ትልቅ የድንጋይ መፍለጫ መዶሻ ማንሳት! ይሄ ነው እንግዲህ በነጻው ፕሬስ ላይ በ ግፈኛው ፈላጭ ቆራጭ ገዢ መለስ ዜናዊ አላዋቂ ጦር አዝማችነት አሁን የተሰነዘረው ጥቃት፡፡” በ2007 በጻፍኩት ርእስ ‹‹በዝንጀሮ ፍርድ ቤት የአንኮ ፍርድ›› የሚል ሲሆን ጉድለትን ማረሚያ ሃሳቦችን ላለመቀበልና ግድፈቶችን ለማስተካከል የሚሰነዘርን ሂስ ለማፈን በጥቅም ላይ የዋለውን ትርጉም የለሽ ሂደትና በነጻው ፕሬስ ላይ የተቃጣውን የ “ካፍካዊ” የአፈና ዘዴ የተመለከተ ነበር፡፡ ዝነኛው የፍራነስ ካፍካ የመጽሃፍ ጥራዝ፤ የፍርድ ሂደቱ በፍርዱ ውሳኔ ይጀምራል:: “የሆነ ሰው ስለ ዮሴፍ የፈጠራ ወንጀል ሲያወራ ነበር፡፡ አንድ እለት ጸሃይ ገና ስትፈነጥቅ ያለ አንዳች ወንጀልና ያለምንም የማስረጃ ጠብታ ተያዘ፡፡” ከየጌቶቻቸውን ቅዠት በሚያዳምጡትና በቅዠት በሚመሩት የዕውቀት ድሆች በሆኑ ዳኞች ፊት ለፍትህ ቅረብ ተባለ፡፡የዮሴፍ ጉዳይ ያለቀት መስተጋብር ነበር፡፡ የፍረዱ ሂደት ከጅምሩ እስከ መጨረሻው ምንነቱ የማይታወቅ ሚስጥር ነበር፡፡ከፍትሕ ወንበሩ በስተጀርባ በድፍረትና በማን አለብኝነት ማሃይምነታቸውን ተከናንበው፤ አሻንጉሊቶቹ ዳኞች ተብዬዎች ተወዝፈዋል፡፡ ዮሴፍ ክሱ ምን፤ ወንጀሉ ምን የት እንዴት የሚለውን ጨርሶ ስለማያውቅና የሚያውቀው ጉዳይ ቢኖር ንጽህናውን ብቻ በመሀኑ እነዚህ አገልጋዮች ላቀረቡት የፈጠራ ውንጀላ መከላከል አልቻለም፡፡ ምኑን ምን ብሎስ ይከላከል፡፡ ሊመሰክሩበት በሽርፍራፊ ጥቅማ ጥቅም ተገዝተው ስብእናቸውን ሸጠው ሊመሰክሩበት የተዘጋጁትን እቃዎች እንኳን መጠየቅ ማወቅም አልተፈቀደለትም፡፡ የዮሴፍ የፍርድ ሂደት በተደጋጋሚ እየተሰረዘ ይቀያየራል፤ ይዘገያል፡፡ ሕግም ሆነ ስርአት በሌለበት የክስ ሂደት ላይ ጠበቃው ጨርሶ ሊረዳው አልቻለም፡፡

በኢትየጵያ ያለው የመለስ ዜናዊ “ካፋካዊ”  የዝንጀሮ ችሎት በኢትየጵያ የቅጥፈት የፍርድ ሂደት እንግዲህ የዚህ ተመሳሳይ ነው፡፡መለስ ዜናዊም እንግዲህ በእስክንድር ነጋ፤ርእዮት ዓለሙ፤ውብሸት ታዬ፤የስዊዲን ጋዜጠኞች ማርቲን ሺብዬና ጆን ፒርሰን፤የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች አንዱዓለም እና በሌሎቹም ላይ አገኘሁት በሚለው ድል የተነሳ እንገመሬ ዝንጀሮ ደረቱን ሊመታ ሊጨፍር ይችላል፡፡ የሁዩማን ራይትስ ዎች ዘገባ እንደሚያሳየው እስካሁን ድረስ በጠረሽብርተኝነት አዋጁ መሰረት ለእስር የታደረጉት ንጹሃን ቁጥር ወደ 34 ደርሷል፡፡ባለፉት 6 ወራት በኢትዮጵያ 11 ጋዜጠኛች፤በትንሹ 4 ተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊዎች እና 19 ሌለች ለግፍ ወህኒ ተዳርገዋል፡፡

የመለስ ችሎት የዝንጀሮ ፍርድ ቤት ለመሀኑ አንዳችም ጥርጣሬ የለም፡፡የአሜሪካን መንግስትና ሌሎችም የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ይህንኑ በአጽንአት ያረጋግጣሉ፡፡‹‹ከፍተኛ ተብለው በሚጠቀሱ ጉዳዮች›› የኢትየጵያ ፍርድቤቶች የአዝጋሚነት ባህሪ አለባቸው፡፡ አንዳንድ ጊዜ የፍርድ ቤቱ የውንጀላ ተከሳሾች ፋይል ጫና፤በአብዛኛው ደግሞ በፍርድ ስርአቱ ላይ በፈጠሩት አላዋቂ ሳሚ አይነት መሃይምነት የበዛበት ሂደት ስለሚሆንባቸውን እራሳቸው የመሰረቱት የክስ ፋይል እራሳቸውም ሊገባቸው ስለማይችልና ምን እንደሀነ ማወቅ ስለሚሳናቸው ከዚያ ግራ መጋባት ለመውጣት ሲሉ ማስረጃ ለማሰባሰብ በሚል ሰበብ የቀጠሮ ማራዘሚያ ይጠይቃሉ፡፡›› በ2010 የአሜሪካን ስቴት ዲፓርትመንት የየሃገሮች ዘገባ በኢትዮጵያ ስላለው ፍርድቤት ‹‹ሕጉ ነጻ የፍትህ ስርአትን ያዛል፡፡ ምንም እንኳን የሲቪሉ ችለት በተሻለ ነጻነት ቢሰረም፤የወንጀሉ ችሎት ግን እጅጉን ደካማና ስንኩል እንዲሆንና በትእዛዝ ውሳኔ እንዲያስተላልፍ ችግር ሲያጋጥምም ከገዚው መደብ ሃላፊዎች ጋር በሞባይል በመነጋገር የሚፈረድበት የፖለቲካ ውሳኔ ጣልቃ የሚገባበትም ነው::››

በዝንጀሮ  ችሎት ላይ  የተጣለ ውግዘት

በግፍ ለእስር የታደረጉት ንጹሃን ጋዜጠኞችና ሌሎችም እንዲፈቱ፤ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተከራካሪ ድርጅት (ሂዩማን ራይትስ ዎች) ና ሌሎችም ውገዘታቸውን እያስተላለፉ ነው፡፡የጋዜጠኞች መብት ጠባቂ ኮሚቴ ባስተላለፈው ተቃውሞ፤ “የኢትየጵያ መንግስት እንደገና እንደተለመደ ባህሪው፤ ሕጉን ሂሳዊና ነጻ የሆኑትን ዘጋቢዎች እያፈነ ነው፡፡ የኢትየጵያ መንግስት አሁንም በማስፈራራትና በማሰር አለያም ለስደት ከመዳረግ አልተቆጠበም፡፡ ይህም የኢትዮጵያ መንግስት በጣም ቀላልና ሚዛን ለማይደፋ ሂሳዊ አስተያየት እንኳን የመቀበያ አቅም እንደሌለውና ፈቃደኛነት አልባ መሆኑን ያሳያል፡፡” ይህን መሰሉ የህግ አካሄድ በፍትህ ስርአቱ እንዲቀለድበትና አመኔታ እንዲያጣ፤የሚሰነዘሩት ክሶች ሁሉ የቅዠትና የድንብር ግትር ፈጠራዎች እንደሆኑ በመግለጽ፤ ‹‹ይህ ወቅት በኢትዮጵያ የፍርድ ስርአት የጨለመበት ጊዜ ነው፡፡መንግስት አንድም የተቃውሞ ድምጽ እንዳይሰማ ለማድረግ በሚወስደው የግፍ ውሳኔ መሰረት ሃሳብን በነጻ የመግለጹ ጉዳይ ወደ መቃብር እየወረደ ነው፡፡ የፍርዱ ውሳኔ አስቀድሞ የተወሰነ ነው፡፡” በኢትየጵያ የአሜሪካን አምባሳደር ዶናልድ ቡዝ ‹‹የጠንካራና ሰላማዊ ታጋይ ጋዜጠኞች ላይ የሚተላለፈው ውሳኔ  የጸረ ሽብርተኛነት ሕጉ ሕገመንግስቱ ሃሳብን በነጻ ለመግለጽ ከሰጠው ሕገ መንግስታዊ መብት ጋር ለመጣጣሙ ጥረጣሬ እያሳደረብኝ ነው›› ብለዋል፡፡ የአሜሪካኑ ሴኔተር ፓትሪክ ሊሂም ባለፈው ሳምንት ለኮንግሬሽናል ሬኮርድ እንዳስቀመጡት፤ እንደ እስክንድር ነጋ ያሉትን ሰላማዊ ሰዎች  በፖለቲካ ጎራ እንዳይነቀሳቀሱና አስተዋጽአ እነዳያደርጉ እያፈናቸውና እያሰራቸውም ነው›› በማለት የፍትሁን መዛባት በተመለከተ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

የኢትየጵያ ሽፍንፍኑ የጸረሽብርተኝነት ሕጉ ነጻውን ፕሬስ ለማንና ለመወንጀል የተፈበረከ መሀኑ በሰፊው ሲተችበት የከረመ ነው፡፡ እስክንድር ነጋና የሌለች ጋዜጠኞች ለእስራት መዳረግ የዓለም አቀፍ ሁኔታ በሚፈቅደው መሰረት በመንቀሳቀሳቸውና ሃሳባቸውን በሰላማዊ መንገድ በመግለጻቸው ነው ለእስራት የተዳረጉት የራሱን ዜጎች ዴመክራሲያዊ መብት መጠቀምን በሚፈራ መንግስት ነው፡፡ ባለፉት ዓመታት የአሜሪካን ምንግስት አስተዳደር የሚነሱ የሥብር ሁኔታዎችን በማጥፋት በኩል ባለን መግባባት በሚል ለመለስ ዜናዊ እውቅናና ድጋፍ የቸረው ቢሆንም፤ ግንኙነቱን የራሱን ጥቅምና የፖለቲካ ስልጣን ማጠናከሪያ በማድረግ ተጠቅሞበታል ከሽብርተኞች የሚለዩንን ጉዳየች አበክረን መመርመር ይገባናል፡፡በዚህም የሚቸረውን እርዳታ ተቀናቃኝ ሰላማዊ የሕዝብ ወገኖችን ለማፈኛነት እንዳይውል ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል፡፡

አይበገሬዎቹ  እስክንድርና  አንዱዓለም!

ከካፍካው ዮሴፍ በተለየ ሁኔታ ‹‹ እንደውሻ›› ሳይሆን እስክንድርና ዓንዱዓለም ወደ መታሰርያ ቦታቸው ሲመለሱ አንበሳ አደን ውሎ በድል እየተከፈሰ እንደሚመለሰው አይነት ነበር አመላለሳቸው፡፡(ከሺ ጅቦች አንድ አንበሳ የላቀ ክብር ይጎናጸፋል፡፡) ቀደም ብለው ከበላይ ገዢ ጌቶቻቸው በሚፈስ የፍርድ ውሳኔ እንደሚጠናቀቅ ተገንዝበዋል፡፡ በመለስ ዜናዊ የዝንጀሮ ፍርድ ቤት ማንም የተከሰሰ ጋዜጠኛም ሆነ የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊ የክስ መዝገቡ በነጻ የለቀቀው የለም፡፡ መጠርያ ስሙ ከምንም በላይ ገኖ፤ በተጠራ ቁጥር የገዢዎቹን መደብ አባላት የሚያርበደብደው ፤ የኢትየጵያ ፕሬስ ነጻነትም አርማ የሆው እስክንድር ነጋ ለነዚያ እርባና ቢስ ዓላማ ቢሶች መልእክት ነበረው፡፡ ‹‹እኔ ለሰላማዊ ትግል ታግያለሁ፤ ማንንም ግለሰብ ደፍሬ አላውቅም ከክብሩ ዝቅ አድረጌ አላውቅም፤ ምንም ወንጀልም አልፈጸምኩም፡፡ ስለዚህም ከከሳሾቼ በበለጠና እጅጉን በገዘፈ መልኩ ንጹህ ሕሊና አለኝ፡፡ ዝም ሊያሰኙት ሞከሩ››:: በሁልጊዜ ባሕሪው እስክንድር ነጋ ለጉልበተኞቹ እውነትን አሳያቸው፡፡ ‹‹ለፍትህ ልትቀሙ የግድ ነው፤ ሕሊናችን የፈቀደልንን እንድንናገር መብታችን ልትነኩብን አይገባም፤… በነጻ የመናገር መብታችንን ለመገደብ አንዳችም ህጋዊ መብት የላችሁምና፡፡››

በቅርቡ  ታዋቂና የተከበሩ እራሳቸው ለግፈኛ ገዢዎች ጡጫና እስር መከራ የተዳረጉ ዓለም አቀፍ ጋዜጠኞች የእስክንድርን መፈታት በመጠየቅ፤ ከባድ የሆነ ውግዘት በመሰንዘር፤ ‹‹እስክንድር ነጋን በሽብርተኛነት ፈርጀ ማሰሩ አግባብነትና ተቀባይነት የሌለው ነው››ብለዋል:: ጀግናዬ ስለሆነው እስክንድር ነጋ ባለፈው ኤፕሪል ለክብሩ ጥቂት ቃላቶች አስፍሬ ነበር፡፡

እስክንድር ለየት ያለ ጀግና ነው፡፡ ጀግንነቱን ያረጋገጠው ደግሞ ከእውነትና ከሃሳብ ባልራቀ መሳርያው ነው፡፡ ቅጥፈትን በሃቅ ሰይፍ ይቀነጥሰዋል፡፡እኩይ ሃሳቦችን በመልካም አስተሳሰብ ያሸንፋል፡፡ ይህን ሁሉ ሲያደርግ ትጥቁ የሰላ ብእር ብቻ ነው፡፡ እስክንድር ተስፋ መቁረጥን በብሩህ ተስፋ ይዋጋዋል፤ፍርሃትን በቆራጥነት፤ቁጣን በምክንያታዊነት፤ስድነትን በጨዋነት፤መሃይምነትን በእውቀትና ብልሃት፤ ግልፍተኛነትን በእርጋታ፤ ጭቆናን በመቻቻል፤ጥርጣሬን በመታመን፤ ጭካኔን በርህራሄ ያሸንፋል፡፡››

በየቦታው ለተበተኑት የፕሬስ ታጋየች አርማና ኩራት፤ ጀግና የሆው እስክንድር ነጋ፤ እርባና በሌላቸው እራሳቸውን እንኳን በማያውቁ፤ ከመታዘዝና ትእዛዝ ከመቀበል ውጪ እኔ የሚለው ቃል እንግዳ በሆነባቸው ግብስብሶች ለፍርድ መብቃቱ እዬዬዬዬ የሚያሰኝ ነው፡፡

አንዱአለምም ሽንጡን ገትሮ ተናገረ:

ያሳለፍነው ግማሽ ምዕተ ዓመት የኢትዮጵያ ህዝብ ለሰብአዊ ክብሩና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የታገለበት ዘመን ነው፡፡ ይሁን እንጂ የሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶቹ ባለቤት ለመሆን እስካሁን አልታደለም፡፡  እኔም በተፈጠርኩበት በዚህ ዘመን ለራሴ፣ ለልጆቼና ለኢትዮጵያውያን ሁሉ ዴሞክራሲና ነፃነት እንደሚገባን በማመን አቅሜ በፈቀደው መጠን ታግያለሁ፡፡ ይኼን በማድረጌ በማንም ላይ በክፋት አልተነሳሁም፤ ይኼን በማድረጌ ህግ ጥሼ አላውቅም፤ ይኼን በማድረጌ በደሃዋሃገሬ ጥቅም ላይ አልተነሳሁም፤ ይሄን በማድረጌ ፈጣሪዬን፣ የኢትዮጵያን ህዝብም ሆነ ህሊናዬን የሚያሳዝን አንዳች ነገር ፈፅሜያለሁ ብዬ አላምንም፡፡ ፍፁም ሰላምይሰማኛል፡፡ እኔን እዚህ ያቆመኝ የነፃነት ናፍቆት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፍርድ ቤቶችም ፍትህን ለምኜ ስነፈግ ይኼ የመጀርያዬ አይደለም፡፡ ከሳሾቼ እንድጠጣውየሚፈልጉትን የግፍ ፅዋ በፀጋ ከመጠጣት ውጪ ባልፈረፀምኩት ወንጀል ማቅለያ የመጠየቅን አማራጭ ህሊናዬ ስላልተወልኝ አዝናለሁ፡፡

መለስ ዜናዊ ደግሞ ደጋግሞ ነጻውን ፕሬስ የሚከሰው የሚደቁሰው ለምንድን ነው?

ቁጥራቸው አነስተኛ የሆኑትንና ተፍጨርጫሪ የሃገሪቱን የነጻውን ፕሬስ አባላት፤መለስ ዜናዊ ወጥቶ ወርዶ አፋሽ አጎንባሽ ሀኖ ለምንድን ነው የሚፈታተናቸው? ለምንስ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ  መብት ተሟጋቾችን ውግዘትስ መስሚያ ጆሮ የደፈነበት ሰበብ ምንድን ነው? በሃገሪቱ ብዙ መዋእለ ንዋይ የሚያስወጡትንና እርባና ቢስ የሀኑትን ጋዜጦች መጽሄቶች፤ሬዲዮና ቴሌቪዥን ይዞና ከፍተኛ ወጪ የሚያስከትሉ ግን የራሳቸውን ስም እንኳን በአግባቡ መጻፍ የማይችሉ ሁልቆ መሳፍርት የሌላቸውን በቀቀን ጋዜጠኞች የሚያንጋጋው መለስ ዜናዊ ትንሽ ሺወች ቅጂ የሚያወጡትን የነጻውን ፕሬሶች ለምኔ ብሎ ነው ግራ የሚያጋበቸው?

መልሱ በጣም ቀላል አጭርና ግልጽ ነው፡፡ሃቁ! መለስ እውነትን መቀበልም ሆነ እውነት ምን እንደሆነ ጨርሶ አያውቃትምና ነው፡፡ የገዢውን ግፈኛ መንግስት ሙስናውን፤ጭቆናውን፤ችጋሩን፤ጋጠ ወጥነቱን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳየው የግሉ ነጻ ፕሬሱ ስለሆነ ነው፡፡ ነጻው ፕሬስ እሱነቱንና ማለቂያ የሌለውን ውድቀቱን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳየው ነጻው ፕሬስ ስለሆነና ያንን መቋቋም ስለማይችል ነው፡፡ የሕብረተሰቡን ትክክለኛ አስተሳሰብና አመለካከት ለመስማትና ሕዝቡ የሚሰነዝረውን አስተያየት አዳምጦ ድክመቱን ለማወቅ ብቃቱም ፈቃደኛነቱም ስለሌለው የእውነት ነጸብራቅ የሆነውን ነጻ ፕሬስ ማድመጥም መስማትም አይችልም አይፈልግም፡፡ ድክመቱን ነቅሰው በማውጣት የሕዝብን ጉዳትና ስሜት በመከታተልና በማወቅ ሲነግሩት ከመስማትና ከማስተካከል ይልቅ ተደፈርኩኝ ባይነትን ዋነኛ የጀግንነት ማስመሰያው አድርጎ መኖርን ይመርጣል፡፡ በአካባቢው ያጎራቸው እርባና ቢሶችም በተናገረ ቁጥር እልታቸውንና ጭብጨባቸውን ስለሚያቀልጡለትና፤ ንግግሩን በመቀባበል ያለ አንዳች ማገናዘብ እየደጋገሙ የማሰልቸት ቱልቱላቸውን በመንዛት ያላንተ ማን አለ በሚሉት የሆድ መሙያ ውሽከታቸው በማሞገስ ያልሆነውን እያደረጉት ወደ ጥፋት ገደል እየገፉት ቢሆንም እሱ ግን ሽንገላቸውን እውነት ብለ እራሱን በማታለል የሚኖር ነውና እውነትን ይፈራታል፤ ከእውነት ጋር ደግሞ የግል ፕሬስ ማህበርተኛ በመሀኑ እሱንም ይጠላዋል ይፈራዋል፡፡

በቅርቡ በአረቡ መንደር በታየው ክስተት መረዳት እንደሚቻለው፤ጨቋኝ ገዢወች ከአሸዋ እንደተሰራ ግንብ ናቸውና በቀላሉ የባህር ወደብ ሲነኩ ፍርክስክሳቸው ይወጣል፡፡ ምንም ያህል ሕዝቡን ቢያስፈራሩትና የነጻውንም ፕሬስ ቢያዋክቡት በመጨረሻው ግን በታላቁ የሕዝብ ውሳኔና መነሳሳት በአቧራ መሰብሰቢያ ተጠራርገው ወደ ታሪካዊ ቀሻሻ መጣያ መወርወራቸው አይቀሬ ነው፡፡

በነጻው ፕሬስ ላይ ወከባውና ጠርነቱ ይቀጥላል...

ወከባውና ጦርነቱ በሃቅ ላይ ያነጣጠረ በመሆኑ የነጻውን ፕሬስ ማዋከቡ ይቀጥላል፡፡ብቸኛው በሃገር ውስጥ በመንቀሳቀስና ፍንክች ያባ ቢላ ልጅ ባለው በፍትሕ ጋዜጣ ላይ የታወጀው ጦርነት ለወከባው መቀጠል ማስረጃ ነው፡፡ዘመቻው በጣም ዝቅተኛና ተራ አሉባልታዊ ሂደት ያለበት፤ተንኮሉ ተራ ያልተገራ ግልቢያ የሚመስል፤ጸሃፊውም ሆነ አርሞ ይሁንታ የሰጠው ውሸት ያለቀበት ተላላኪ መሆኑ በይፋ ይታያል፡፡ይህን የሚያደርገው የስለላ ቡድንም በፍትሕ ላይ ያነጣጠረውን የውንጀላ ዳር ዳርታ በዚህ መልኩ ማድረጉ ሃገሪቱ በምን አይነት ሰዎች እንደምትጠበቅ የሚያሳይና የሚያሳፍር ነው፡፡የፍትሕ ጋዜጣን ዋና አዘጋጅ ተመስገን ደሳለኝን ከአልሸባብ ጋር ግንኙነት እንዳለው አስመስሎ በማዘጋጀት ወደ ኢሜይሉ መላክ ቢያሳፍርም እነሱ ላኪዎቹ ግን ድል አደረግን ጉድ ሰራነው ብለው እየተጨባበጡ ሳይገባበዙ አይቀሩም፡፡ ያሳዝናል ተራ የውንብድና ተግባር ነውና! ኢሜይሉ በአልሸባብ ሰዎች እንደተዘጋጀና ወደ ተመስገን ሲላክ በሰላዮች ተጠልፎ የተያዘ ለማስመሰል ከንቱ ጥረት ተደርጓል፡፡

እንደሚታወሰው አልሸባብ በሚስጥር በኢትዮጵያ፤በሶማሌላንድ፤በኬንያና ኡጋንዳ የሽብር ቅስቀሳ ስራ እንድሰራ መድበኛል፡፡ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ እንድችል ከወኪልህ ከአቶ ማሙሽ ፈንቴ ጋር ኤርትራ ውስጥ ተገናኝተን በጋዜጣህ ላይ የፕሮፓጋንዳ ጽሁፎች ለማተም በተደረሰው ስምምነት መሰረት የኢትዮጵያንና የአሜሪካንን ጥቅም የሚገዱ ጽሁፎች ለማተምም ያንተን ስምምነት አግኝተናል፡፡

ምነው ብትተዉን  ጃል!

ይሄ እኮ አዲስ አይደለም ላለፉት በረካታ ዓመታት ያየነው ነው፡፡የመለስ ዉንጀላ ሶስት ደረጃ አለው፡፡መጀመርያ ተቃዋሚ አስደንጋጮቹን ለማሳነስ ይመክራል:: ለጥቆ ይወነጅላል፤ በሶስተኛው ስብእናቸውን ይነጥቃል፡፡ በእስክንድር ነጋ፤ በአንዱዓለም አራጌ፤በዳዊት ከበደ እና በለሎቹም ላይ የፈጸመው  ደባ ይህንኑ ነው፡፡አሁን ደሞ ፍትሕ በአንደኛው ደረጃ ላይ ነው፡፡ስም ማጥፋትና ወንጀል ማግበስበስ፤ ተመስገን ደሳለኝና ፍትሕ አሁን በስም ማሳነሱና ማጥፋቱ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡በቅርቡ የገዢው ስርአት ንብረትና አፈ ጉባኤ በሆኑት መገናኛዎች ሁሉ ‹‹አሸባሪዎች፤‹‹ሰርጎ ገቦች›› ‹‹ጠብ ጫሪዎች›› ‹‹የሽብር ሴራ ቀስቃሾች›› ‹‹የውጭ ቀጥረኞች›› ‹‹ሰላዮች›› ሌላም ሌላም በመባል የንባብና የጽሁፍ መማርያ አፍ መፍቻ ይሀናሉ፡፡ ልክ በእስክንድር ነጋና አንዱ ዓለም አራጌ ላይ እንደተፈጸመው ሁሉ ከጥቂት ቀናት በኋላ በመንገድ ላይ ሲያዝ በቪዲየ ይቀረጽና የተመስገን መታገት ይወራል፡፡ (አስክንድር ነጋ በታገተበት ወቅት የነበረውን ዘግናኝና አሳፋሪ የሰላዮች ተግባርና በዚያ በሽብር ወቅት ሕጻን ልጁ ሲያለቅስ እነዚያ ለሰው ክብር፤ ለሕጻናት ርህራሄ የሌላቸው ማፈሪያዎች ሲፈነድቁና ሳቅ በሚመስል ግልፈጣ ሲያጓሩ ያሳዩትን ቪዲዮ ሁሉም ሊያየው ተገቢ ነው፡፡)

ከዚያም የተጀመረው የስብእና ማራከስ ሂደት ይቀጥላል፡፡ማሰቃየቱ፤ ፍርድ ቤት ከመቅረብ አስቀድሞ ዱላው፤ ሕክምና መከልከል፤ ከቤተሰብ ጋር ግንኙነት መከልከል፤ በየቀኑ እስረኛ መዘለፍ፤ ለብቻ ለይተ ማሰርና ሌላም ሌላም የግፍ ጫና ይከተላል፡፡ በመጨረሻም የተመስገን ደሳለኝና የሌለቹም የፍትህ ጋዜጣ ባለሙያዎች የፍርድ ጨዋታ በዝንጀሮዎቹ የፍትህ አደባባይ አምባሳደሮችና የውጭ ዓለም አቀፍ ድርጅተች ወኪሎች፤ የንጹሃን ተከሳሸች ቤተሰቦች በአዳራሹ በሚገኙበት ይቀጥላል፡፡ወዲያውም የፍርዱ ውሳኔ ይነበባል… ጥፋተኛ፤ ጥፋተኛ፤ ጥፋተኛ…15 አመት.. 20 አመት… የሞት ፍርድ…

ሁሉም ነገር ሳያታለም የተፈታ ነው!

ዘመቻው ይከሽፋል፤ ጠርነቱ ግን በአሸናፊነት

ይህ በኢትየጵያ ያለው የነጻው ፕሬስ ያላለቀ ታሪክና በውስጡ የሚገኙት የባለድሎችና የፍትህ አልባዎች እጣ ፈንታ መንታ ስለት ያለው ሰይፍ በመዘዙ ግፈኛ ፈላጭ ቀራጭ ገዢዎችና የተባእራቸውን፤ እርሳሶቻቸውን፤ የኮምፒዩተር መተየቢያ ቦርዳቸውን በአነገቱ ጋዜጠኞች የሕዝብን አመኔታና ፍቅር ይሁንታ ለማግኘት በሚካሄደው ጦርነት ይለያል፡፡ የዚህ ጦርነት ውጤት ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ተፈትዋል ብዬም አምናለሁ:: ኤድዋርድ ቡልዌር­-ሌተን በግጥሙ እንዳሰነበበው የመጨረሻው ድል ያላንዳች ጥርጥር የብእር አንጋቢዎቹ ነው፡፡

እነሆ እውነት!

ከሰዎች  አገዛዝ  በጣሙን የላቀ

ከማንኛውም ሃይል የብእር ሃይል ነው እጅግ የመጠቀ

የአጎብጓቢዎች ድንፋታ ምንም ላይፈይድ

ከጌቶቻቸው አፍ በሚሰነዘር ፍርድ

አይበገሬዎችን ለማንበርከክ ዱካቸውን ለማጥፋት

የማይወጡትን መሞከር የማይቻለውን መመኘት

ምድር ድምጽ አልባ መስላ እየታዘበች

ሰይፉ ይውደቅ ትላለች ብእርም; ሃገርን ታድናለች፡፡

ሆኖም: ታላቁ ጥያቄ ሃገርን ማዳን ወይስ ነጻውን ፕሬስ ማዳን ከሆነ: እኔ ቶማስ ጄፈርሰን እንዳለው ሁሉ ሁለተኛውን እመርጣለሁ፡፡ ‹‹የመንግስታችን  መሰረቱ የህብረተሰቡ አመለካከት በመሆኑ፤ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባወም ያንን ማስከበር ነው፡፡መንግስት ያለ ጋዜጣ ይኑረን ወይስ ጋዜጣ ያለመንግስት የሚለው ሃሳብ ቢቀርብልኝ እኔ ሁለተኛውን ለመምረጥ ቅንጣት ታህል ጊዜ አልፈጅም::››

የጠላቶቻችን ተግባርና፤የወዳጆቻችን ዝምታ

ደ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግ እንዳሉት ‹‹የጠላቶቻችንን ቃሎች ከምናስታውስ ይልቅስ የወዳጆቻችንን ዝምታ እናስበዋለን›› እኔ ደግሞ፤ የጠላቶቻችንን ተግባርና ግፋዊ ድርጊት እያሰብነው ይቅርታንም እንቸራለን የሚያደርጉትን አያውቁትምና፡፡ የሚፈጸመውን ግፍ፤የሕዝብ መብት ገፈፋ፤ የሰብአዊ መብት መጣስን፤የፍትህን እጠትና ሌላውንም ሁሉ እያዩ እነዳላዩ እየሰሙ እንዳልሰሙ በመሆን ጀሯቸውን የጠቀጠቁትን፤ አፋቸውን የለጎሙትን፤ አንደበታቸውን የዘጉትን ወዳጀቻችንን ግን ይቅርታም አልቸር ልረሳውም አልፈቅድም፡፡

በእስር ስር ያሉትን ዘወትር አብረናቸው እንዳለን ከማሳወቅና እንዳልረሳናቸውና እንዳልተውናቸው ከማሳየት የላቀ ምንም ተስፋ የለም፡፡ እስክንድር ነጋ አንዱዓለም አራጌ ርእዮት ዓለሙና ሌሎችም የግፍ ታሳሪወች በጨካኝና ግፈኛ ገዢ ዋሻ ውስጥ ናቸው፡፡ በየእለቱ ነፍሳቸው እንዲሳሳና እንዲንበረከኩ እየተደረጉ ነው፡፡ ይህን ደግሞ አንሰማውም ዋሸው ጥልቅ መዝጊያው ድርብ ነውና፡፡ ድምጻቸው ታፍኗልና ድምጻቸው ልንሆንና ልንጨህላቸው ይገባል፡፡ ያሉበት ቦታ የግፈኛው አገዛዝ የግፍ ዋሻ በትንፋገት የተሞላና ለበሽታ የሚያጋልጥ በመሆኑ ስቃያቸው ሊሰማን ተገቢ ነው፡፡ ስለኢትየጵያ የፐለቲካ እስረኞች ጉረሯችን እስከሰል መጨህ ያለብን ለታይታ ሳይሆን፤ግዴታችን፤ክብራችን፤ትክክልና እውነትም በመሆኑ ነው፡፡ በመጨረሻም፤ የኢትየጵያ ፍጻሜ ሊሆን የሚገባው የግፍ ገዢዎችና ፈላጭ ቀራጮቹ እንደሚያስቡት ግልብነት አይደለም፤ ጭካኔ፤ግፍ፤ኢሰብአዊነት ሳይሆን፤ ያለሃጢአታቸው ለተዘጋባቸው ወገኖቻችን ክብር ስንል  በሰብአዊነት፤ በክብር፤በመደማመጥ፤ በመግባባት፤ በአንድነት መሆን አለበት፡፡ለዚህም ነው በአንድ ላይ እጅ ለእጅ በመያያዝ ላለመድከም ለራሳችን ቃል ገብተን፤ጥሪዎችን በማዳመጥ ብቻ ሳይሆን አዳምጦ በመቀላቀል፤ ያለ እረፍት በኢትዮጵያ ያሉትን የፐለቲካ እስረኞች የነጻነት መድረሻ ማፋጠን አለብን፡፡

በኢትዮጵያ ያሉ ሁሉም የፐለቲካ እስረኞች ይፈቱ!

የእትዮጵያ ነጳ ፕሬስ ነጳ ይሁን!

ካሁን በፊት የቀረቡ የጸሃፊው ጦማሮችን  ለማግኘት እዚህ ይጫኑ::

http://www.ecadforum.com/Amharic/archives/category/al-mariam-amharic

http://ethioforum.org/?cat=24

Leave a Reply